ዳግም ከበደ
የሀገራችን ሰሞነኛ ወሬ ምርጫ ነው። ምርጫ ደግሞ ትንሽ ኮስተር ያለ ነገር የሚበዛበትና ብዙሃኑን የሚያሳትፍ እንቅስቃሴ እንደመሆኑ መጠን ትኩረት ይስባል። ለዚህ ነው ይህ ሰሞን ከምን ጊዜውም በላይ የትንሽ ትልቁን ቀልብ ይዞ እያነጋገረ የሚገኘው።
ምእራባውያን ከቀሪው ዓለም በተለየ መንገድ ዲሞክራሲ የሰፈነባቸው አገራት እንደሆኑ ስለሚታመን በምርጫ ወቅት ብዙም ስጋቶች ይስተዋላሉ ተብሎ አይታሰብም። ይሁን እንጂ ብዙ አነጋጋሪ ጉዳዮች ግን አይጠፉትም። ፓርቲዎች እርሰ በእርስ እሰጣ ገባ ውስጥ ከመግባታቸውም ባሻገር ደጋፊዎቻቸው ጎራ ለይተው ዱላ ቀረሽ ጭቅጭቅ የሚያደርጉበት ጊዜም አይጠፋም።
በምርጫ ወቅት ከኮስታራው እንቅስቃሴና ስሜት ባሻገር ደጋፊዎችና የምረጡኝ ቅስቀሳ የሚያደርጉ ፖለቲከኞች ፈገግ የሚያደርጉ ድርጊቶችና እንቅስቃሴዎችን ሲያከናውኑ ይስተዋላሉ። በተለይ ይህን ጊዜ ይበልጥ አዝናኝ እንዲሆን የሚያደርጉት ተመራጮች የሚጠቀሙበት የምርጫ ምልክት አሊያም መፈክሮች ናቸው።
በዚህ ርእሰ ጉዳዬ ላይ ይህን ስሱ የሆነ ጉዳይ አንስቼ ለሌላ ተጨማሪ አተካራ ርእስ ማድረግ አልፈልግም፤ላዩን ግን በማህበራዊ ድረገፅ የሚንሸራሸሩ አንዳንድ የምርጫ ነቆራዎችን አነሳሳለሁ። ከነቆራዎቹ ይልቅ ተገቢ ያልሆኑ የምርጫ ሰሞን የመልስ ምቶችና እንቅስቃሴዎች ላይ ለማተኮር ወድጃለሁ።
በቅስቀሳ ወቅት የምረጡኝ ዘመቻ የሚያደርገው አካል ወይም ግለሰብ የደጋፊዎቼን ትኩረት ይስብልኛል ብሎ ካሰበ ከህግ አግባብ ውጪ ያልሆኑ ማንኛቸውንም ጉዳዮች የማድረግ መብት አለው። ካሻው እንደ ፌንጣ እየዘለለ፣ ካልሆነ በጭንቅላቱ ቆሞ አሊያም ደግሞ ሌሎች ግራ የሚያጋቡ ድርጊቶችን በማከናወን ደጋፊዎቹን ማማለል ይችላል። ታዲያ ይህን በሚያደርግበት ወቅት ለዚህ የምርጫ ቅስቀሳው የሚሰጡ ምላሾችና መነቆሮች/አንዳንዶች ነቆራዎች ይሉታል/ወደ ግጭትና ውዝግብ ይዞን ሊሄድ ይችላልና ጠንቀቅ ማለቱ ይሻላል።
በተለያየ ምክንያት ተራዝሞ የቆየው የአገራችን ምርጫና የምርጫ ቅስቀሳ ሰሞኑን በይፋ መጀመሩ ይታወቃል። ይህንን ተከትሎ በማህበራዊ ድረ ገፅና በተለያዩ የመገናኛ አማራጮች መልካምና መልካም ያልሆኑ ጉዳዮችን እየተመለከትን እንገኛለን። ፓርቲዎች እጩዎቻቸውን ይፋ ከማድረግ አልፈው የምረጡኝ ቅስቀሳ ማስጀመሪያ ስነስርአቶችን ሲያከናውኑ አስተውለናል።
ታዲያ ይሄ ጅምር እንጂ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ የተካሄደ አይደለም። የምረጡኝ ዘመቻ ግለት ከዚህ በኋላ እየጨመረ ይሄዳል። በዚህ ወቅት ታዲያ ገና ከጅምሩ ያየናቸው ተገቢ ያልሆኑ ከስነ ምግባር ያፈነገጡ ድርጊቶች በጊዜ መቀጨት ካልቻሉ መዘዞችን ጎትተው ማምጣታቸው አይቀርም።
