በዛሬ ወጋ ወጋ አምዳችን ገበያው ላይ ህመም መፍጠር የሚሹ፣ አሁንም ለበሽታው መባባስ ምክንያት ሆኑ ተዋናዮችን ተግባራችሁ ጥሩ አይደለም እንላቸዋለን።ስራችሁም ለአገርና ለህዝብ ጎጂ ነውና ታቀቡ ልንላቸው ወደናል፡፡ ለበሽታቸው መዳን ይሆን ዘንድ መፍትሄ የምንለው መርፌ እነወጋቸዋለን፡፡ የሚሰሩትን ተገቢ ያልሆነ ስራ ጠቅሰን ልክ አለመሆኑንና ስራቸው በልክ እንዲያደርጉት እንነግራለን፡፡
ገበያ ስናነሳ ስለሸማቾች ፣ነጋዴዎችና ደላሎች እያነሳን ነው፡፡ ገበያችን ሥርዓት የለውም ብቻ ሳይሆን ቅጡ የጠፋ ሆኗል፡፡ የተወሰኑት ነጋዴዎቻችን ደርሰው ባለፀጋ የሆኑና የከበሩ ናቸው፡፡ የቀሩት ደግሞ የነሱን ፍኖት በመከተል ለማትረፍ የሚጥሩ ይመስላሉ። በማትረፍ ካባ የመዝረፍ ደባ የሚፈጽሙ ናቸው፡፡ “ሆድ ዕቃ” የሌለው ዳቦ ሲሸጡልን እያተረፉ (ን) ሳይሆን እየዘረፉ እና እያጠፉን ይመስለኛል፡፡ እንደውም ሳስበው እምነት የላቸውም ወይ? እንዴት ቢጨክኑ ነው? እላለሁ፡፡
የሚገርመው ደግሞ እነዚህ ገበያው ላይ አሻጥር የሚሰሩ ነጋዴዎች ግብርን መሸሻቸው ነው፡፡ መገበር እያለባቸው የማይገብሩ ነጋዴዎች ገበያው ላይ እነቅፋት ሲፈጥሩ አሰባችሁት፡፡ መገበር እያለባቸው የማይገብሩ ብዙ ነጋዴዎች በርካቶች ናቸው፡፡ ፈረንጆቹ የደረሱበት መድረስ የሚቻለው የሚገብረውን በማስገበር ነው። የሠራ ሲገብር ለሀገሩ ግዴታውን እየተወጣ ነው። ለሰላምና ለደህንነት ኃይሎች እየከፈለ መሆኑ ማሰብ አለበት።መቼም በመነገድ ውስጥ መንገዳገድ አለ፡፡ በተለይ በመነገድ አሻጥር ካለበት ይዘገያል እንጂ መውደቅ የማይቀር ነው፡፡
ነጋዴዎቻችን ማህበራዊ ህይወት የሚባለውን አያውቁትም ፤መነገድን ብቻ አስበው የሚንቀሳቀሱ ናቸው፤ በመነገድ ውስጥ ማገልገልም የሚባለውን ሰብአዊ ትርፍ አያውቁትም፡፡ ህዝቡ በማትረፍ ስም በነጋዴዎችና ደላሎች እየተዘረፈ ነው፡፡ ለነገሩ ለመቆጣጠርም እኮ መቆጣጠር የሚችለው አካል፤ አካል ሲኖረው ነው፡፡ ብንተሳሰብ አይሻልም ጎበዝ? ነጋዴ ከሸማች ጋር ሲተጋገዝ ያተርፋል ድሮ ዳቦ በዕንቁላል ሲበላ አስታውሳለሁ (ሳንድዊች) ዘንድሮ ደግሞ ዳቦ በብስኩት ልክ እንደሳንደድዊች ተደርጎ ሲባላ እያየሁ ነው። ከላይ እንደገለጽኩት ዳቦ ቀፎ ስለሆነ እንቁላሉ ደግሞ ዋጋው መጥፎ (ውድ) ስለሆነ ማለት ነው፡፡
ለዚህ ደግሞ መርካቶ ውስጥ ውጥንቅጡ የወጣ ህብረተሰብን ኑሮ ማየቱ ተገቢ ነው፡፡ በድህነትና በጉስቁልና የሚኑሩ የመርካቶ ዜጎች ከመርካቶም እምብዛም ያተረፉት ነገር የለም፡፡ እርግጥ ነው የተወሰኑት ልዩ ልዩ ሙያዎችን በቦታው በልምድ አግኝተው እየሠሩ ይኖራሉ፡፡ መርካቶን እንደ ምሳሌ አነሳነው እንጂ በሌላም ክፍል/ ከተማ የሚኖሩ ተመሳሳይ ይመስላሉ፡፡
