ይቤ ከደጃች ውቤ
ከአንድ ወር በፊት ጎጃም በረንዳ አካባቢ ማለዳ ላይ ያገኘኋት ልጅ እግር ወጣት ልጅዋን ታቅፋ በስካር መንፈስ ውስጥ ነበረች፤ በእጅጉ አሳዘነችኝ ፤ላነጋግራት ብፈልግም አልቻልኩም።በማግስቱም በዚያው አካባቢ ሳልፍ አሁን እዚያው ቦታ ላይ አገኘኋት፤ ላወራት ይገባል ስል ወሰንኩ።ላነጋግራት ስጠጋት አስቀድማ “የጨብሲ ጀባ” በለኝ፤ ጫት የምቅምበት ስጠኝ አለችኝ።
በዚህም የማነጋግርበት አጋጣሚ አገኘሁ።ወጣቷ ከገጠር መጥታ ቤት ተከራይታ ከጓደኞቿ ጋር ትኖር ነበር።ቀን ቀን ምግብ ቤት በአስተናጋጅነት ሰርታለች።በዚህ ስራዋ ምግብ ቤቱ ከሚሰጣት ደመወዝ ይልቅ ተገልጋዮች ጥለውላት የሚሄዱት ጉርሻ (ቲፕ) ያረካት እንደነበር ታስታውሳለች።
አንድ ደንበኛ ግን በተደጋጋሚ ዳጎስ ያለ ገንዘብ ይሰጣት እንደነበር አስታውሳ፤ በዚህም ሳያበቃ እንደሚወዳት ገልጾላት እንደነበር ገለጸችልኝ።ይህ ሰው በዚህ ብቻ ሳይወሰን ሊያገባት መወሰኑን ያረጋግጥላታል።ይህ ሁሉ ቀልቧን ሸረሸረው፤ “በተደጋጋሚ መገናኘት ጀመሩ፡፡
ይህ ግንኙነት ሌላ ትስስር ፈጠረ ጸነሰች፤ ሰው ቤት ተከራይተን እንኖራለን የሚል ሀሳብ አመጣ፤ ይህ ሁሉ አልዘለቀም አለች ወጣቷ።ምክንያት ደግሞ ማርገዟ ሆነ፤ ማርገዟን ሲመለከት ተሰወረ፤ አድራሻውን አጠፋ፤ የተሻለ ህይወት ትቼ፣ ወላጆቼን ጥዬ እዚህ መጥቼ መከራ ገረፈኝ ስትል በተሰበረ ልብ አጫወተችኝ፡፡
የምጠጣውም ሆነ የማጤሰው ይህን የብስጭት ስሜቴን ለመርሳት ነው የምትለው ወጣቷ፣ ጎዳና ተዳዳሪ ሆና መኖሯን ታስታውሳለች።ጎዳና ተዳዳሪ በሆነችበት ወቅት ኑሮ አስከፊ ሆኖባታል፣ አሁን እየለመነችም ቢሆን በየቀኑ ትንሽ ከፍላ የምታድርበት ቦታ አግኝታለች።ይህንንም ከጎዳና ኑሮ መርጣዋለች።አከራዮቿ ጭምር ይራሩላታል፤ ገንዘብ ከሌላት በማግስቱ ታመጣለች ብለው ያሳድሯታል።
የምታድርበት ቦታ የኪራይ ቤት እንዳይመስላችሁ፤ የጎን ማሳረፊያ ነው።በመርካቶ ቋንቋ “ኬሻ በጠረባ” ይባላል።እመጫትም ባለጫትም የሆነችው ይህች ወጣት፣ “ገንዘብ ሳገኝ ልጄን ጉልበቴ ላይ አቅፌ ጡቴን እያጠባሁ እኔ ደግሞ ሲጃራዬን እመጣለሁ” ትላለች።ወደፊት ለልጇ ስትል ጫት መቃሙን፣ መጠጣቱንና ሲጃራ ማጨሹን ለመተው ሃሳቡ አላት፡፡
የዚህችን ወጣት አይነት ህይወት የሚመሩ በርካታ ወጣት ሴቶችን በአዲስ አበባ እና በተለያዩ ከተሞችም እናገኛለን።ከእነዚህ ወጣቶች መካከል አንዳንዶቹ በደባል ሱሶች ውስጥ ሰምጠዋል፤ በየመንገዱ ልጃቸውን ታቅፈው ሲጃራ የሚመጡም ጥቂት አይደሉም፤ መጠጥ የሚያዘወትሩት፣ ጫት የሚቅሙት በርካታ ናቸው፡፡
