አብርሃም ተወልደ
አንዳንድ ሰዎች ምንም ያህል ያማረ መልክና ቁመና በጣም ተወዳጅ የሆነ የተፈጥሯዊ ባህሪ ያላቸው ቢሆኑም ስለራሳቸው ጥሩ የሆነ አመለካከት ወይም እተያየት የላቸውም። ሰው ሁሉ የማይወዳቸው በህብረተሰቡ ዘንድ ተቀባይነት ያጡ በስራቸው ብቃት የሌላቸው መስሎ ይሰማቸዋል። ይሁን እንጂ ስሜታቸው በእውነት ላይ የተመሰረተ አይደለም።
ባሉበት ህረተሰብ ውስጥ ተቀባይነት ያላቸው ራሳቸውን እና ኑሯቸውን አሸንፈው የሚኖሩ የስንፍናን ባህሪ የማይታይባቸው ትጉህ ሰራተኞች ቢሆኑም ሁልጊዜ ራሳቸውን ዝቅ አድርገው ይመለከታሉ። በተለይ ከእነርሱ የበለጠ የተሳካላቸው ሰዎች ሲያዩ ደስታቸው በቀላሉ ይጠፋል።
በኑሯቸው ከእነርሱ የተሻሉ ሰዎችን መመልከት ከእነርሱ ትምህርት ለመቅሰም እስከ ሆነ ድረስ “እንዴት ከዚህ ደረሱ” ብሎ መጠየቅ ያን ያህል ክፉ አይደለም። ራሳቸውን ከሌሎች ሰዎች ጋር አወዳድረው የራሳቸውን ዝቅተኝነት ለማየት ከሆነ ግን ይጎዳቸዋል እንጂ አይጠቅማቸውም አንዳንዶች ራሳቸውን ዝቅ አድርገው በመመልከት “የማልረባ ነኝ” ብለው ስለደመደሙ ሲሳካላቸው እንኳን ባገኙት ስኬት በመደሰት ፋንታ “የተሳካልኝ እንደ እድል ወይም እንደ አጋጣሚ ሆኖ ነው እንጂ ጥሩ ሰርቼ አይደለም” ይላሉ፤ ችግራቸው እዚህ ላይ አያቆምም። ራሳቸውን ዝቅ አድርገው ስለሚመለከቱ የሆኑትን ፈንታ ሌሎች ከደረሱበት ለመድረስ የሌላውን ሰው ኮፒ ወይም ግልባጭ ለመሆን ይሞክራሉ።
ይህን ሁሉ ያነሳሁት በትናትናው እለት የገጠመኝን ሁኔታ ለማንሳት ይረዳን ከሆነ ብዬ ነው። ቢሮ ስራ ሰርቼ የተሰላቸውን እና ድካም ያዛለውን አካሌን በተለይ ደግሞ ቢሮ ጭብጥ ብሎ የዋለ ሰውነቴን ለማፍታታት የተወሰነ መንገድ በእግሬ ልጓዝ እና ትንሽ ከተነቃቃሁ ድካሙ ድሞ እንዳያይል በአገኘሁት ትራስፖርት እሄዳለው ብዬ ተነሳሁ፤ ታዲያ ብዙም ሳልጓዝ ነው አሁን ልነግራችሁ ያሰብኩትን ሁነት ያየሁት።
ፒያሳ እንደወትሮዋ የስራ ሰዓት መውጫ በመሆኑ ወደ ቤቱ ለመሄድ በሚጣደፍ፣ የእለት ጉርሱን ለመሙላት ከደንብ አስከባሪዎች ጋር ድብብቆሽ እየተጫወተ ከሚነግደው ፣ በየኔ ቢጤ፣ ኪስ አውላቂው በትንራንስፖርት ተሳፋሪ ሰልፍ … ብቻ ምን አለፋችሁ ገና ከርቀት ሲታዩት አንዳች ነገር እየተርመሰመሰ ነው የሚመስለው።
