አብርሃም ተወልደ
ብዙ ውጣ ውረዶች እና ችግሮችን አልፎ የተገነባው የባቡር ሀዲድ እና የመጀመሪያው ባቡር ከመነሻው ጅቡቲ ወደ ድሬዳዋ የገባው ባሳለፍነው ሳምንት ታህሳስ 14 ቀን 1895 ዓ.ም ነበር። ሳምንቱን በታሪክ ታዲያ ይህን ቀን መሰረት በማድረግ የባቡር ሀዲዱ እና አጠቃላይ ስራው እና ዳግማዊ አጤ ሚኒልክ ያሳላፉትን ውጣ ውረድ በአጭሩ ያስቃኛል።
አጤ ቴዎድሮስ መቅደላ ላይ ያሰሯቸውን አውሮፓውያን እስረኞችን ለማስለቀቅ የእንግሊዝ ጦር በመጣበት ጊዜ ጦሩ ከወደቦቻችን ወርዶ በኢትዮጵያውያን መሬት ሀዲድ ዘርግቶ መደፍና ከባድ ዕቃ በመንኩራኩር በቀላሉ ያመላልስ እንደነበር አጤ ሚኒልክ ሰምተዋል።
መቅደላ ተቀምጠው በነበረበት ጊዜ በዚያ ከነበሩ የውጭ አገር ሰዎች ጋር በመጫወት ብዙ ተምረዋል። በተለይ እስረኛው የዎልድሜር ተማሪ ስለነበሩ ስለባቡር ሀዲድ በዝርዝር ነግሯቸዋል።
ምኒልክ በሸዋ ንጉስ ከሆኑ በኋላ ያን ሀዲድ አዘርግተው ባቡር ለማስገባት አሰቡ። ይህም ሀሳባቸው እንዲፈቀድላቸው የበላያቸውን ንጉሰ ነገስት አጤ ዮሐንስን ፍቃድ ጠየቁ። በአጤ ዮሐንስ አካባቢ የነበሩ መኳንንቶች መክረው ሚኒልክ ከግዛታቸው ከሸዋ ውጭ ሀዲድ መዘርጋት እንደማይችሉ ተነገራቸው።
የአልፍሬድ ኢልግን ታሪክ የጻፈው ኬለር በመጽሐፉ ሲያትት “… የሸዋ ንጉስ ሚኒልክ ለባቡር ሀዲድ ስራ ብዙ ጓጉተው ነበር፤ በእሳቸው መቸኮልና መጓጓት ምክንያት አልፍሬድ ኢልጎ በስራ እና በሀሳብ ተጠምዶ ነበር።
የባቡር ስራ እንዴት እንደሚካሄድ ለማሳየት አንድ ሞዴል ሰራ። ሞዴሉ ጎታች ጋሪዎችን እየጎተተ በሀዲድ ላይ ሲሄድ የሚሳይ ነበር፡ ፡ሚኒልክ ሞዴሉን አይተው ተደሰቱ። ኢልግ ሰራተኛ እንዲፈልግም ሙሉ ስልጣን ሰጡት። ኢልግም ሙሉ ፍቃድ ከአገኘ በኋላ የባቡር ሀዲድ ከመወሰን ጀምሮ እንጠጦ ድረስ እንዳይሰራ አጤ ዩሐንስ ስለከለከሏቸው ነገሩ ቀረ…”ሲል አስነብቧል።
አጤ ምኒልክ የሀዲዱን መስመር በሸዋ ውስጥ ብቻ መዘርጋት ምንም ጥቅም እንደማይሰጥ ተገንዝበው ጊዜ እስኪያገኙ አሳባቸውን አዘገዩት። በኢትዮጵያ ላይ ሙሉ ስልጣን አግኝተው ንጉሰ ነገስት ከተባሉ በኋላ የሀዲዱን መዘርጋት ሀሳብ አንቀሳቀሱት።
ፈረንሳዊው ሙሴ ፖውል የባቡር ሀዲድ መዘርጋት አሳብ ላይ ስሜት አደረበት። ከአቦክ (ጂቡቲ ውስጥ) ተነስቶ አንኮበር ቢደርስ የሚያዋጣ መሆኑን አሰበ። የምኒልክ የቅርብ ወዳጆች እና ነጋዴ የነበረው ፈረንሳዊው ሙሴ ሳቡሬ ለወዳጆቹ ለፈረንሳዮች ሲመክር ለመስራት ቢፈልጉ ምኒልክ ሙሉ ስልጣን እንደሚሰጧቸው ቃል ገባ።