የመርካቶው ነጋዴ መርካቶ እየነገደ ኑሮውን እያሳመረ ተሽከርካሪ እንደ ሸሚዝ እየቀያየረ ያማረ የሰመረ ቤት ሠርቶ ሲኖር፤ በመርካቶ ኑሮውን ላደረጉ የተወሰኑ ድሆች ቤታቸውን አድሶ ለመሥራት ኑሮዋቸውን ለማሰማመር ሲጥሩ አይታይም፡፡ ይህ ደግሞ ከማህበራዊ ህይወት አንዱ ነው፡፡ ራስንም ድርጅትንም ማስተዋወቅ የሚሉት ነገር ማሰብ ይቻላል፡፡ ይሄ መቼም የነጋዴው ብቻ ሳይሆን የክፍለ ከተማው ዝርክርክ አመራሮች ውጤት ብዬ አስበዋለው፡፡ ቀን መርካቶ ሠርተው አትርፈው ማታ ግን ቆሻሻቸውን መርካቶ አፍሰው ቤታቸው የሚሄዱ ናቸው። ችገሩ ግን ያለው መርካቶዎች ላይ ብቻ ሳይሆን በሌላም አካባቢ የሚነግዱ ትልልቅና መካከለኛ ነጋዴዎችም ላይ ነው፡፡
በያዝነው ክረምት ወጣቶች ብዙ የበጎ አድራጎት ሥራዎች ተሠርተዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ የመንግሥት አካላት ወጣቶችን አስተባብረው ዝቅተኛ ኑሮ የሚኖሩ ሰዎች የወዳደቁ መኖሪያ ቤት በክረምቱ ወራት እያፈረሱ እንዲታደሱ ጥረት አድርገዋል፡፡ የመንግሥት አካላቱ የሠሩት ሥራ ፋና ወጊ እና ለሌላ ጊዜ እንደምሳሌ የሚጠቀስ የበጎ አድራጎት ሥራ ነው፡፡ ነጋዴዎቻችን በአዲስ አበባ ደረጃ እንኳ እንደዚህ የሠሩ ብዙም አላየንም፤ በክፋት ሆነ በስስት ሳይሠሩ ቀርተው አልያም የሚያስተባብራቸው ጠፍቶ ይሆናል፡፡
የአንድ አገር የምጣኔ ሀብቱ ዋልታና ማገሩ ግብር ነው፤ ከህውሓት አሸባሪዎቹ ጎን ሆነው ጎናችንን ሊወጉ የጣሩት አሜሪካ እና ጀሌዎቿ የደነፉብን ድህነታችንን ተገን አድርገው ነው፡፡ እኛ ለአገራችን መቆም መቻል አለብን፡፡ እኛ ለአገራችን ስንቆም አገራችንም ለእኛ ትቆምልናለች ብቻ ሳይሆን ፤ባላንጣዎቻችንም ያፍራሉ ይተክዛሉ፡፡ ለአገራችን ከምንቆምበት መንገድ አንዱ የግብር ሥርዓታችን ነው፡፡ እየሠሩ መገበር ያባቸው ዜጎች በግብር መረብ ውስጥ ለማካተት ጥረት መደረግ አለበት፡፡ ይሄንን መቼም ግብር ሰብሳቢው አካል በቅጡ እየሠራበት አይደለም፡፡ ለእኔ ችግሩን ለመቅረፍ ዜጎችን የግብር መረብ ውስጥ ለመክተት ግለሰቦች እና ድርጅቶች ፈቃድ ወስደው የማይገብሩ አካላትን እንዲያስሱና ግብር መረብ ውስጥ እንዲከቱና እግረ መንግዳቸውን የልፋታቸውን እንዲያገኙ ለማድረግ ቢሞከር የተሻለ ይመስለኛል፡፡
