ወቅቱ ዜጎች ከሀገሪቱ ጎን በመቆም ርብርብ ማድረግ የሚጠበቅባቸው መሆኑን ማንም ይገነዘበዋል መንግስት በትግራይ ክልል የህግ የበላይነትን አስከብሮ በጁንታው የወደሙ መሰረተ ልማቶችን መልሶ በመገንባት እና በመጠገን ላይ ተጠምዷል። በክልሉ ከሚያስፈልገው ሰብአዊ ድጋፍ 70 ከመቶው እየቀረበ ያለው በመንግስት ነው። የፈረሰውን የክልሉን አስተዳደር በአዲስ የመተካት ስራም እየተከናወነ ነው።
ሁሉም ስራዎች ከፍተኛ መጠን ያለው ሀብት ይጠይቃሉ። መንግስት ያለ የሌለውን ሀብት መድቦ እየሰራ ነው። ዜጎች፣ባለሀብቶችና ክልሎች ድጋፍ እያደረጉ ናቸው።
ወቅቱ ሀገሪቱን እንዳሻን ማድረግ የምንችለው አሁን ነው ያሉ የውጭ ሀይሎች በሀገሪቱ ላይ የተሰለፉበት ነው። ሱዳን የኢትዮጵያን ድንበር አልፋ መሬት ይዛለች። መንግስት ችግሩን በዲፕሎማሲያዊ መንገድ ለመፍታት መስራቱን ቀጥሏል።በዚህ ላይ በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ድርድር ላይም የሌላ ሶስተኛ ወገን አጀንዳ ይዛ እየተንቀሳቀሰች ትገኛለች።መንግስት የግድቡ ድርድር በአፍሪካዊ መፍትሄ እንደሚፈታ በማመን ጉዳዩን በጥሞና እየተከታተለው ነው።
ራሱ በከፈተው ጦርነት የተደመሰሰው የጁንታው ርዝራዦች አሁንም አርፈው አልተቀመጡም። እነዚህ ኑራቸውን በውጭ ሀገር ያደረጉ ርዝራዦች ነጭ ውሽት በማሰራጨት ላይ ተጠምደዋል። በዚህም አንዳንድ የአለም አቀፉን ማህበረሰብ ድርጅቶች፣ ሀገሮችንና አለም አቀፍ መገናኛ ብኃንን እያሳሳቱ ናቸው። የህግ ማስከበሩን፣ሰብአዊ ድጋፍ የማቅረቡንና የመሳሰሉትን የመንግስት ስራዎች በመቃወም ላይ ተጠምደዋል። በዚህ እኩይ ተግባር በህግ ማስከበር ዘመቻው አገሪቱ በጁንታው ላይ የተቀዳጃቻቸው ድሎች እንዲሸፍኑ ለማድረግ እየጣሩ ናቸው።
አሁን ነገሮች እየተለወጡ መጥተዋል እንጂ በተወሰነ መልኩም ቢሆን አንዳንድ ሀገሮችና ተቋማት አብረዋቸው እንዲቆሙ ያደረጉበት ሁኔታ ታይቶ ነበር። የእናት ጡት ነካሾቹ ሀገሪቱ ላይ ማእቀብ እንዲጣል ነበር የተረባረቡት። ምስጋና ለኢትዮጵያ መንግስትና በውጭ ሀገር ለሚኖሩ ኢትዮጵያውያን እንዲሁም ወዳጅ ሀገሮች ያሰቡት ግን አልተሳካም።
ይህ የዜጎች ርብርብ በእጅጉ ሊደነቅ ይገባዋል።ርብርቡ በሀገር ውስጥ የኢኮኖሚ አሻጥር እንዳይደረግ በመተባበር ጭምር መደገም ይኖርበታል።
በሀገራችን በአሁኑ ወቅት የኑሮ ውድነት እየታየ ነው።የኢንዱስትሪ ውጤቶች ዋጋ ብቻ ሳይሆን የግብርና ምርቶች ዋጋ ጭምር በዚህ ምርት በተሰበሰበት ወቅት መረጋጋት ሲገባው እየጨመረ ይገኛል።