ዳግማዊ አጤ ምኒልክ በ1882 ዓመተ ምህረት በጥቅምት ወር ንጉሰ ነገስት ሲሆኑ፣ በህዳር ወር ስለባቡር ጉዳይ እንዲያነጋግርላቸው ሙሴ ሳቡሬን ወደ ፈረንሳይ ፕሬዚዳንት ሙሴ ካርኖ ዘንድ ላኩት። አውሮፓውያን ኢትዮጵያን ለመከፋፈል የሚያስቡበት ዘመን ስለነበር የምኒልክ ጥያቄ አጥጋቢ መልስ አላገኘም።
በአጥኚዎች በተደረገው ጥናት ሀዲዱ ያኔ ዱር ከነበረችው ከጂቡቲ እንጂ ከተማ ከነበረው ከአቦክ ቢነሳ አስቸጋሪ እንደሚሆን ታወቀ። አቦክ በዚያን ጊዜ የፈረንሳይ ቀኝ ግዛት የነበረችው የጂቡቲ ዋና ከተማ ይሁን እንጂ ወደብነቱ የማይወደድ ነበር። ከዚህም ሌላ ሀዲዱን ከአቦክ ለመጀመር መንገዱ መልካም ባለመሆኑ ከጅቡቲ እንዲጀመር የመሐንዲሶቹ ጥናት ወሰነ።
ምኒልክ ከፈረንሳይ መንግስት የሚጠብቁት መልዕክት እየዘገየ በመሄዱ የቴክኒክ አማካሪያቸው የነበረውን ሙሴ አልፍሬድን ኢልጎ ከማንኛውም ኩባንያ ጋር ተዋውሎ ሀዲዱን ለማሰራት የሚችልበትን ፍቃድ እና የሚዋዋልበትን የውል አይነት መጋቢት 1ቀን 1886 ዓ.ም የተጻፈውን በማህተማቸው አትመው ሰጡት።
ይህን ፍቃድ እና የሚዋዋልበትን መንደርደሪያ ሀሳብ ሙሴ ኢልግ ካገኘ በኋላ ከሸፍኔ ጋር በመሆን ወደ ፓሪስ ከተማ በመሄድ ቢሮ ከፈቱ። ከዚያም ከፈረንሳይ መንግስት እና ከባለጠጋዎች ጋር ንግግር ጀመሩ። ብዙ ሰዎች እንደሚሉት የባቡር ሀዲድ ስራ በውል የተቀበለው ኢግል ነው። ኢግል ከሌሎች ኩባንያዎች ጋር የሚዋዋልበት የውል አይነት ተቀብሎ የምኒልክ ወኪል የሆነ ሰው እንጂ ራሱ እሰራዋለሁ ብሎ የስራ ተቋራጭነትን ከምኒልክ ጋር አልተዋዋለም።
ስለ ሀዲዱ መዘርጋት ጉዳይ የሚያነጋግሯቸው ሀብታሞች ሁሉ “የባቡር መስመር ቢዘረጋ ምን ጥቅም ይገኝበታል” የሚል ጥያቄ ስላቀረቡ ጥናቱ ተፈጽሞ ውጤቱ ቀረበ። ስለዚሁ ጥናት ጉዳይ ኬለር እንደጻፈው በ50 ሺህ ግመሎች የሚጫን 12 ሺህ ቶን ጭነት በየዓመቱ ከሸዋ ብቻ እንደሚመጣ ተረጋገጠ። ይህም ጭነት ሲተነተን 33ሺህ የግመል ጭነት ቡና 1ሺህ 200 የግመል ጭነት ቆዳ ፣500 የግመል ጭነት የዝሆን ጥርስ ሌላም ዕቃ ነው።
ገቢ ዕቃስ ተባለ ወደ አገር ውስጥ የሚገባው 6ሺህ 800 የግመል ጭነት ከጥጥ የተሰሩ ልብሶች፣ 7ሺህ 500 የግመል ጭነት ጭነው አንድ ሺህ የግመል ጭነት የተለዩ እቃዎች መሆናቸውን አጥኚው ኮሚቴ አረጋገጠ። የገቢ ዕቃ ከጠረፍ አዲስ አበባ ድረስ 25 ቀን ጉዞ እንደሚፈጅበት እና ለአንድ ቶን ክብደት ላለው ዕቃ ከ73 እስከ 77 ብር መከፈሉን አጠና።
