ምህረት ጫንያለው
እያንዳንዱ ነገር በወቅቱ ሁኔታ መዋጀት አለበት ብዬ አስባለሁ።ከዚህ አንጻር ሽፍትነትም እንደየወቅቱ ሁኔታ ታይቶ ትርጉም ሊሰጠው ይገባል።የቀደመ ሽፍትነትን ከዛሬው ጋር ሲተያይ ብዙ የማይወዳደሩ ነገሮች ያሉበት ነው።ወቅቱ ሰውን ሲቀይር የሽፍታውንም ምልከታ በዚያው ልክ ቀይሮታል።ለዚህም የቀደመው ሽፍታን ባህሪ ማንሳት ብቻ በቂ ነው።ይህ ሽፍታ ወደ ጫካ የሚገባበት ምክንያት አንዳንዱ ከአሁኑ ጋር ቢመሳሰልም ፍጹም የሚለይበት ጉዳይም ግን አለው።ለዚህም በአብነት የሚነሳው የቀደመው ሽፍታ በአገር ጉዳይ የማይደራደር፤ መሞት ካለበት የሚሞት ነው።እንደውም የሸፈተበት ጉዳይም አገሩን ከያዘው መንግሥት ለመታደግ ሊሆንም ይችላል።
ከዚህ የሚልቀው ደግሞ እንደዛሬው ንጹሐንን እየገደለና ለእርሱ ማመጺያ እየተጠቀመ አለመሆኑ ነው። ይልቁንም ንጹሐንንን የሚያሰቃይን አይታገሱም።ቆጥሮ፣ ነጥሎ ከፊታቸው ገሸሽ ያደርጋልም።ሰውነትን በእጅጉ የሚረዳ፣ የሚራራም ነው።ከእነርሱ በላይ ፊት ለፊት በሕዝቡ ላይ የሚደረግበት ጭካኔ ጫካ ከገባው ስለሚበልጥም አብዛኛው ሰውም ቢሆን ይህንን ስለሚያውቅ መረጃ ጭምር የሚሰጠው፣ የሚያከብረውና የሚወደውም ነው።
የዛሬውስ ከተባለ ሽፍነቱ የተለየ መልክ አለው።ከእነዚህ በብዙ ነገር ይቃረናል።ለዚህ ደግሞ ብዙ ማሳያዎችን በመጥቀስ መናገር ይቻላል።በዋናነት የምናነሳው ለፖለቲካ ፍጆታ ንጹሀንን መጠቀሙ አንዱና ዋነኛው ነው።ከእኛ ውጪ አገርን የሚመራ መኖር የለበትም፣ አገር የሚባል ስያሜ ጭምር ሊነሳ አይገባውም መፈክራቸው ነው።ይህ ብቻ ሳይበቃቸው አለመረጋጋትን በተለያየ መልኩ መፍጠራቸውም ሌላው መለያቸው ሆኗል።ህጻን አይሉ፣ ሴት፣ አረጋዊ አይሉ ወጣት ሁሉንም በመደዳ ደርድረው ካሻቸው ይረሽናሉ፤ አለያም የማይገባ ተግባር እንዲከውኑ ያስገድዷቸዋል።
እነርሱን እንዲከተሉም እድሜያቸውን ጭምር ግምት ውስጥ ሳያስገቡ ያሰልፏቸዋል።ከመሳሪያው በላይ ጥላቻን እንዲታጠቁም ያደርጓቸዋል።ምክንያቱም መሳሪያ ስጋን እንጂ ልብን አይገልም።ማንነትንም አይሰብርም።በዚህ ደግሞ ማሸነፍ በፍጹም አይታሰብም።ስለዚህም የእነርሱ ራዕይ ይሳካ ዘንድ አንድነትን ድምጥማጡን ማጥፋት ያስፈልጋልና በቤተሰቦቻቸው ላይ ጭምር እንዲዘምቱ ያደርጓቸዋል።በጎረቤቶቻቸው ላይም የሌላቸውን ማንነት እንዲያሳዩ ይሞሏቸዋል።በዚህም ጎረቤት ጎረቤትን ውጣልኝ ይላል።ከዚያም አልፎ ቤቱ ውስጥ በተኛበት በእሳት ሊያጋየው ይነሳል፤ ያደርገዋልም።ብሔር ተገኑ ሆኖ ውጣልኝን አንግቦ በዝምድና ብቻ ሳይሆን በሥጋ የተሳሰረውን ጭምርም እያጋጩት መቃቃሩ አገር ሰላም እንዳትሆን የዘየዱት መላ ነው። ይህ ደግሞ መቼም በቀላሉ የሚፈታ አልሆነም።