እርግጥ ነው በቅርቡ በሀገራችን የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ በተደጋጋሚ ታይቷል። ይህን ተከትሎም የትራንስፓርት ታሪፍ ክለሳም ተደርጓል። እንደ ተለመደው እንደ ሀገር የውጭ ምንዛሬ እጥረት እንዳለም ማንም ይገነዘበዋል።እነዚህ ሁሉ ግን አሁን የሚታየውን ያህል የዋጋ ጭማሪ ሊያስከትሉ አይችሉም።
በሸቀጦችና የግብርና ምርቶች ላይ የተደረገው የዋጋ ጭማሪ የነዳጅ ዋጋ ከመከለሱ በፊትም መታየት የጀመረ ነው።ጭማሪው በየቀኑ የሚደረግ ይመስላል፤ የዛሬው ዋጋ ከትንሽ ቀናት ጨምሮ ይገኛል።
ለነገሩ በሀራችን ጤነኛ የዋጋ ጭማሪ በመንግስት በኩል ተደርጎ ካልሆነ በስተቀር ተደርጎም አያውቅም ።ምክንያት እየፈጠሩና ምክንያት እየፈለጉ ዋጋ መጨመር የሐገራችንን የንግዱ ማህበረሰብ መሰረታዊ ችግር ነው።
ሀገሪቱ በተለያዩ ችግሮች ውስጥ ባለችበት በአሁኑ ወቅት ሳይቀር በሌለ ምክንያት እንዲሁም ነዳጅ ጨመረ ብሎ ዘግናኝ የዋጋ ጭማሪ ማድረግ በእጅጉ ያስፍራል፤ የወቅቱ የሀገሪቱ ጠላቶች ተባባሪ ከመሆንም አይለይም። በሀገሪቱ ሰላምና መረጋጋት እንዲመጣ አጥብቀው ሲጠይቁ ከነበሩት መካከል የንግዱ ማህበረሰብ ዋናው ነው። ምክንያቱም ሰላም ከሌለ እንደልብ እየተዘዋወሩ መነገድ አይቻልምና ነው።መንግስት ይህን ጥያቄ ለመመለስ ያለ የሌለ አቅሙን እየተጠቀመ ባለበት በዚህ ወቅት ዜጎችን በዋጋ ጭማሪ መጉዳት መንግስትን መውጋት ነው።
የንግዱ ማህበረሰብ አባላት የዋጋ ጭማሪ ማድረግ የሚያስችል ምክንያት ሲኖር አግባብ ያለው የዋጋ ጭማሪ ቢያደርግ ማንም አይቃወምም። ነጋዴው ለጽድቅ አይሰራምና ተገቢ ነው።
የሀገራችን የንግዱ ማህበረሰብ የመጣበት መንገድ ጤነኛ አይደለም። ዋጋ የሚያስጨምር ሁኔታ ሲፈጠር የሚያደርገው ጭማሪ ጤነኛ ሆኖም አያውቅም።በዚህች ተለዋዋጭ ነገር በሚደጋገምባት ሀገር የተለዋወጠው ዋጋ ተዘርዝሮ አያውቅም። በሀገሪቱ ዋጋ ወደፊት እንጂ ወደ ኋላ ተመልሶ አያውቅም።
ምክንያቱም ስግብግብነት ነው። ምክንያቱም ቢያጡ ቢያጡ ቁጭ ብለው ምክንያት ይፈበርካሉ። ቅቤ ነጋዴ ሁሌም ስለድርቅ ነው የሚያወራው እንደሚባለው የሌለ ችግር ፈብርከው ዋጋ በመጨመር ይታወቃሉ።
በእርግጥ ነጻ ገበያ ነው፤ ነጻ ገበያ አንድ ነጋዴ የፈለገውን ምርት አምጥቶ በአሻው ዋጋ የሚሸጥበት መንግስት ጣልቃ የማይገባበት ስርዓት ነው፤ ስርዓቱ ግን ልቅ ነው፣ መንግስት አይቆጣጠረውም ማለት አይደለም። የዋጋ ጭማሪው ግን ልቅና የመንግስትን የቅርብ ቁጥጥርና ክትትል የሚፈልግ ሆኖ ቆይቷል።