እኔም አይደርሱ የለም ከቦታው ማለትም መሐል ፒያሳ አያሌው ሙዚቃ ቤት አካባቢ ደረስኩ፤ ከአልፎ ሂያጂ መካከል የቀድሞ ጓደኛዬን ቢኒን ያገኘሁት፤ ቢኒ ራሱን ለመቀበል በጣም የሚቸግረው ልጅ ነው፤ ሁልጊዜ ምኞቱ ቁመት የሚጨምር መድሃኒት እንዴት እንደሚያገኝ፤ ያኔም ጸጉሩ ሳሳ ያለ ስለነበር ጸጉሩን ጠንከር እና ብዙ የሚያደርግለትን ቅባት እንደሚፈልግ አውቃለው።
ታዲያ አሁን ሳገኘው ቢኒ ከቀድሞ ትንሽ ወፈር ብሎ የነበረችውም ጠጉር በመኖር እና መጥፋት መካከል ሆኗ አገኘሁት፤ ከተገናኘን ብዙ ጊዜ ስለሆነ ተበቅ እና ጠንከር ያለ ሰላምታ ከተሰጣጣን በኋላ ምን እግር ጥሎት ፒያሳ ብቅ እንዳለ ጠየቁት፤ ያው ቀድሞ በነገርኳችሁ ጉዳይ ቢኒያም ያው በኒ ነው፤ ጸጉር የሚያሳድግ ከሬት የሚሰራ ቅባት አለ ተብዬ እርሱን ልገዛ መጥቼ ነው አለኝ፤ ዘንድሮም ያው ነህ አልኩት እርሱም ለሚያደርጋቸው ነገሮች ይደግፍልኛል ያለውን አመክኒዮ አቀረበ፤ ኋላ ግን ቅም ብሎ እንዲያስብ የሚያደርገው ንግግር ተናገርኩት ተገልጦልኝ ይሁን ጥበብ ጨምሬ እንጃ! ያን ቅባት የሚሸጠው ወጣት ልጅ ራሰ በራ ጠጉር የሚባል የሌለው ልጅ ነው፤ እናም ወዳጄ ቢኒያምን ይህ ቅባት የሚሰራ ቢሆን ለምን የራሱን ጠጉር አልታደገውም ብዬ ጥያቄ አቀረብኩለት፤ ልጁንም እንዲሁ ቀርበን አወራነው የሞተ ጠጉርን እንኳ የሚመልስ ነው፤ አለን እኔም ታዲያ ምነው የአንተን አልመለስከው አልኩት እኛን ጨምሮ ሌሎች ቅባቱን ሊሸምቱም ሊጠይቁ የነበሩ ሰዎች እኩል በሳቅ አደበላለቁት፤ ልጁም ማለቴ ነጋዴው የሞት ሞቱን የምንገዛ ከሆነ እንድንገዛ ካልሆነ እንድንሄድ አዘዘን። በአገራችን አንድ የታወቀ አባባል አለ ይህም “የቸገረው እርጉዝ ያገባል” የሚል ነው። ስለዚህም ያለውን የተፈጠሮ ነገር ተቀብሎ እንዲኖር በመነጋገር ከቢኒ ጋር ተለያየን።
አንዳንዴ የጉድ ቀን ይረዝም የለ! ፒያሳ ወደ ሰፈሬ የሚሄደውን ሰርቪስ ለመያዝ ሰልፍ ተሰልፌ እኔ ከተሰለፍኩበት ፊት ሁለት እድሜያቸው ወደ 32 እና 35 የሚገመት እንስቶች ያወራሉ ከንግግራቸው እንደተረዳሁት አንደኛዋ ባላት የእረፍት ጊዜ ዱባይ በመሄድ የመዋቢያ እቃዎችን ታመጣለች ታዲያ ስለ አንድ ምርት ለጓደኛዋ እያስረዳቻት ነው፤ ልትሸጥላት እንደሆነ ገምቻለሁ፤ ታዲያ የምታሳያት ሎሽን የፊት ሲሆን ቡጉርን እንደሚያጠፋ የሞተ ቆዳን ከፊት ላይ እንደሚያነሳ እያስረዳቻት ነው ታዲያ ይህን ምስክርነት ስሰማ የምታወራውን ነጋዴ ፊት ለማየት ጓጓው። ፊቷ አዲስ በወጡ እና ጥቋቁር ነጠብጣብ ጥለው በከሰሙ በጉሮች የተወረረ ነው። ይልቅ ልትገዛው የምትከራከረው ሴት የተሻለ ነው።