ስልጣኔ ላይ የደረሱና የዲሞክራሲ ፅንሰ ሃሳብ የገባቸው አገራት የምርጫ ቅስቀሳቸውን በጥንቃቄ ያደርጋሉ። በክርክርና በቅስቀሳ ወቅት ተፎካካሪዎቻቸውን በሰላ ትችት ይሸነቁጣሉ። ለህዝቡ የሚያቀርቡትን የፖሊሲ አማራጭ በተለያዩ ዘዴዎች በማቅረብ ተፎካካሪያቸውን ያሳጣሉ።
ይሄ አካሄድ ጤናማ ነው። ጀርባ እጅ ለእጅ ተጨባብጠው ተሳስቀውና ማህበራዊ ጨዋታዎችን ተለዋውጠው ተፎካካሪያቸውን ዴሞክራሲያዊ በመሆን መልኩ የሚበልጡበትን መንገድ ለማዘጋጀት ይተጋሉ። ይሄ በሃሳብ ልዩነት ማመን የሰውነትን ልክን መረዳት ነው።
አያ ጅቦ መጣልህ
ለዓመታት በኢትዮጵያ ውስጥ የሚካሄዱ ምርጫዎች ይዘት በልጅነታችን ስናስቸግር ቤተሰቦቻችን የሚጠቀሙበት “ አያ ጅቦ መጣልህ” የሚለው ማስፈራሪያ አይነት ነው። እንደውም አንዳንዴ በዚህ ማስፈራሪያ ያደገ ልጅ ምርጫ ላይ ሲሳተፍ ህዝቡንና ተፎካካሪዎቹን በመሰል መንገድ የሚያስደነግጥ እየመሰለኝ ፈገግ እላለሁ።
ስልጣን ላይ ያሉትም ሆነ በተለያየ መንገድ ተደራጅተው የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች ደጋፊዎቻቸውንም ወይም ቆሜለታለሁ የሚሉትን ህዝብ “አያ ጅቦ መጣልህ” ከማለት የማይተናነስ የፍረጃ ቅስቀሳ ሲያጧጡፉለት ይታያሉ። ለህዝቡ ዳቦ የሚያገኝበትን መንገድ፣ ለብሶ የሚያድርበትን ሁኔታ፣ የስልጣኔ ደጃፍ የሚደርስበትን ቁርጥ ቀን በፖሊሲ አማራጮቻቸው ከማሳየት ይልቅ ባላጋራዎቻቸውን እንደ ጋኔል አስመስለው በማቅረብ ኮሮጃቸውን ለመሙላት ከላይ ታች ሲራወጡ ማየት ነው የለመድነው።
ይሄ አካሄድ ጥላቻን ይዞልን መጣ እንጂ እንደምናስበው በህይወታችን ላይ ምንም የተሻለ ለውጥ አላሳየንም። ይሄ አካሄድ ከድህነት ማቅ ከእርስ በርስ ነቆራ አንድ ኢንች ሊያራምደን አልቻለም።
“ወግ ወጉን” እንተወው
ዲሞክራሲን ለመገንባት፣ በማስተዋል ላይ የሚራመድ ትውልድ ለመፍጠር የይድረስ ይድረስና የይስሙላ ተግባሮችን ማቆምና ከልብ በመነጨ ፍላጎት ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን ወደፊት ማራመድ ያስፈልጋል። ይህን ለማድረግ አገራቸውን የሚወዱ እውቀቱና ፍላጎቱ ያላቸው ግለሰቦችና ቡድኖች የበኩላቸውን ለማድረግ ደፋ ቀና እንደሚሉ አውቃለሁ። ታዲያ እነዚህን ማበረታት ተጨማሪ ሃይል መፍጠር ለነገ የሚባል ነገር የለውም።
