ስምን መልአክ ያወጣዋል ይላሉ፤ አጽንቶ የሚያቆየው ደግሞ ግብር ነው። ስማቸው በግብራቸው የሚደምቅ ታዲያ ሰዎች ብቻ አይምሰሏችሁ፤ አገራትና ከተሞችም ጭምር እንጂ። እንደምናውቀው አገራችን ደግሞ በዚህ የታደለች ናት። ስማቸውን ስንሰማ ብቻ ከዳሽን ተራራ የገዘፈ ታሪክና እውነትን የምናስታውስባቸው ሰዎች፤ ስማቸው ከመጠራቱ ከእልፍ ሄክታር ማሳ የበለጠ በረከትና ፍሬ የተገኘባቸው እንደሆኑ የምናውቃቸው ከተሞች አሉ። እንዲህ ካሉ የአገሬ ክፍሎች መካከል ጎንደርን ለማየት እድሉን አገኘሁ። እድለኛነት ነዋ! ያለሁበት የሥራ መስክ በተለያየ አጋጣሚ የተለያዩ ከተሞችን እንዳይ መንገድ ሆኖልኛል። «ሰው የገዛ አገሩን እንዴት አያውቅም? የአገር ውስጥ ጎብኚኮ በጣም ጥቂት ነው» እያልኩ የምፈርድ ሰው ያደረገኝ ይኸው ሥራዬ ነው። እንጂ ሌላ ቦታ ብሆን ከተፈራጆቹ መካከል እገኝ አልነበር! ጎንደርን በመጻሕፍትና በትዕይንተ መስኮት አይቻታለሁ፤ ከሚያውቋት ብሎም ከሚወዷት አንደበት ሰምቻታለሁ። ለአገር አንድነት ዘመኑን የሰጠ፣ ስለአገር ክብር ሕይወቱን የከፈለ ንጉሥ ተወልዶባታል፤ ዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ።
እነ አፄ ፋሲልና ቤተመንግሥታቸውን አኑረውባታል፤ በኪነ ህንጻ ጥበብም ተራቅቀውባታል። ይህን ብቻ ሲሰማና በምስል ሲያይ የኖረ ሰው፤ ምን ጠብቆ ይሄዳል ትላላችሁ? እንግዲህ ያ ሰው እኔው እህታችሁ ነኝ። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቤተመዛግብትና ቤተመጻሐፍት ኤጀንሲ ያዘጋጀው «ማንበብ ሙሉ ሰው ያደርጋል» የንባብ ሳምንት ነበር የጉዞው ምክንያት። ከተቋሙ ግቢ በር አፍ ላይ የተነሳው መኪና የመጀመሪያውን ቀን ባህርዳር አፍሮ በማግስቱ እኩለ ቀን ላይ ጎንደር ደርሷል። ሙቀቱ አይሏል፤ የነገሥታቱን ቤተመንግሥት፤ የዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስን መታሰቢያ ሃውልት ለማየት የጓጓው ዓይኔ ከተማዋ በዘለቅንበት ቅጽበት ወዲያና ወዲህ ሲያማትር ነበር። ገጠር የኖረ ሰው ከተማ ሲገባ በየመንገዱ የሚያልፈውና ያለፈው ሁሉ ደንቆት እንደሚያይ፤ አስተያየቴ እንደዛ ሳይሆን ይቀራል ብላችሁ ነው? መቼም ከተሜ እንጂ ታዝቦ የሚስቅ፤ ባላገሩ «አይ የጨዋ ነገር! ወዲህ ላሳይሽማ!» እያለ ያስረዳል፤ ያሳያል። የኔ ነገርም በታሪክና በዝና የምታውቁትን ሰው በአካል እንደማግኘት ነበር።
ምን ያደርጋል ፖስታ ነጋዴው ቢያመጣ መገናኘት ነበር ናፍቆት የሚያወጣ…» እንዳለ አቀንቃኙ፤ እስከዛች እለት ስለጎንደር ከሰማሁት፣ ካነበብኩትና ካየሁት በላይ በአካል ስገኝ አዲስ ሆነብኝ። «ፍሬሽ» ሆንኩኝ በሉት። ያው «አላውቅም…ንገሩኝ» የሚል ሰው አይደለ የጠፋው? ጠያቂ ሆኜ ተገኘሁ። የመጀመሪያ ቀን ማረፊያችን ተስተካክሎና ቀጣይ ሥራዎች ከታወቁ በኋላ በመረጋጋት ከጎንደር ጋር ለማውጋት ጊዜ ተገኘ። ጎንደር በየማለዳው ከፀሐይዋ ጋር አብራ የምትሞቅ ከተማ ነች። ሽር ጉድና ግርግሯም እንደ ፀሐይዋ ቀስ እያለ ነው የሚሞቀው። ጎንደርን ከአረንጓዴ ቢጫ ቀይ ሰንደቅ ዓላማ ጋር እኩል ያያት ሰው ኢትዮጵያን ያይባታል፤ ጎንደር ቁልጭ እናቷን ኢትዮጵያን ትመስላለች። ተመልካች በከተማዋ ከፍታ ላይ ሆኖ ቢያይ፤ ጸጉሩ ገባ ገባ ይል እንደጀመረ ጎልማሳ፤ ተራሮቿ ተገልጠው ይታያሉ። በእነዚህ የሳሱ ስፍራዎች ላይ ደግሞ ጅምር ዘመናዊ ህንጻዎች በብዛት አሉ፤ አላለቁም። ምንአልባት ሲያልቁ ውበት ሊሆኗት ነበር፤ በጅምር መቅረታቸው ግን ዐይን ይሰብራል። የውበት ማረፊያ ዙፋን የነበረችና የሆነች ጎንደር፤ የቀደሙት አፈር አልመው ተጠብበውና ተመራምረው ቤተመንግሥታት የገነቡባት ጎንደር፤ በ«ዘመናዊ» ጅምር ህንጻዎች ተነካክታለች።
እድገት ጉዞ ነው፤ ሮጠው የሚደርሱበት ጠርዝ አይደለም። የሳር ጎጆዎች ወደ ዘመናዊ ቤት እየተቀየሩ ሰዎች የተሻለ ኑሮ እንዲመሩ ያስፈልጋል። ግን ቀለምን ባያስቀይር ብለን ደግሞ እንመኛለን። እንግዲህ አትቀየሙኝ፤ ጎንደርን የሚመስልና ስለጎንደር የሚናገር ህንጻ እና ቤት የማየት ጉጉቴ ነው ያናገረኝ። ከዛ ውጪ ግን እውነትም ለመናገር ጅምር ህንጻዎቹ ለመቀጠላቸው ምንም ምልክት የማይታይባቸው መሆኑም ያሳስባል ። ያየሁትን ልንገራችሁ! ጎንደር መሃል ከተማ ፒያሳ የሚባል አካባቢ አለ። ይህ ሰፈር ልክ እንደ አዲስ አበባ ፒያሳ መልኩ፣ መታጠፊያው፣ አኳኋኑ ሁሉ ይመሳሰላል። እንደውም ሞቅ አደረግሽው ካላላችሁ፤ ሰፈሮቹን በደንብ የማያውቅ ሰው የአዲስ አበባው ፒያሳ ተኝቶ የጎንደሩ ፒያሳ ቢነቃ ልብ የሚል አይመስለኝም። እና ምንአልባት እነዛ ጣልያኖች በአገራችን ወዲያ ወዲህ ባሉበት ጊዜ የተከሏቸው ህንጻዎች፤ ስለእነርሱ ሳይናገሩ ይቀራሉ ብላችሁ ነው? ጣልያን ይህን ያደረገች እኛስ በገዛ አገራችን ምን ያንሰናል? ስለጎንደር የሚናገር፤ ጎንደርን በወፍ በረር የሚያሳይ፤ ታሪኳን ቁልጭ የሚያደርግ፤ የነፋሲለደስና የሠርጸ ድንግል ማረፊያ መሆኗን የሚያሳውቅ ምልክት ፈልጌባታለሁ። የጎንደር ዩኒቨርስቲ በዚህ የሚመሰገን ነው። ውስጥ ዝርዝርና ትንታኔ ውስጥ ባንገባም፤ ከመግቢያው ጀምሮ የጎንደር መሆኑን ይናገራል። እልፍ እንበል፤ የጎንደር ምሽት በአዝማሪዎች ቅኔና መሰንቆ ይደምቃል። ክፍት በር ካገኙ ወደ አገራችን ሙዚቃ ዘርፍ እንደ ንብ እየተመሙ ሊገቡ የሚችሉ ድምጻውያን አሏት፤ ጎንደር። ይግረማችሁ! ሁሉም ደግሞ ገጣሚ ነው።
ባህልንና ታሪክን ብቻ አይደለም፤ ከጎንደር ጥበብ ይቀሰማል። ሻገር ብለን ማክሰኚትና እንፍራንዝን፤ እንዲሁም ጉዛራን አየን፤ የሀገር ስሜት፣ ፍቅርና ቁጭት እዚያ አለ። እስከዛሬ ያላባራ ወኔ ከየጎንደሬው ዐይንና ስሜት ይነበባል። ፍቅሩና ስሜቱ ለአገር ነው፤ ቁጭቱ ደግሞ ለትውልድ። ባለማስተዋል ብሎም በመደንዘዝ እየጠፋ ስላለ ትውልድ ጎንደር አዝናለች። በጥበብ የሚጠሩ የነበሩ እንደ እንፍራንዝ ያሉ ከተሞቿ በጫት ስማቸው ይጠራ ጀምሯል። ወቅታዊ የፖለቲካው ትኩሳትም ደርሷታል፤ ታተኩሳለች። እና ይህ ሁሉ ተደማምሮ እንዴት አይቆጭ!