ከሌር በመጽሐፉ እንደሚተነትነው በዚህች ሀብቷ ባልተነካ ድንግል መሬት ገብቶ ስራ መጀመሩ ለአውሮፓ ብዙ ጥሬ ዕቃ ማቅረብ እንደሚቻል ተረጋግጦ ሀብታሞች ተደሰቱ። የመዘርጊያውስ ዋጋ ተባለ።
በዚህች በታወቀች አገር ውስጥ የሀዲዱ መዘርጊያ ዋጋ ይህን ያህል ይሆናል ተብሎ ለመወሰን አስቸገረ። እንዲያው በደፈናው እንደ አፍሪካ አገሮች ግምት ተባለና ለአንድ ኪሎ ሜትር ርቀት አንድ መቶ ሺህ ፍራንክ እንደሚያስፈልግ ተገመተ። ጠቅላላ ማሰሪያውም ከ33 ሚሊዮን 500 ሺህ ፍራንክ ይሆናል ተባለ።
… የተጠቀሱት እና ሌሎችም ነገሮች ሆነና የባቡሩ ሀዲድ መዘርጋቱ ስራ በ1890 ህዳር 22 ቀን ጅቡቲ ላይ ተጀመረ። የፈረንሳይ መንግስትም ከተማውን ከአቦክ አንስቶ የሀዲዱን ስራ ወደ ተጀመረበት ወደ ጅቡቲ ማዘዋወሩን ቀጠለ። የባቡሩ መስመር ስራም እየተፋጠነ ሄዶ የመጀመሪያው ባቡር ከጅቡቲ ተነስቶ በ1893 ዓ.ም ሐምሌ 15 ቀን ከኢትዮጵያ ግዛት ደወሌ ደረሰ። ይህ የመጀመሪያው ባቡር ከጅቡቲ ተነስቶ ከወሰን የመጀመሪያ ጣቢያ ደወሌ ለመድረስ አምስት ሰዓት ተኩል ፈጀበት።
የሀዲዱ መዘርጋት ስራ ይካሄድ ጀመር። ለስራው እንቅፋት ከሆኑ የሰው ልጆች በተጨማሪ ምስጦችም ሌሎች ተቋዋሚዎች ነበሩ። በብዙ የአውሮፓ እና የእሲያ አገሮች እንደሚደረገው ለሀዲዱ መዘርጊያ አግድሞሽ እንጨት አለፍ አለፍ እየተደረገ ተጣለ።
በላዩም ላይ ሀዲዱ በብሎን እየታሰረ ስራው ፎቀቅ አለ። በጥቂት ቀናት ውስጥ ምስጦች አግድሞሹን እንጨት በልተውት ባዶ ብሎንና ሀዲዱን ለኩባንያው ተውለት ፤የሥልክ መስመሩን ስራ ከሀዲዱ ስራ ጋር አብሮ ይጓዝ ስለነበር ለስልክ መዘርጊያ የተተከሉ እንጨቶችም በምስጥ ተበሉ።
ይህንን ሁኔታ ጸሐፊው ፓውሎስ ኞኞ እንደሚከተለው ገልጸውታል። ሚስታቸውን እቴጌ ጣይቱን ወዳጆቻቸውን ወንድማቸውን ራስ መኮንን ዋና ጠላቶቻቸውን ኢጣሊያን እንግሊዝን ፈረንሳይን በጦርነትም በፖለቲካም በልመናም በግዴታም ድል የነሱት ምኒልክ በምስጥ ግን መሸነፋቸውን አሜን ብለው ተቀበሉ።
ምኒልክም በወቅቱ ለነበረው የቴክኒክ ተቆጣጣሪ “እንዲያው ምስጥ በሌለበት ደጋ ደጋውን አድርጋችሁ ብታመጡ” በማለት ሃሳባቸውን ሲያቀርቡ አማካሪው ኢግሊም “ጃንሆይ አዳል መሬት ውስጥ ምን ደጋ አለ“ቢላቸው፣ ምኒልክም “ስማኝ ኢግል አንዳንዱን በጦርነት ሌላውን በማስፈራራት እና በጉልበት አሸነፍኩኝ፤ ከውጭም ከአገሬ ሰው ጋር ተጣላሁ፤ ጂማ ከፋ በደቡብ ኢትዮጵያ ያለው ሰው በጨለማ መቅረቱ ነው፤ በሙሉ ነጭ አባይ ድረስ ማለቴ የከፋውም ንግድ እንዲሄድ ብዬ እንጂ እኔ የሸዋው ነጋዴ የሰጠኝ ይበቃኝ የለም እንዴ፤ ከሰው በኩል ያለውን እኔ ጨርሻለሁ፤ ከምስጥ ጋር ያለውን እናንተ ጨርሱ እንጂ የባቡሩ ስራ እንዳይቋረጥ ነግሬሃለሁ….”ሲሉ ኢንጂነር ኢልግን አስጠነቀቁት። ኢንጀነሩም የአግድሞሽ እንጨት የነበረውን በብረት በመለወጥ አስቸጋሪ የነበሩት ምስጦቹም ድል ተነሱ።