እንደጠቅሳናት ወጣት ያሉት ደግሞ ሁሉም አይነት ሱሶች ቤታቸውን ሰርተውባቸዋል።ሲቅሙ፣ ሲጠጡ፣ ሰው አየኝ አላየኝ ብለው አይደለም፤ እንዲያውም ይይኝ ብለው ነው ማለት ይቻላል።መሸማቀቅ የሚባል ነገር እነሱ ዘንድ የለም።‹‹ስካርና ምርቃና ያሞላቅቃል፤ ያሳስቃል›› ሲሉ እሰማለሁ።የለመዱ ሲያወሩ፤ ካሻችሁ የተጠመዱ በሉት።
የጎዳና ተዳዳሪ ሴቶች ህይወት ብቻ አይደለም እየተመሰቃቀለ ያለው።በርካታ እናቶች ቤት እና ትዳር እያላቸው ኑሮ ፈተና ሲሆንባቸው ይታያል።አብዛኞቹ የሐገራችን እናቶች የቤት እመቤቶች ናቸው፤ በዚህ የተነሳ የራሳቸው ገቢ የላቸውም፤ በባሎቻቸው ገቢ ነው ቤተሰቡ የሚተዳደረው።
አንዳንድ እናቶቸ ደግሞ ባለቤት ቢኖራቸውም፣ አስቤዛ ብሎ ነገር አይሰጧቸውም።ባለቤት ተብዬው ጠጥቶ እና አምሽቶ ቤቱ የሚገባ ነው፤ ቤቱን እንደ አልቤርጎ ነው የሚጠቀመው ማለት ይቀላል።ሃላፊነት ብሎ ነገር የለም፡፡
አንዳንዱ ደግሞ ከምሽቱ ስምንት ዘጠኝ ሰአት በኋላ ቤቱ ስለሚገባ ቤቱ ተኝቶ አይባልም ተገኝቶ ነው የሚሉ እናቶች አሉ።ባል ኃላፊነቱን እየሸሸ ሲያስቸግር ቤተሰብ ልጆቻቸውን የሚያሳድግላቸው እናቶችም ጥቂት አይደሉም።
ኃላፊነቱን የሚሸሹ አባቶች አንድም የሚታዩት ጫታቸውን በጉያቸው ታቅፈው ነው፣ እንደዚህ አይነት አባት ከሚባል ባለጫት ቢባል ጥሩ አርጎ ይገልጸዋል።ይህን ስል ግን ሃሳቡን መሆኑን ተረዱልኝ፤ “መንገዱ በየት አቅጣጫ ነው? “ብላችሁ እንዳትጠይቁኝ።
ጫትም ሆነ መጠጥ በልኩ እየወሰዱ ልጆቻቸውን በአግባቡ የሚያሳድጉ ቤታቸውን በአግባቡ የሚመሩ አባቶች መኖራቸው አይካድም።ከባሎቻቸው ተለያይተው የራሳቸውን ሥራ እየሠሩ ልጆቻቸውን የሚያሳድጉ እናቶችም አሉ፤ በዛም ሆነ በዚህ ግን ልጆቻቸውን በማሳደግ ከፍተኛውን ድርሻ የሚወጡት ሴቶቹ ናቸው።
ከባሎች መካከል ሠርቶ በላዎች መኖራቸው ባይካድም፣ ወሮበላዎችም አሉ።ያወራሁላችሁ ቅንጭብጫቢዎች ስጋዬ ስለሆኑ ሥጋት ተሰምቶኝ ነው ለኔ ሳይሆን ለነሱ፣ ለህዝብና ለመንግሥትም ጭምር፡፡
በአዲስ ከተማ ትምህርት ቤት አካባቢ፣ ሰባተኛ፣ አራዳ ዶሮ ማነቂያ አካባቢ ለወጣቶች በየስርቻው ልዩ ስፔሻል ፊልም ቤቶች አሉ። ፊልም ቤቶቹ የሚታወቁት ልቅ የወሲብ ፊልም የሚታይባቸው በመሆናቸው ነው። የሺሻና የጫት ቤቶችም ብዛት ወጣቱን ከሚያባክኑትና ከሚያመክኑት መካከል ዋና ዋናዎቹ ናቸው።
የጫት ንግድ ጦፏል።የጫት መሸጫ ሱቆች ማስታወቂያ በራሱ ዘመኑን ተቀላቅሏል።ኪራያቸው ውድ ሊባሉ በሚችሉ ቤቶች ውስጥ ንግዱ የሚካሄደው።የሺሻ ማጨሻ እቃዎች ተያዙ ተወገዱ እየተባለ በስፋት ቢነገርም፣ የሚያጨሱት ቁጥር ግን እየጨመረ ነው። በእንደዚህ ዓይነቶቹ ከንቱ ቦታዎች የሚውሉ ዜጎች በመዝናናት ስሜት ጾታዊ ጥቃት ለማስፋፋት ጫናቸው ከፍተኛ ነው።
