የሽምግልና ፋይዳ ብዙ ነው፡፡ በጋብቻው፣ በእርቁና በድግሱ ሽማግሌዎችና የሀይማኖት አባቶች ያስፈልጋሉ፡፡ በዚህም ተጋቢዎችን ያጣምራሉ፤ የተጋጩን ያስታርቃሉ፤ደጋሾችን ይመርቃሉ… ወዘተ፡፡
በጋብቻ ላይ ሽማግሌ ያለው ፋይዳ ከፍተኛ ነው፡፡ይህ ፋይዳው በገጠር ከእነሞገሱ ቢሆንም፣ በከተሞች ግን ቀለሙ እየደበዘዘ መምጣቱ ይታወቃል፡፡ ሆድ ሲያውቅ ዶሮ ማታ እየሆነ ለይስሙላ ሽማግሌ ይላካል፡፡ ተጋቢዎች ነገር አለሙን ጨርሰው፣ውሉን ጨርሶ ላለመሳት በሚል ብቻ ሽማግሌ ይላካል፡፡ለነገሩ ይህንንም የሚያደርጉት ትንሽም ቢሆን ወግ እና ስርዓቱ በውስጣቸው ስላለ ነው፡፡ ፍቺ ሽምግልና ካየው እንደማይጸድቅ ሁሉ ተጋቢዎች ሽማግሌ ካልላኩ መጋባት አይችሉም የሚል ህግ ስለሌለ በዚህ ብዙ መነጋገር አይቻልም፡፡ ጋብቻ አልጸና እያለ ያስቸገረው በዚህ ምክንያት ይሆን?
ጥንዶች ፍቺ መፈጸም ሲፈልጉ ግን ፍርድ ቤቶች ከሄዱም በኋላ ቢሆን የሽምግልና ፋይዳ ይታያል፡፡ፍርድ ቤቶች ጋብቻው የሚፈርስ እንኳ ቢሆን በቅድሚያ ጉዳዩ በሽማግሌዎች እንዲታይ ያደርጋሉ፡፡ ይህ እንግዲህ ካለው ጠቀሜታ የሚመነጭ ነው፡፡ በዚህ ሽምግልና ምን ያህል ትዳር እንዲጸና እንደተደረገ መረጃው ባይኖረኝም ሽምግልናው ግን አበቃለት የተባለን ትዳር አልጠገነም ብዬ አላስብም፡፡
ከባልና ሚስት ጉዳይ ባሻገር በተለያየ ምክንያት የተጋጩ ወገኖችን ማስታረቅ የሽምግልና ሥራ ነው፡፡ እርቅ ደም ያደርቅ የሚባለውም በዚሁ መንገድ እየተፈጸመ ነው፡፡ በእርቅ ደም የተቃቡ ሲታረቁ አስፈላጊው ካሳ ተፈጽሞ ቂም መያዝ እንዳይኖር ይደረጋል፡፡
ሽምግልና የቤተሰብ ፣የቀዬ ጉዳይ ብቻ የሚታይበትም አይደለም፡፡ የሀገር ጉዳይ አልፎም ተርፎ የሀገሮች ጉዳይ ጭምር ይታይበታል፡፡ የኢትዮጵያና ኤርትራን ጉዳይ በሽምግልና ለማየት ሙከራዎች ተደርገው ነበር፡፡ በሽምግልና የፓለቲካ እስረኞችን ለማስፈታት ተሰርቷል፤በኢትዮጵያና ኤርትራ መካከል ከሀያ ዓመታት በላይ ለሚሆን ጊዜ የዘለቀውን አለመግባባት ለመፍታት ሽማግሌዎች ብዙ ጥረት አድርገዋል፡፡
በሀገራችን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተለያዩ አካባቢዎች እንደ ሰደድ እሳት ለተቀጣጠሉት ግጭቶችና አለመግባባቶች መፍትሄ ለማምጣት ሽምግልናው ርብርብ እያደረገ ነው፡፡ ማንም እንደሚረዳው ሽማግሌዎቻችንና የሀይማኖት አባቶቻችን ለወራት እንቅልፍ አጥተዋል፡፡ ዛሬ የእዚህ ክልል እና የዚያ ክልል ነገ ደግሞ የዚያ ክልልና የዚያ ክልል ፣የዚያ ከተማ ፣ወዘተ፣ ጉዳይ ባተሌ አድርጓቸዋል፡፡