ነገር ግን እንዴት የአንቺ ፊት ሊጠራ አልቻለም ብላ መጠየቅ ለምን እንዳልፈለገች ወይም እንዳላስተዋለች ከእራሴ ጋር ሙግት ገጠምኩ ወዲያው ቢኒ ትዝ አለኝ፤ የቸገረው … ስለዚህም ራሱን ካወቀ ምንነቱን ሳይለቅ የሆነውን ሆኖ ለመኖር ቆራጥ የሆነ ውሳኔ መወሰን ይቻላል። የሰው መሰረታዊ የሆነ የህይወቱ ዋና ዓላማ “ራሱን ማወቅ” ነው።”
ራስን ማወቅ” ስል የሚወደውንና የሚጠላውን ነገር ለይቶ ከማወቅ በላይ ነው።”ራስን ማወቅ” ስር የሰደደ በሂደት ውስጥ የሚገኝ አቋም ነው። ራስን ወደ ማወቅ የሚያደርሰው መንገድ ረጅም ፣ጠመዝማዛ እና አስቸጋሪ ነው። ይሁን እንጂ ማንኛውም ሰው የግድ በዚህ መንገድ ማለፍ የለበትም።
ራስን ለማወቅ በሚያደርገው ጥረት ውስጥ አልፎ አልፎ በመጠራጠር ልምምድ ውስጥ ሊያልፍ ይችላል። ስለዚህ ራስን ከማወቅም ደረጃ ለመድረስ ውስጣዊ የሆነ “በራስ የመተማመን” ጉልበት ወይም አቅምን ይጠይቃል። ራስን ማወቅ ድካማችንና አቅማችንን ጥልቅ የሆነውን የፍቅር ስሜታችንን እና ፍርሃታችንን መረዳት ያጠቃልላል።
የምንወደውንና የምንጠላውን ትእግስታችንን እና የአቅማችን ገደብ ማወቅን ያጠቃልላል። ስለለዚህም ራስህን በማወቅ በጭንቀት እና በችኮላ ከሚወሰኑ ነገሮች በመውጣት ያለንን በመቀበል በደስታ እንኑር፤ ከቅኝቴ ያገኘሁት ይህ ነው፤ አበቃው ሰላም።
እዚህ ጉዳይ ላይ እንዲህ አይነት ነገር ገጥሞኛልና እንዝመትበት።ሀሽታግ በሚሉት ማስፈንጠሪያ አጅበን ድህረ ገፁን እንሙላው ይላል።የሚገርመው ተከታዩ ብዛቱ፤ የሚያግዘው የሚደግፈው መበርከቱ።
ለቻሌንጅ ተብሎ የተመረጠው ጉዳይ አልያም ሊዘመትበት የታቀደው ርዕሰ ጉዳዩ ለዘመቻ ቀርቶ ለመነሳት እንኳን የማይበቃ የግለ ጉዳይ ሊሆን ይችላል።ብቻ ምንትስ ቻሌንጅ ተብሎ አንዱ ካንዱ ይቀባበላል።
የተዛነፈ ማህበራዊ ጉዳይ ትኩረት ተሰጥቶት ሊቀረፍ የሚገባው የህዝብ ችግር ላይ እሺ ችግር የለም ይዘመት ይጮህ ይሰማ ይራገብ ችግሩ እስኪቀረፍ ይወራ።ነገር ግን ተራ የግለሰብ ብሶትና ማላዘን እንዴት “ቻሌንጅ”ተብሎ ይዘመታል ወገን።ኧረ ተው የምናከብድና የምናቀለውን ጉዳይ እንለይ።የጉዳይ መክበድና መቅለል፤ የርዕሰ ጉዳይ ግዝፈትና ተራ መሆን እናብጠርጥር፡፡