ይህም ስር የሰደደ ችግር ነው።መንግስት እየተደረገ ያለው የዋጋ ጭማሪ ኢኮኖሚያዊ ምክንያት የለውም እያለ መጋዘን ሲፈትሽ፣ ሱቅ ሲያሽግ ነጋዴ ሲቀጣ ፣ዋጋ ሲተምን ኖሯል። ዋጋ ላይ ለጊዜው የሆነ ለውጥ ይመጣና ተመልሶ እዚያው ችግር ውስጥ ይወድቃል።
በቅርቡ ሀገራችን በርካታ ችግሮች ውሰጥ መሆኗ እየታወቀ እንደ ዜጋ ማሰብ ጭምር በተሳናቸው አንዳንድ የንግድ ማህበረሰቡ አባላት አስደንጋጭ የዋጋ ጭማሪ ተደርጓል። ዋጋው የሚጨምረው ደግሞ በአናት በአናቱ ነው። መጋዘን ውስጥ ባለ ምርት ላይ የዋጋ ጭማሪ በማድረግ መክበር ተለምዷል።
ሀብት የሚገኘው ሀገር ስትደማ ወይም ስትለማ ነው የሚሉ ወገኖች እንዳሉ ይነገራል።እነዚህ የንግዱ ማህበረሰብ አባላት ሀብት የሚገኘው ሀገር ስትደማ ነው ከሚሉት ናቸው።አሁን በምርቶች ላይ የተደረገው የዋጋ ጭማሪም ከዚሁ አኳያ ሊታይ ይገባዋል።ሀገር በብዙ መልኩ ችግር ውስጥ ባለችበት በዚህ ወቅት ኢኮኖሚያዊ ምክንያት ሳይኖር የተደረገ ዘግናኝ ጭማሪ ነው።ይህ አመለካከት በጭራሽ መቀየር አለበት።
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እየተደረገ ያለው የዋጋ ጭማሪ ለየት የሚያደርገው ከጨመረው ነዳጅ ጋር ከጠፋው ዶላር ጋር ተያይዞ የመጣ አለመሆኑ ነው፤እነዚህ ሁለት ነገሮች ማለትም ዶላር እና ነዳጅ ለዋጋ ጭማሪ ከፍተኛ ሚና የሚጫወቱ እንደሆነ ይተመናል። የአሁኑ የዋጋ ንረት ሰው ሰራሽ ነው፤ ይህም ዶላርም ሆነ ነዳጅ ሳይጨምር የገቡ ምርቶችን በመደበቅና ምርቱን ከገበያ በማጥፋት የተደረገ ጭማሪ ነው።ይህ ደግሞ የኢኮኖሚ እና የፖለቲካ አሻጥር ነው።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በቅርቡ ያካሄደው ጥናት የሚያስገነዝበውም ይሄንኑ ነው። ጥናቱን ዋቢ ያደረገ መረጃ እንዳመለከተው፤ በከተማዋ የኑሮ ውድነቱ የተከሰተው በፖለቲካ አሻጥር የአዲስ አበባን ህዝብ ለማማረር ታስቦ ነው፤ የኑሮ ውድነቱ የተከሰተው ምርቶች ወደ አዲስ አበባ እንዳይገቡ እና የገቡትም በተዛባ መንገድ እንዲሸጡ በሚያደርጉ ህገ ወጦች ነው።
ይህ ችግር በቀጥታ የሚመለከታችሁ ነጋድራሶች/ነጋዴዎች/! በዚህ አስቸጋሪ ወቅት ከአገር ጎን በመቆም የበኩላችሁንም ድርሻ ትወጡ ዘንድ እመክራለሁ፤ በያዛችሁት የተሳሳተ መንገድ ሆናችሁ እንኳ ብታተርፉ ፤ የአተረፋችሁትን የምትበሉት አገር እና ህዝብ ሲኖር ነው ፤ከገባችሁበት ከየትኛውም አሻጥር በመውጣት አገር እና ህዝብን ወገንን አስቀድሙ!
አዲስ ዘመን መጋቢት 5 ቀን 2013 ዓ.ም