ዳግም ከበደ
ትህነግ ጥጋብና እብሪት ውስጥ ገብታ ጥቅምት 24 ቀን 2013 አ.ም የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ሰሜን እዝን “መብረቃዊ ጥቃት” ባለችው ግፍ ከጀርባ ወግታለች። ድርጊቱ በየትኛውም የአለም ፅንፍ ያልታየ ፊልም በሚመስል መልኩ መላው ኢትዮጵያን አስቆጥቶ መንግስት አፀፋዊ ምላሽ እንዲሰጥ አስገድዶታል።
የትህነግ ጁንታ ቡድን /ወንበዴዎቹ/ ሶስት ዓመት ሙሉ የተዘጋጀበት የጦርነት ድግስና የገነባው ምሽግ እንዲሁም ለ30 ዓመታት የዘረፈው የኢትዮጵያውያን ሃብት ሳያስጥለው ለሶስት ሳምንታት ብቻ በተደረገ የህግ ማስከበር ስራ ወደ ቀበሮ ጉድጓዱ እንዲመለስ ተደርጓል።አሳፋሪ ጥቃት የፈፀመው ጁንታው አሳፋሪ ሽንፈት ተከናንቦ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከኢትዮጵያውያን ጫንቃ ላይ ተወግዷል።
መንግስት ጁንታውን ቢያስወግድም፣ ርዝራዦቹ የተሳሳተ መረጃ በማሰራጨት በያዙት የፕሮፓጋንዳ ስራ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ይህን የህግ ማስከበር ዘመቻ በተሳሳተ መንገድ እንዲረዳው አድርገዋል።
የጁንታው ካድሬዎችና ተላላኪዎች ግን የመንግስት ህግ የማስከበር ዘመቻ የተለየ ይዘት እንዲኖረው ለማድረግ ከመስራት አልቦዘኑም።የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ማድረጉን ከጦርነቱ እኩል ነው የጀመሩት። ከሀገር የዘረፉትን ሀብት ለእኩይ ድርጊታቸው ተባባሪዎች እየከፈሉ /ሎቢ ማድረጊያ/ እየተጠቀሙ የፕሮፓጋንዳ ስራውን ተያይዘውታል፡፡
ኢትዮጵያ ወንበዴው ቡድን እንዳይነሳ በማድረግ እውነታዋን ይዛለች።በቡድኑ የወደሙ መሰረተ ልማቶችን በመገንባት፣ሰብአዊ ድጋፍ በማድረግና መልሶ ግንባታ ላይ ትገኛለች፡፡ይሁንና ይህ ሁሉ ጥረቷ በውጪ ጣልቃ ገብነት ጫና እንዲደበዝዝ እየተደረገ ነው። ይህ የሆነው በህግ ማስከበር በተገኘው ድል ላይ በዲፕሎማሲያዊው ዘርፍ ይህ ነው የሚባል ስራ ባለመሰራቱ ነው ብሎ መውሰድ ይቻላል።
ድሉ በዲፕሎማሲው መድረክ ባለመደገሙ ምክንያት የተፈጠረው ጫና መስተካከል ይኖርበታል በሚል ስንወተውት ቆይተናል። በአንዳንድ አገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን ሲደረግ ከነበረው ከልብ የመነጨ የቡድኑን የተሳሳተ መረጃ የማጋለጥ ስራ ውጪ በመንግስት መዋቅር ውስጥ ያስተዋልነው የዲፕሎማሲ እንቅስቃሴ እጅግ ደካማ እንደነበር ገልጸን መስተካከል ይኖርባቸዋል ያልናቸውን የመፍትሄ ሃሳቦችም ጠቁመን አልፈናል። በትህነግ መሰባበር ማግስት የታዩ የዲፕሎማሲ ስራዎች ማሻሻያዎችን በማድነቅ ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ከማሳሰብም አልቦዘንም።
ዛሬስ?