ባነሱ ጉዳዮች ተባድነን ጮኸን በገዘፈ ጉዳይ አመል ነው ተብልን አድማጭ እዳናጣ ቢያንስ ዘምተን የምንጮክበት ጉዳይ ምንነት እንረዳ። በየማህበራዊ ትስስር ገፁ የሚታዩ “ቻሌንጅ” እየተባለ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የሚያተክኑን ዘመቻዎች ሀይ ማለት አይገባም ጎበዝ።ነገ የምር ጉዳዮች ገጥመውን ብንጮህ ሰሚ እንዳናጣ እንዳያደርጉን የዛሬ ተራ “ቻሌንጅ”ተብዩ ዝውውርና ዘመቻዎች ሳይ ስጋት ገባኝ፡፡
በጥቃቅን የግል ጎዳዮች ፤ባልረቡ እንቶ ፈንቶዋች ገፃችን መጫናነቁ ሳያንስ በግል ጥቅምና እውቅና ናፍቆት መነሻነት እንዲህ ሁኛለሁና እዚህ ላይ ጩሁልኝ ባዩ በርክቶብናል።የ ዘመቻው ወይም የ”ቻሌንጁ” ቀስቃሽ በተራው ጉዳይ መነሻነት አደባባይ ወጥቶ እንዲህ ሆኛለሁ እንዲህ ተደርጌያለሁና ጮኸቴን አሰሙልኝ ይላል።
የጩኸቱን ልክ ያልገባው የጮኸበት ምክንያት ምንነት ያልተረዳው አጋዥና ተከታይ ግን የምር የራሱ የሚለው ጉዳይ የሚያሳስበው ምንም ነገር ሳይኖር ቀርቶ ነው ስለሌላው ዘራፍ የሚለው ጎበዝ፤ አይ የኛ ነገር የት ይሆን መድረሻችን፡፡
ምክንያት አልባ በርክቶ የሌለ ተቀብሎ እንዴት ብሎ ሳይጠይቅ እሺ ብሎ ተቀብሎ ምንጥሴ ቻልንጅ ብሎ እሱም ይከተላል።የእርሱ ወዳጅም ተቀብሎ ለሌላ ወዳጄ ላለው እንዲህ ሆኗልና ትኩረት ይሰጥበት የሚል መልዕክት አክሎ ሀሽታግ በሚሉት ማስፈንጠሪያ ታግዞ ገፁን ይሞላዋል።
ጠዋት 3 ሰዓት ላይ የተጀመረ አንድ ዘመቻ ከምሳ በፊት በሌላ ይተካል።ምሳ ሰዓት ላይ የተለጠፈው መክሰስ ሳይደርስ በሌላ ይለወጣል።ወይ ጉድ እነደው ምን ተሻለን።ቆዩኝማ ቢያንስ ቻሌንጃቸው ተደራሽ እንዲሆን እንደው የቀናት እድሜ ኖሮት እንዲዳረስ ቢታገሱ ምን አለ።
የንጠይቀውን ለይተን የሚያስጠይቀንን አውቀን ትክክለኛ በሆነ መንገድ ሀሳብ መግለፅ መልዕክትን ማስተጋባት ያለ ነው።ነገር ግን አገር ላይ የተትረፈረፈ ችግር እያለ፤ ወገን ላይ የሞላ መሰናክል እየታየ የግል ጉዳይን አጉልቶ የቡድን ጥያቄን ይዞ ህዝብ ጋር መቅረብ ያስተዛዝባል።እና እባካቹ “ቻሌንጅ” እያላችሁ ገፃችንን በመሙላት ቻሌንጅ የሆናችሁብን ባለጉዳዮች ስከኑ አልን፡፡
አበቃሁ ቸር ይግጠመን።
አዲስ ዘመን የካቲት 06/2013