በሀገሪቱ የተለያዩ ክልሎች እና አካባቢዎች የተቀሰቀሱት አለመግባባቶችና ግጭቶች የበሉት የሰው ሕይወት፣ የጎዱት አካልና፣ ያወኩት ጤና፣ ያወደሙት ጥሪት፣ያስከተሉት መፈናቀል አላስቀምጥ አላስተኛ ብሏቸዋል፡፡ ወጥቶ መግባት፣ ሰርቶ መብላት፣ ወዘተ ስጋት ውስጥ ወድቀዋልና ነገ በእጅጉ አሳስቧቸዋል፡፡ በእዚህ የተነሳም እሳት ማጥፋት ላይ ተጠምደዋል፡፡
ባለፈው ሳምንት ከኦነግ ታጣቂ ሀይል ጋር በተያያዘ የተፈጠረውን አለመግባባት ለመፍታት አባገዳዎችና ሀደ ሲንቂዎች መጀመሪያ በአዲስ አበባ ቀጥሎም በአምቦ ከተማ በተካሄደ መድረክ ሁለቱን ወገኖች ያስማሙበት ሂደት ተጠቃሽ ነው፡፡ በእዚህም ከኦነግ ታጣቂዎች ጋር በተያያዘ የተፈጠረውን ውጥረት የሚያረግብ ተግባር ተከናውኗል፡፡
እንደሚታወቀው በኦነግ ታጣቂዎች እንቅስቃሴ ምስራቅና ምዕራብ ወለጋ እንዲሁም ቤንሻንጉል ጉሙዝ ካማሺ ዞን ክፉኛ ተጎድተዋል፡፡ የዜጎች ህይወት ጠፍቷል፤የተፈናቀሉት በርካታ ናቸው፤ትምህርት እና ትራንስፖርት ተስተጓጉሏል …ወዘተ፡፡
ጉዳዩ ሁለቱን ወገኖች ሲያወዛግብ ቆይቶም የኦሮሚያ ክልል የፌዴራል መንግሥቱ ጣልቃ እንዲገባ በጠየቀው መሰረት መከላከያ ከብዙ ጥናት እና ትዕግስት በኋላ እርምጃ ወደ መውሰድ መግባቱ ይታወቃል፡፡ በዚህም አካባቢዎቹ ለወራት የራቃቸውን ሰላምና መረጋጋት ማግኘት ጀምረዋል፡፡
የክልሉ አባገዳዎችና ሀደ ሲንቄዎች ስምምነት እንዲመጣ መስራታቸው ይህን የሰላም ቡቃያ በመጠበቅ ለበለጠ ውጤታማነት ለማድረስ የበኩሉን ሚና ሊጫወት እንደሚችል ይታመናል፡፡ በአማራ እና ትግራይ ክልል መካከል በራያ እና በወልቃይት ጉዳይ ላይ የተፈጠረው ውዝግብ ያሳሰባቸው የሀገር ሽማግሌዎች የሁለቱን ክልል ርእሳነ መስተዳድሮች አገናኝተው ማነጋገራቸው ይታወሳል፡፡ በሁለቱ ክልሎች መካከል ያለውን ውጥረት የሚያረግብ ንግግር ከርእሳነ መስተዳድሮቹ ሰምተናል፡፡
የሰላም ሚኒስቴር በአዲስ አበባ ከሀገር ሽማግሌዎችና የሀይማኖት መሪዎች ጋር ትልቅ መድረክ ማካሄዱ ይታወሳል፡፡ በእዚህ ታላቅ መድረክ ላይም የሰላም ሚኒስትሯ ወይዘሮ ሙፈሪያት ካሚል የተገኙ ሲሆን፤ የሀገር ሽማግሌዎች ለሀገር ሰላምና መረጋጋት አጥብቀው እንዲሰሩ ጠይቀዋል፡፡