የጁንታው ተላላኪዎች ዛሬም በዓለም አቀፍ መድረኮች በፕሮፓጋንዳ ዘመቻ እየተወራጩ ናቸው። ቀበሮ ጉድጓድ ውስጥ የቀሩ ርዝራዦቹ ረጅሙን ምላሳቸውን ወደ ባህር ማዶ አካላቸው መዘርጋታቸውን ቀጥለዋል። ዓለም አቀፉ ማህበረሰብና ያልተጣራ መረጃ በማግበስበስ የሚታወቁት የምእራባዊያኑ ሚዲያዎችም የትህነግን ካድሬዎች ፕሮፓጋንዳ ሳያላምጡ እየዋጡት ይገኛሉ። ይህም እውነት በእጃቸው የሚገኘውን ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያውያንን ዋጋ እያስከፈለ ነው።
መንግስት አገራዊ ሃላፊነቱ ብዙ ነውና የጁንታውን “ጠረን ሳይቀር” ከኢትዮጵያ የማጥፋት ዘመቻውን በሁሉም መንገድ መቀጠል ይኖርበታል። ከመንገዶቹ ዋንኛው ያካሄደው ዘመቻ ጁንታውን እና ተላላኪዎቹን መደምሰስ ላይ ያተኮረ እንጂ የሰብአዊ መብት ጥሰት ማድረስና ህዝብን ለጥፋት ማድረግ አለመሆኑን ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ በአግባቡ ማስረዳት መሆን አለበት።ለዚህም ድጋፍ ለማግኘት ዲፕሎማሲ ስራ ማካሄድ ይኖርበታል።
በዚህ ደረጃ ከመጀመሪያው አንስቶ መንግስት ደካማ አካሄድ እየተከተለ ስለመሆኑ በርካታ ማሳያዎች አሉ። ሚዲያዎችን ሆነ የተለያዩ አለም አቀፍ ተቋማት ጭምር የትህነግ ርዝራዥና ሌቦች በሆኑ አካላት ተጠልፈዋል።
እውነት ጫማዋን እስክታስር ውሸት ብዙ ርቀት ትሮጣለች እንደሚባለው የትህነግ አምላኪ ድልብ ዲያስፖራዎች በዓለም አቀፍ አደባባይ ላይ ያለ ሃፍረት እየተንደባለሉ የአዞ እንባ ሲያነቡ እያስተዋልን ነው። አንዳንድ እውነታውን ያልተገነዘቡ አሊያም ደግሞ ተገንዝበው አይናቸውን የጨፈኑ ምእራባዊያን አብረዋቸው ለቅሶ ተቀምጠው ኢትዮጵያ ላይ ጫና ለመፍጠር እየሞከሩ ይገኛሉ።
መንግስትም ይህን ለመቀልበስ የሚያስችለውን የዲፕሎማሲ መድረክ የምር ይዞታል ብለን ለመናገር እየከበደን ነው። የአምባሳደርነትና የዲፕሎማሲ ወንበሩን በፖለቲካው ያኮረፉና ብቃት የሌላቸው አካላት እየመሩ ያሉበት ሁኔታ የማሸሸጊያ ስፍራ እንዲያገኙ አርጓቸዋል በሚል በርካታ ማስረጃዎችን ጠቅሰው የሚከራከሩ አካላት አሉ። ይህን ትችት እንድንቀበል በህይወት የሌለው ትህነግ አሁንም ድረስ ምላሱ መርዘሙና የኢትዮጵያ መንግስት ለምዕራባውያኑ ጫና ተላልፎ እየተሰጠ ያለበት ሁኔታ ይህንኑ ያመለክታሉ።
በዲፕሎማሲው መስክ በአንዳንድ ከፍተኛ ባለስልጣናት ለጊዜውም ቢሆን የተሰሩና ውጤት ያመጡ ስራዎች መኖራቸውን እናምናለን፤የተቀናጀ ተቋማዊ ስራ ቀጣይነት ባለው መልኩ እየተሰራ አለመሆኑን ግን እያየን ነው፤ የሀሰት ዘመቻው መድራትም ይህን ያስገነዝባል።