ግብጽ ምናምን ነች ይህንን የምታደርገው እያልን ለእነዚህ አካላት ሽፋን መስጠቱ ተገቢነቱ ብዙም አይታየኝም።ምክንያቱም እነርሱ በራሳቸው ኢትዮጵያዊነታቸውን ክደው እንቧ ከረዮ እያሉ ሌለኞቹ ግብጻውያንን ሆነዋል።አገራቸው ከገንዘብና ስልጣን በላይ ዋጋ የላትም።ምክንያቱም እንደፈለጉ አልቆራረጧትም፣ እንደፈለጉ ሊሰብሯት አልቻሉም።ለሌላም እየሸጧት ኪሳቸውን በገንዘብ ህሊናቸውን በውሸት መሙላት አልቻሉም።እነርሱ በስሟ እየለመኑ ስልጣናቸውን ማስጠበቅም አልሆነላቸውም፡፡
በአገር ሰላም ኪስ በገንዘብ እንደሚሞላ ፣አዕምሮ በነጻነት እንደሚፋፋ አልተረዱም።ሁሉም ሲያሸረግድልን ማየት የሚመጣው አገር ሰላም ስትሆን እንደሆነ አያውቁትም።ምክንያቱም በጉልበት እረግጠው ዝም አሰኝተው ስለኖሩ አሁንም ያንን ማድረግ ይፈልጋሉ።ምሱ የቀረበት ሰይጣን ደግሞ የሚያደርገውን እንኳን አያውቀውም።ነገር ግን ይህ ረሀብ ላይ የሆነን አካል እናድሰው፤ ስልጠና ሰተን ለአገሩ ይሁን ተባለለት።ውስጡና ውጪው ሳይናበብ የቀረ ሰው መሆኑ እየታወቀ የአገር መከታ እንዲሆን ተፈቀደለት፡፡ይህ በመሆኑ አሁንም አገር ሰላም እንዳትሆን የሚፈልግ አካል እንዳለ ይሰማኛል።ምክንያቱም የዚህ ሽፍትነት ማስክ እንጂ ንጹህነት አይደለም።እንደቀደመው የአገር ልብም የለውም።
ዛሬ ትውልዱን ለመውቀሻችን መነሻው አገር ጠል የሆኑ ባለስልጣናት እንደሆኑ ግልጽ ነው።ምክንያቱም አገር እንዲወድ ሳይሆን ብሔሩን እንዲያመልክ አድርገው አሳድገውታል።በዚህም አገሬ ሳይሆን ብሔሬ ቅድሚያ ያግኝ ቦታውን ተፈናጥቶታል።በሽፍትነት የገባውም አካል በተለያየ መንገድ እያወቅነው ያለነው ህወሓትና አጃከሮቹ እንዲሁም ኦነግ ሸኔና ባለውለታዎቹ ናቸው።ታዲያ ያንን አምጥቶ ሁለት ወር አሰልጥኖ ግባ ከምን የመጣ ነው? እነዚህ አካላት እድሜ ልክ ስልጠና ቢሰጣቸውስ አገር ከመበጥበጥና ንጹሐንን ከመገበር ይርቃሉ ብሎ ማሰብስ ከምን መጣ? መልሱ ግልጽ አይደለም።
አገር የሚወድ ሽፍታ በራሱ ጊዜ ሽፍትነቱን ይተዋል።ከሕዝቡ ጋር የሚቀላቀልበትን መንገድም ያመቻቻል።አሁን እየተደረገ ያለውን የለውጥ ሥራም የሚቃወም አይሆንም።ይህ ደግሞ ተጠያቂነትን የሚፈራበት ምክንያት ምንም እንደማይኖረው የሚያሳይ ነው።ስለሆነም ተጠያቂነት መቅደም አለበት።ይህንን የሚፈልግ ደግሞ መጥቶ ይጠየቃል እንጂ አይሸሽም፣ አይሸፍትምም።መንግስት ጨካኝ ነው ብሎ ቢያስብ እንኳን ጓደኞቹ የሚያደርጉትን ተግባር እያየ አይቀመጥም።እጁን ሰጥቶ ለሕዝብ ነጻነት ሲል ይሞታል።