በምስራቁ የሀገሪቱ ክፍል በአፋርና በሶማሌ ክልል መካከል የተፈጠረውን አለመግባባት ለመፍታት የሁለቱም ብሄረሰቦች የአገር ሽማግሌዎች መምክራቸውም እነዚህ የሀገር እንቁዎች ለሰላም ሲሉ እፎይታ ማጣታቸውን ያመለክታል፡፡
እንዳልኩት እነዚህ የቅርቦቹ ናቸው፡፡ በቡራዩ የተፈጠረውን ግጭት ተከትሎ የጋሞ የሀገር ሽማግሌዎች ያበረከቱት አስተዋጽኦ አይዘነጋም፡፡ በሶማሌ እና ኦሮሚያ ክልል አዋሳኝ አካባቢዎች ግጭት ተቀስቅሶ በርካታ ወገኖች ህይወታቸውን ባጡ ሌሎች በርካታ ዜጎች ደግሞ በተፈናቀሉ ጊዜም ግጭቱን በማስቆም ሁለቱም ወገኖች እንደ ቀድሟቸው እንዲኖሩ ለማድረግ ያልፈነቀሉት ድንጋይ አልነበረም፡፡
ሽማግሌዎቹ ከፓለቲካ ትኩሳት ጋር በተያያዘ በጥሞና መንቀሳቀስ ባልቻሉ፣ ሆድ በባሳቸው ወገኖች ወይም በእኩይ ተግባር አራማጆች ሴራ ሳቢያ ግጭት ውስጥ የገቡትን ወንድማማችና እህትማማች ኢትዮጵያውያን አንተም ተው አንተም ተው እያሉ አንደ ቀድሟቸው እንዲኖሩ እያደረጉ ናቸው፡፡ የሰላም መልዕክተኛ መሆናቸውን ያረጋገጡ ሌሎች በርካታ የሽምግልና ስራዎች ባለፉት ዘጠኝ ወራት ተሰርተዋል፡፡ ሽምግልናው የጀመረውን ዳር ሊያደርሰው እንደሚችል ይታመናል፡፡
መንግሥት እነዚህን ግጭቶች በሀይል ለመፍታት ከመንቀሳቀሱ በፊትም ሆነ የሀይል እርምጃ ከወሰደ በኋላ ነገሮችን ወደ ቀድሞ መስመራቸው ለመመለስ ሲጠቀም የሚታየውም የሀገር ሽማግሌዎችንና የሀይማኖት መሪዎችን ነው፡፡ በእዚህም ብዙ ተሰርቷል፤ በቀጣይም ሊሰራበት ይገባል፡፡
በሀገሪቱ ባለፉት 27 ዓመታት የተሰራጨው መርዝ ኢትዮጵያዊነትን ቢሸረሽረውም እነዚህ አባቶች ግን ስለአንድነት ስለወንድማማችነት እያስገነዘቡ አንዱ በአንዱ ሊነሳ የሚችልበት መሰረት እንደሌለው እያስገነዘቡ ናቸው፡፡ እኔ አንድም የሽምግልና ሥራ ከዚህ ውጪ ሲንቀሳቀስ አላስተዋልኩም፡፡ ስለአብሮ መኖር ነው የሚናገሩት፡፡
በቅርቡ ሽማግሌዎች ካደረጓቸው ንግግሮች፣ የመንግሥት አካላት የሽምግልናን ፋይዳ አስመልክተው ከተናገሩት መረዳት እንደሚቻለው መሬት ጠብ የሚል ነገር አለመኖሩን ነው፡፡ ንግግሩ ወርቅ ነው፤አድማጩንም ይማርካል፡፡ ዋናው ነገር በእዚህ ላይ ተመስርቶ ተስፋ ሳይቆርጡ ሰላምን ለማስፈን መስራቱ ነው፡፡