ቆይታችን ከአንድ ሳምንት የዘለለ አልነበረም። ወገኛ አትሉኝም? ጎንደር እንኳንና በአንድ ሳምንት ተወልደው ኖረውባትም ሁሌም አዲስ መሆኗን እዛው የተዋወቅኳቸው ወዳጆች አውርተውኛል። በየቀኑ አዳዲስ ስንኝ እንደሚቀባበሉ አዝማሪዎች፤ አዲስ ነገሮችን ይዞ እንደሚገኘው ቀን፤ አዲስ ሆና እንደምትወጣው ፀሐይ፤ በጎንደር ሁሌም አዲስ ነገር አለ። ጎንደር ውበቷ፣ ክብሯና ድምቀቷ አንድም ሰላሟ ነውና፤ ያ አዲስ ነገር ሁሌም መልካም እንዲሆን እየተመኘን ቆይታችንን አጠናቀቅን። ቅድም ብያችሁ ነበር፤ ጎንደር ቁልጭ እናቷን ኢትዮጵያን ትመስላለች። እንዴት ሳትሉኝ ቀራችሁሳ! ታሪክና ባለታሪክ ያገነናት፤ የብዙ ጥበብና ሀብት ባለቤት። ኩሩና በሥራው የሚመካ ሕዝብ ያለባት፤ ብዙ ሆኖ በአንድ መኖርን አውቆ፤ «አንተ ጎንደሬ…እንደ አገርህ እንደ አገሬ» የሚባባሉባት ጎንደር፤ አዎን! አቃፊዋን እናት ኢትዮጵያን ትመስላለች። እናቷም ልክ እንደእርሷ ናት። የገነነች፤ የታፈረችና የተከበረች አገር። ዘመንና ልጆቿ ከፍ አድርገዋት የነበረ፤ አሁን ደግሞ በየዕለቱ ክፉዋን ላለመስማት ሁሉም በሰቀቀን የሚጨነቅላት። ጎንደርና ኢትዮጵያ በዚህ ይመሳሰላሉ፤ ዘመንበትውልድ እየገመገመ፤ በአቅም እየፈተነ፤ በፖለቲካ እያነደደ ይከታተላቸዋል። ሁለቱም ግን ተስፋ አይቆርጡም፤ አለን ይላሉ፤ ደኅና ነን ይላሉ።
በዚህ ላብቃ እንጂ ይህ የነገርኳችሁ በአቅሜ ካፈስኳቸው መካከል አንዷ ፍሬ ወይም ጠብታ ናት። ብቻ «አትሂዱ! ክረሙ» ብላ እንዳታግደረድረንና እንዳታስቀረን፤ ፀሐይ ሳትወጣ ማልደን ከጎንደር ተነስተን ወጣን። ጉዞ ወደ ሸገር፤ አዲስ አበባ። ሰው ከትምህርት ቤት መልስ፣ ከሥራ መልስ፣ ከቀጠሮ መልስ፣ ከተዝናኖት መልስ ወዘተ አብሮ ይዞት የሚመጣው ነገር አለ አይደለ? እኔም ከጉዞ መልስ ያመጣሁት አለኝ። ከጎንደር መልስ ሁለት ነገር ያዝኩ፤ አንደኛ ከእንግዲህ ለጎንደር እንግዳ አለመሆኔን አወቅሁ። ሌላስ? ቀና ለማለት እየጣረች ያለች አገሬን በጎንደር ውስጥ አየኋት። አንጀት የምትበላዋን፣ ልጆቿን የምትጣራዋንና «አስተዋይ ሁኑልኝ» የምትለዋን አገር ተመለከትኳት። «የሄድሽበት ሥራስ?» ካላችሁ ያው የሄድኩበት የሥራ ጉዳይማ በሌላ ገጽ ይቆየን፤ ከብሔራዊ ቤተመዛግብትና ቤተመጻሐፍት ኤጀንሲ ጋር ልታጣሉኝ ነው? ሰላም!
አዲስ ዘመን የካቲት 12/2011
ሊዲያ ተስፋዬ