በየመንደሩ የተሰገሰጉ ልቅ የወሲብ ፊልም እና ሺሻ ቤቶች ላይ በዘመነ ኮረና በተወሰዱ እርምጃዎች ትንሽ አረፍ ተብሎ ነበር።ነገሮች ወደ መደበኛው እንቅስቃሴ ሲመለሱ እነሱም እንደ ደግ ስራ ወደ ለመዱት ስራችን ወዳሉት የጥፋት ድርጊት ተመልሰዋል።
በጾታ ላይ በሚደርስ ጥቃት ሴቶች በእጅጉ ተጎጂ መሆናቸው ይታወቃል።በሴቶች ላይ የሚደርስ ጥቃትን ፀረ -ጾታዊ ጥቃት ዘመቻ የተወሰነ ጊዜ በማድረግ ብቻ መከላከል እና ማቆም አይቻልም፤ እንቅስቃሴው ተጠናክሮ እንዲቀጥል ግን መንገድ ይሆናል።በመዲናችን ጎዳናዎች የምናያቸው ወጣት እመጫቶችና ባለጫቶች የበዙትም አንድም በዚሁ ተፅዕኖ ይመስለኛል።
ብዙ ሥራ አጥ ወጣቶች ኑሯቸውን ለመለወጥ ብለው ወደ መዲናዋ እየኮበለሉ ጎዳና ተዳዳሪዎች ሆነዋል፤ መራራን ህይወት እየጎነጩ በጫት በሲጃራ ብሎም ቤንዚን በመሳብ የሀገር ሸክም ለመሆን እያኮበኮቡ ነው።ታዳጊዎቹ ለአቅመ አልጋ ሳይደርሱ የጾታ ጥቃት ፊታውራሪ ተጠቂና አጥቂ መሆናቸው ሳይታለም የተፈታ ነው።
ከየክልሉ የተሻለ ህይወት ብለው ወደ ሸገር የመጡ ወጣትና ታዳጊ የጎዳና ተዳዳሪዎች በሱስ ተጠምደው ሲቸገሩ ይታያል።መንግስት በተቻለው አቅም ዜጎችን እያስተባበረ የእነዚህን ህብረተሰብ ክፍሎች ህይወት ለመለወጥ ሲሰራ ቆይቷል፤ እየሰራም ነው።ከችግሩ ግዙፍነት አኳያ ብዙ መስራት ግን ያስፈልጋል።ክልሎችም ድርሻቸውን መወጣት አለባቸው።ክልሎችና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የተቀናጀ ስራ መስራትም ይጠበቅባቸዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የተለያዩ ድርጅቶችን በማስተባበር በመዲናዋ በየጎዳናው የሚወድቁትን ሰብስቦ በአንድ ግቢ ውስጥ በማድረግ መመገብ፣ ማሰራትና ማስተማር የሚቻልበት መንገድ ቢታሰብበት መልካም ነው። በዚህም ከሱስ መከላከል ብቻ ሳይሆን ከኮረናም ራሳቸውን እንዲጠብቁ ማድረግ ይቻላል፡፡
የከተማው አስተዳደር እና የኦሮሚያ ክልል ሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮዎችና ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ፣ ሌሎች መንግሥታዊ አካላት እና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ታዳጊዎቹን በስነምግባር ተቀርጸው ኃላፊነት የሚሰማቸው ዜጎች ሆነው ሊወጡ የሚችሉበትን መንገድ ማመቻቸትም ጊዜ ሊሠጡት የሚገባ ጉዳይ አይደለም፡፡
አዲስ ዘመን ታህሳስ 24/2013