በእነዚህ የኅብረተሰብ ክፍሎች ፋይዳ ላይ በደጉ ቀንም ተሰርቶ ቢሆን ኖሮ ወጣቶቻችን እና ሌሎች የኅብረተሰብ ክፍሎች ከመስመር ባልወጡ፣ በወጡም ጊዜ መመለስ ባልቸገረን ነበር፡፡ አለመግባባቶችም እዚህም እዚያም እንደ እንጉዳይ ባልበቀሉ፡፡
መንግሥት በተለያዩ ወገኖች፤ እየተረጨ ባለው ለውጥን የሚገድል መርዝ ሳቢያ እየተቀሰቀሱ የሚገኙ አለመግባባቶችና ግጭቶች እንዲቆሙ እንደ መንግሥት የሚያደርገው እንዳለ ቢታወቅም ይህን ሥራ በዋናነት እነዚህ የሀገር ሽማግሌዎች እና የሀይማኖት አባቶች እንዲይዙት መደረጉ ፋይዳው ከፍተኛ ነው፡፡
የሽምግልናው ፋይዳ እንዲህ ክፉ ቀን ሲመጣ ብቻ መታወቅ የለበትም፡፡ በደጉ ቀን ያላቸው ፋይዳ በተለይ ሥነ ምግባር በመቅረጽ ረገድ ፋይዳ በሚገባ ሊሰራበት ይገባል፡፡ አንዳንዳች ግጭት እንደአሸን የፈላው ፣ለመፍታትም አስቸጋሪ የሆነው በስነ ምግባር ላይ በሚገባ ባለመሰራቱ ነው ይላሉ፡፡ ለእዚህም የሀገር ሽማግሌዎችንና የሀይማኖት መሪዎችን ተጠያቂ ያደርጋሉ፡፡
ሽምግልናው በጥቅማ ጥቅም ተጠልፏል፤ ፓለቲካ ፓለቲካ ይሸታል የሚሉ ወገኖችም አሉ፡፡ ለእዚህም ነው ሽምግልናው በያዛቸው ጉዳዮች ብዙም ውጤታማ ሲሆን የማይታየው ይላሉ፡፡ የመንግሥት ጣልቃ ገብነት እንዳለም የሚናገሩ ፣መንግሥትን አጀንዳ ይዘው ነው የሚንቀሳቀሱት የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡
ሀሳቡ የሽማግሌዎቹና የሽማግሌዎቹ ብቻ መሆን ይኖርበታል፡፡ ሽማግሌዎች በምንም መልኩ የፓለቲካ ሰዎችን አጀንዳ ይዘው መንቀሳቀስ የለባቸውም፡፡ እነዚህና ሌሎች በሽምግልናው ላይ ይስተዋላሉ የሚባሉ ክፍተቶች እንዴት ሊከሰቱ ቻሉ ብሎ በመጠየቅ ምላሽ ሊፈለግላቸው ይገባል፡፡
ሽማግሌዎቻችንና የሀይማኖት መሪዎቻችን ራሳቸውን ሆነው መንቀሳቀስ ይኖርባቸዋል፡፡ እንደ ዲፕሎማት ሳይሆን እንደ ሽማግሌ ማሰብ ይገባቸዋል፡፡ ማለት ያለባቸውን ብለው ማስታረቅ ይጠበቅባቸዋል፡፡
መንግሥታት ሽምግልናውን እንዴት ይጠቀሙበት ነበር የሚለውም መታያት ያለበት ጉዳይ ነው፡፡ ዛሬ መንግሥት የህግ የበላይነትን ለማስከበር በቀጥታ ባለው ሀይል ከመንቀሳቀሱ በፈት እና ከተንቀሳቀሰ በኋላ ሽምግልናውን ለሰላምና መረጋጋት መጠቀሙ መልካም ነው፡፡
ሽምግልናው ቀደም ሲል በዚህ መልኩ አልታየ ሊሆን ይችላል፡፡ ለመፍትሄ ካልተጠራ እንዲሁም የደረሰባቸው መፍትሄዎች በመንግሥት ሥራ ላይ ካልዋሉ ሽምግልና መቀመጥ ለምን ያስፈልጋል፡፡ የፍርድ ቤት ውሳኔ የማይቀበል መንግሥት እንደነበረ ይታወሳል፡፡ ከዚህ አንጻር ያ መንግሥት የሽማግሌዎችን ሀሳብ ይቀበላል ብዬ ለመውሰድ እቸገራለሁ፡፡ ይህ መደገም የለበትም፡፡