ለሽፍቶቹ መስመር ጠቋሚ የሆኑ ባለስልጣናትንም መመርመር ተገቢ ነው።እንደሚታየው አንዳንድ አመራሮች አቅጣጫ ጠቋሚ ሲሆኑ ይስተዋላል።ለመያዝ አልቻሉምም።ለዚህም ማሳያው ወታደሮች ሲወጡ በየት በኩል ወጡ የሚለውን ለዛኛው ወገን ይነግሩታል።አስበውበትም ወታደሩ ከዚያ እንዲነሳ ያደርጋሉ።እናም ማንም ሰላም አስከባሪ ባልነበረበት ሁኔታ ላይ ንጹሐኑ እንዲፈጁ ያደርጉና ለአስታራቂነት ይቀመጣሉ።ስለዚህም እነዚህን አስፈጂ አስታራቂ መሰል አመራሮችንም ለአገሩ ከሚሰራው ለይቶ ማውጣት የመንግሥት ድርሻ መሆን ይገባዋል።ጅምር ብቻ ሳይሆን ጥልቅ የሆነ ተግባርም ያስፈልገዋል።ምክንያቱም ማስክ አድራጊው እንክርዳድ በዝቷልና።
በመጨረሻ ማለት የምፈልገው የመንግሥት አሰራር በተለይም በወታደራዊ ኃይሉ ላይ ያለውን አመራር መፈተሽ ለነገ የማይባል መሆን አለበት።በዚህ ዘርፍ ላይ ብዙ ግልጽ የሆኑ ለውጦችን ቢደረጉም አሁንም አረሙ ሙሉ ለሙሉ አልተነቀለምና ለውጦች በአንዳንድ አድር ባዮች እንዳይዘወሩ ማድረግ ቀዳሚ ተግባር መሆን ይኖርበታል።ዛሬ ሰው ወንድሙን ጭምር መፍራት ጀምሯል።ምክንያቱም ገንዘብና ሌሎች ጥቅማጥቅሞች ዓይናችንን ጋርደውታል።የቀደመ ፍቅራችንንም ቀምቶናል።ብቻውን የበላ ብቻውን ይሞታል፣ ድር ቢያብር አንበሳ ያስር፣ ሀምሳ ሎሚ ለአንድ ሰው ሸክሙ ለሀምሳ ሰው ጌጡ የሚሉት መልካም አባባሎቻችን በሌላ ተተክተዋል።ብቻዬን የሚለው ሀሳብ ንግስናውን ይዟል።እናም መንግሥትም ይህንን አውቆ ሰው ተቀምሶ ባይታወቅም ከምግባሩና ከሥራው እየለየ ለአገር ሰላም ይሰራ።ሕዝብም ከጎኑ ይሰለፍ።
አሁን ያለው ሁኔታ ጊዜ የሚወስድ ሊሆን ይችላል።ከአንድ ትውልድ በላይ የተሰራ ጥላቻ በቀናት፣ በወራትና በጥቂት ዓመታት ሊፈታ አይችልም።ነገር ግን አቅጣጫን እያስተካከሉ ካልሄዱ ረጅም ዓመታትም ይህንን ማስተካከል አይችሉምና ቅድሚያ የሚሰጣቸው ነገሮች ቅድሚያ ያግኙ።በተለይ በተለይ ግን አገርን አገር የሚያሰኛት ሰው ነውና ሰው አይሙትብን። እናም ወታደራዊ አመራሩ ላይና ይቅርታ የሚሠጣቸው አካላትን ለይቶ በማወቅ በኩል መንግሥት አጥብቆ ይሥራ።ሕግ ማስከበሩም ቢሆን ከመቼውም በላይ ይጠናከር።ተጠያቂነት ያለበት አካል ሳይጠየቅ ምንም ውስጥ አይግባ።ማስተማርም ከእነዚህ ተግባራት ይጀምር እያልኩ ሀሳቤን ልቋጭ።ሰላም !
አዲስ ዘመን ሚያዚያ 7/2013