ባለፈው መጋቢት አጋማሽ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ለተወካዮች ምክር ቤት መግለጫ ‹‹የኢትዮጵያ ገቢ ማስገባት ከሚገባው አንፃር ሲታይ ዝቅተኛ ነው። ግን በሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ በተቀመጠ ዕቅድ መሠረት ለውጡን በመረጃ አስደግፈን ስንመለከት ምን ያህል የተሳካ ሥራ መሥራት እንደቻልን ያሳያል ›› ብለው ነበር፡፡
በርግጥ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ አነጋገር መረዳት እንደሚቻለው ሀገሪቱ በየዓመቱ የምታገኘው ገቢ እየጨመረ ነው፡፡ ነገር ግን የገበያውን አሻጥር የምንከላከልበት አንዱ መንገድ መገበር እየቻሉ የማይገብሩትን እንዲገብሩ ማስገደድ ነው፡፡ ከዚሁ ጎን ለጎን የገበያ ሥነሥርዓቱን እና ሰንሰለቱን ማሳጠር ነው፡፡ አገራችን የህልውና ዘመቻ ያለችበትን ወቅት እንደመልካም አጋጣሚ በመጠቀም ዋጋ እያናሩ ነዋሪውን የሚያማርሩ ላይ ከጋዜጣዊ መግለጫ የዘለለ እርምጃ ይወሰድ፡፡ የመንግሥት ንግድ ቤቶች ከሆኑ በውድድር ለሌሎች ነጋዴዎች ንግድ ቤቱን ማስረከብ፤ ነጋዴዎቹ ለራሳቸው ሲሉ ዋጋ ከማናር ተቆጥበው ማገልገልንና ማትረፍን ሰንቀው እንዲሄዱ ያስገድዳል፡፡
ግብር ሰብሳቢው አካልን ጨምሮ የንግድ ሚኒስቴር ሸማቹና በነጋዴዎች መካከል ያለውን መቃቃር እና መናቆር ማስቀረት አልቻሉም፡፡ መቃቃርና መናቆር ስል በተዘዋዋሪ በሀሜትም በሉት በስሜትም ዋጋው እንደዚህ ሆነ እየተባለ ሸማቹ ህዝብ ብሶቱንና ቅሬታውን ሲናገር ይሰማል፡፡ ቅሬታውን የሚቀበለው የለም እንጂ ቅሬታውን በቀጥታ ለሚመለከተው አካል ያቀርባል፡፡
ግብር ሰብሳቢና ህገወጥ ንግድን ተቆጣጣሪ የግል አካላት እንዲስፋፉ ቢደረግ፤ ህገወጥ የንግድ አሻጥርን ለመከላከልም ይረዳል፡፡ (በነገራችን ላይ ሕገውጥ የንግድ አሻጥር የሚል ያለ አይመስለኝም) ፤‹‹የንግድ አሻጥር›› ሲባል በራሱ ቃሉ ሕገ ወጥ መሆኑንም እናስበው፡፡ ያለንበት ወቅት አሸባሪዎቹ አጋጣሚውን ተጠቅመው ህዝቡን የእህልና የቁሳቁስ ዋጋ በማናር ለግጭት ሊቀሰቅሱት ይፈልጋሉ፡፡ ‹‹በአንድ ወንጭፍ ሁለት ወፍ›› እንደሚባለው ፤በግብሩ ምጣኔ ሀብትን ማሳደግ ይቻላል፤ብዙ የመሠረተ ልማት ሥራዎች ይሠራሉ ፤ ለብዙ ሰዎች የሥራ ዕድል ይፈጠራል፤ ሕገወጥ የንግድ አሻጥርንም ለመቆጣጠር የሚችልበት መንገድ ቀላል ይሆናል፡፡ ህዝብና መንግሥት የአገር ሰላምና ፀጥታ እያስከበሩ ባለበት ሰዓት ነጋዴዎች ዋጋ በማናር ምርት በመደበቅ አሻጥር የሚፈጽሙ ከሆነ አገር እየወጉ ካሉ ባንዳዎች ጎን ናቸው ማለት ነው፡፡
ይቤ ከደጃች.ውቤ
አዲስ ዘመን ነሐሴ 30 ቀን 2013 ዓ.ም