በውጭ ሀገር የሚገኙ የትህነግ ርዝራዦች ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በኢትዮጵያ ላይ አለም አቀፍ ጫና ወይም እቀባ እንዲደረግ አጥብቀው እየሰሩ ባሉበት ሁኔታ ይህን የሚመክት ጉልህና ቀጣይነት ያለው ስራ በዲፕሎማሲው መስክ እየተሰራ አይደለም።ይሄ ሊታረም ይገባል። ለእዚህም የዲፕሎማሲ መድረኩ በድጋሚ ሊፈተሽ ይገባል እንላለን። እስከነአባባሉ “ጦር ከፈታው ወሬ የፈታው” ነውና ኢትዮጵያውነትንና ኢትዮጵያን ለማጥፋት ቀን ከሌሊት በፕሮፖጋንዳ እንቅልፍ አጥተው የሚሰሩ አካላትን በጥበብ መመከት እንደሚያስፈልግ ዛሬም ደግመን እናስገነዝባለን።
በዋናነት ትህነግ በስልጣን ላይ በቆየባቸው ዓመታት ያደረሳቸውን መቅሰፍቶች በግልፅ ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብና ህዝብ ይፋ ማድረግ ያስፈልጋል፤ ጦርነቱን ራሱ አሲሮና ለኩሶ አገር ሊያፈርስ ቀጣናውን ሊያምስ ሲል በመንግስት እርምጃ እንደተወሰደበት በተደጋጋሚ በማሳያዎችን እያስደገፉ ማሳወቅ ይገባል።
የሽብር ቡድኑ ደጋፊዎች ሲያሻቸው በዝርፊያ በገዙት ቅንጡ መኪና የዓለም አደባባይን ሲያጨናንቁ ሲላቸው ደግሞ እንደ አህያ በረዶ ላይ ሲንደባለሉ መክረማቸው አሁንም ያን የዝርፊያ ሰንሰለት ለማስቀጠል ሀሳቡ ያላቸው ስለመሆኑ መንግስትና የሀገሪቱ ወዳጆች ማጋለጥ ይኖርባቸዋል። ይሄ ደግሞ በእለት ተእለት የዲፕሎማሲ ስራ ብቻ የሚከናወን ሊሆን አይችልም፤ለታላቁ የህዳሴ ግድብ የተደረገውን አይነት ታላቅ ዲፕሎማሲያዊ ዘመቻ ማድረግን ይጠይቃል።
በትግራይ ክልል የሰብዓዊ ድጋፍ አስፈላጊ መሆኑ እርግጥ ቢሆንም የፖለቲካ አላማቸውን ለማስፈፀም ሁኔታውን ከጣራ በላይ አጋነው የሚያቀርቡ በተራድኦ ድርጅት ስም የሚሰሩ አካላትን በመረጃ ከማጋለጥ ጀምሮ እውነታውን ማስረዳት ለነገ የሚተው ጉዳይ አይደለም።
እንደ መውጫ
ሰሞኑን የፀጥታው ምክር ቤት በኢትዮጵያ ላይ እስከ መምከር ያደረሰውና ምዕራባዊያኑም ጣልቃ ገብተው በአገራችን ሉአላዊነት ላይ ለመፈትፈት ያሰፈሰፉት በዲፕሎማሲው መድረክ ላይ የደረሰብን ሽንፈት አንድ መገለጫ ነው። ስብሰባው ያለስምምነት ተጠናቅቋል፤ ይህ የሆነው ግን በእኛ ብልሃት የተሞላበት እውነትን አደባባይ የማውጣት ስራ ሳይሆን በወዳጅ አገሮች ጥረት መሆኑን መካድ የለብንም። ከዚህ ብዙ መማር ይኖርብናል። የትህነግን ምላስ እስከወዲያኛው ቆርጦ መጣል እንደሚያስፈልግ የሰሞኑ ጫና አሁንም ሊያስተምረን ይገባል።
መንግስት የዲፕሎማሲውን መድረክ የሚያሳልጡ ባለሙያዎችንና ባለስልጣናትን አካሄድ መፈተሽ ይኖርበታል። በዚህም ለዘላቂ ኢኮኖሚያዊ ጥቅም አብረን የምንሰራቸው አገራት በወዳጅነታቸው እንዲቀጥሉ እንዲሁም ሌሎች ሉአላዊት አገራችንን ከመድፈር እጃቸውን እንዲሰበስቡ ማድረግ ያስፈልጋል። ለዚህ ነው በተደጋጋሚ መንግስት ዲፕሎማሲያዊ ስራዎችን በጥልቀት ይፈትሽ እያልን የምንጮህው። ሰላም!!
አዲስ ዘመን የካቲት 28/2013