በሀገራችን እንደምንመለከተው መንግሥት ሽምግልናውን ሲጠቀምበት የሚስተዋለው በግጭት እና አለመግባባት ወቅት ብቻ ነው፡፡ ባለፉት ወራት ሽምግልናው ላይ ለመስራት የተደረገው ጥረትም ይህን ያመለክታል፡፡ ጉዳዩም በእዚህ የሀገር ሀብት ላይ በትኩረት የመስራት አስፈላጊነትን ያመለክታል፡፡
የእነዚህ እንቁዎች ፋይዳ ይህን ያህል መሆኑ በሚገባ ይታወቃል፡፡ ይሁንና ይህ እሴታቸው በመዛግብት በሚገባ ሰፍሮ ስለመገኘቱ እጠራጠራለሁ፡፡ ሰፍሮ ቢገኝ እንኳ የሚፈለገውን ያህል ነው ብዬም አልገምትም፡፡
በክፉ ቀን ይህን ያህል ወጥቶ የአገርን ሰላምና መረጋጋት ለመመለስ ያገለገለን እሴት ዜጎች እንዲያውቁት፣ ተማሪዎች በሚገባ እየተገነዘቡት እንዲያድጉ በስርዓተ ትምህርት ውስጥ እንዲካተት መደረጉንም እጠራጠራለሁ፡፡ ተደርጎም ከሆነ አሁንም ስስ ነው ብዬ ነው የምገምተው፡፡
እናም ሽምግልናውን ለሀገር ሰላምና መረጋጋት አሁን እንደሚስተዋለው መጠቀሙ እንዳለ ሆኖ በቀጣይ ግን በየብሄረሰቡ በየአካባቢው እንዲሁም አንደ ሀገር ሲከናወኑ የቆዩ የሽምግልና ሰራዎች ህዝብ እንዲያውቃቸው ማድረግ ይገባል፡፡ ለእዚህ ደግሞ ጥናት ምርምር ማድረግ፣ ውጤቴን በሰነድ ማስቀመጥ፣ የመሳሰሉት ተግባሮች መከናወን ይኖርባቸዋል፡፡
የሽምግልና ተቋም እንዲኖር ማድረግም ይገባል፡፡ አሁን ያሉት ሽማግሌዎቻችን እኮ በግላቸው ነው የሚገኙት፡፡ እንደ ክልልም እንደ ሀገርም በየደረጃው የሽምግልና ተቋም እንዲኖር በማድረግ በኩል ራሳቸው ሽማግሌዎቹ ሊሰሩ ይገባል፡፡ መንግሥት ደግሞ ሁሌም ይፈልጋቸዋልና ድጋፍ ማድረግ ይኖርበታል፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ መስሪያ ቤታቸው እዚህ ነው የሚባሉ የሽምግልና ስራዎች የሚከሄድባቸው ተቋማትን ማግኘት የሚቻል አይመስለኝም፡፡ በሽምግልና ላይ ለመሥራት ሞክረን ያጋጠመንም ይሄው ነው፡፡
እናም የቱንም ያህል ብንዘምን ከሽምግልና ውጪ አይደለንም፡፡ በሀገራችን የሚታየውም ይሄው ሃቅ ነው፡፡ የሽምግልናን እሴት ለክፉ ቀን ብቻ መፈለግ የለብንም፤ለደጉም ቀን ሥራ ላይ በማዋል ዜጎችን ለመቅረጹ ሥራ መጠቀም ይገባል፡፡
አዲስ ዘመን ጥር 21 /2011
ኃይሉ ሣህለድንግል