በእቴጌ ጣይቱ በራስ መኮንን እና በሌሎች መኳንንቶች የተጠነሰሰው የባቡር መስመር መዘርጋት ስራ ተቃውሞ በተግባር ይገለጽ ጀመር። በሀዲዱ መስመር ስራ አካባቢ እያደፈጡ ሰራተኞችን ህዝቡን በተኩስ ብዛት ያሸብሩት ጀመር። በወቅቱ 30 ሰራተኞችም ተገደሉ። ወረበሎቹም ፈረንጆቹን ጭምር ያባርሩ ጀመር።
ሰራተኞቹ ፈረንጆቹንም እንደ አረብ እየጠመጠሙ እና እያገለደሙ በየአረቡ ቤት ይደበቁ ጀመር። በኤድን ያለው የፈረንሳይ መንግስት ወኪል በጅቡቲ ያሉትን ዜጎቹን ለማስጠበቅ በጦር መርከብ የተጫኑ ወታደሮችን ወደ ጅቡቲ ላከ።
በአፋር በረሃ ውስጥ ሁማ በተባለ ቦታ ሽፍቶች ከባድ ግጭት አድርሰው ከሰራተኛው መሃል የተወሰኑትን ከገደሉ በኋላ የሀዲዱን መስመር የሚሰሩት ሰራተኞች ተበታተኑ። አዲስ እየተቀጠረ የሚመጣው ስራተኛ በአንዲት ጥይት ጩኸት እየተደናበረ ይጠፋ ጀመረ።
ጉዳዩ ለምኒልክ ቀረበ። ምኒልክም “በሊዋ ምክሩበት” አሉ። የስራ ተቃዋሚዎች ሽብር ለማስነሳት አስበው “አገሩን በጦር ይመታ”አሉዋቸው። ምኒልክ ግን “ወንበዴው ያለው ከጉያዬ ;በጦር ይመታ የምትሉት ምንም ያላደረገውን የአገሩን ህዝብ ነው፤ እኔ አውቅበታለሁ” ብለው ስብሰባውን በተኑ።
ከነጮች ጋር ተማክረው በፈረንጅ ሹም የሚታዘዙ የኢትዮጵያን ወታደሮች ለጥበቃ አሰማሩ። ለስድስት ለሰባት ሰራተኞች አንድ ጠመጃ የያዘ ጠባቂ ተደረገ። እየሰረገ የሚመጣውን ሽፍታ እያስያዙ በየጎሳው ባህል እንዲሰቀል እና መቀጣጫ እንዲሆን በገመድ እየተንጠለጠለ ስምንት ቀን ያህል እንዲቆይ አደረጉ። ረብሻውም ጋብ አለ።
እንዲህ ያሉ እና ከባባድ ችግሮችን በማለፍ ሁሉም ስራዎች በአግባቡ ተካሂደው የመጀመሪያው ባቡር ታህሳስ 14 ቀን 1895 ዓ.ም በጥር ማለቂያ በተመሰረተችው ድሬዳዋ ደረሰ። ከጂቡቲ ከንጋቱ በ12 ሰዓት የተነሳው ባቡር ድሬዳዋ የገባው ከምሽቱ 2 ሰዓት ሲሆን፣ ነው።
ከጅቢቲ ድሬዳዋ ለመድረስ 14 ሰዓት ፍጅቶበታል። (ለዚህ ጽሑፍ አጤ ምኒልክ በጳውሎስ ኞኞ የተጻፈውና በ1984ዓ.ም የታተመው እና አጼ ምኒልክና የኢትዮጵያ አንድነት በተክለጻድቅ መኩሪያን/ የ1983 ድጋሚ እትም/ ተጠቅመናል።)
አዲስ ዘመን ታህሳስ 18/2013