በምርጫ ወቅት ገዢው ፓርቲም ሆነ ተፎካካሪ ፓርቲዎች የፖሊሲ አማራጮቻቸውን ህዝብን በማያወናብድ መንገድ ግልፅ አድርገው ማቅረብ አለባቸው። ከዚህ ባሻገር በደጋፊዎቻቸው አማካኝነት ጎራ ለይተው መናቆር እና ለይምሰል ወንበር ለመያዝ ከሚደረግ የለብ ለብ የቅስቀሳ ፖለቲካ መውጣት እንደሚኖርባቸው ይሰማኛል። በተለይ በማህበራዊ ገፅ ላይ አንደኛው ተፎካካሪ ከሌላኛው ተሽሎ የሚገኝበትን መንገድ ግልፅ ባለ መንገድ ማሳየትና ድጋፍ ማሰባሰብ እንጂ የባላጋራን ስም፣ ስራ፣ ሃሳብና አማራጭ በማጣጣል የሚገኝ ዳረጎትን መለቃቀም ወግ ወጉን ብቻ ከመያዝ የተለየ መንገድ የለውም።
አሁን በዚያን ሰሞን በተደረጉ የድጋፍ ሰልፎችና የምረጡኝ ቅስቀሳ ማስጀመሪያ ዘመቻዎች ላይ ያስተዋልናቸው ሰሞነኛ መነቋቆሮች መጪውን ጊዜ ስለሚያመላክቱን “ሳይቃጠል በቅጠል” እንደሚባለው የአገሬ ብሂል ሳይመሽ ነገሮችን ለማስተካከል መሞከር አይከፋም።
ለመማማር እንዲጠቅምና ዳግም እንዳይደገም የሚከተሉት ነገሮች በጥንቃቄ ቢታዩና ቢስተካከሉ በማለት ሃሳቤን ልቋጭ። ፓርቲዎች እጩዎቻቸውን ይፋ በማድረጋቸውና አንዳንድ እንቅስቃሴዎች በመደረጋቸው በድርጅታቸው አባላት ላይ ጥቃት ስለመፈፀሙ መረጃዎች ያመለክታሉ። ይሄ በገለልተኛ አካል መጣራት ይኖርበታል። ትክክል ከሆነም እብደት ስለሆነ በጭራሽ መደገም የለበትም።
በድጋፍ ሰልፎች ላይ በህጋዊ መንገድ የሚንቀሳቀሱ ድርጅቶችን በሽብረተኛነት የመፈረጅ ሁኔታም ታይቷል፤ ድርጊቱ በምርጫ ቦርድም ተወግዟል። ይህን ከመሰለ ያልሰለጠነ አካሄድ ፓርቲዎችም ሆኑ ደጋፊዎቻቸው ራሳቸውን ሊያርቁ ይገባል። ማንኛውም ህጋዊ ሰውነት ይዞ ከምርጫ ቦርድ እውቅና አግኝቶ የሚጠቀምባቸውን ፖስተሮች፣ ምልክትና አርማ ማንቋሸሽም ሆነ በደጋፊዎች በቅስቀሳ ወቅት ተይዘው ሲታዩ ጥቃት ለማድረስ መሞከር ወንጀል ነው፤ በመሆኑም ህብረተሰቡም ፓርቲዎችም ይህን በሚገነባ ሊገነዘቡት ይገባል።
በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ደጋፊዎችና የፓርቲ አባላት የማይገባ መልእክት እንዳያስተላለፉ ቅስቀሳውን በአግባቡ መምራት ያስፈልጋል፡፡ ሌሎች ፓርቲዎችን የሚጎዳ መልእክት ተላልፎ ከሆነም በፍጥነት ማረም ያስፈልጋል፡፡ ይህን ሳያደርጉ መልእክቱ የግለሰቦች እንጂ የፓርቲው አቋም ነው ማለቱ ብቻውን በቂ አይሆንም፡፡ ድርጊቱ እንዳይደገም መስራትም ይገባል፡፡
ምርጫ የሚካሄደው ግለሰቦችን ወንበር ላይ አስቀምጦ እየቀለቡ አምባገነን ለማድረግ ሳይሆን ዜጎች በሰላም፣ በእድገት ጎዳና በዴሞክራሲያዊ አግባብ ሰብአዊነታቸው ተከብሮ መኖር እንዲችሉ ለማድረግ ነው። በመሆኑም ምርጫውን ቅርጫ አታርጉት። ለስልጣን ሳይሆን ትክክለኛ የዲሞክራሲ ስርአት ለመገንባት በሚደረገው ጥረት መሰረት ለመጣል ተዘጋጁ። ቸር ያሰማን!
አዲስ ዘመን የካቲት 21/2013