አዲሱ ገረመው
እንደ ልምድ ሆኖ ብዙ ሰዎች የቀበሌ ስም ሲጠራ ጥሩ አይሰማቸውም። ቀበሌ ከደርግ ስርአት ጀምሮ በእርግጥም ጥሩ ስም የለውም።በዚያ ዘመን የብዙዎች ገመና የተበረበረው በቀበሌ በኩል ተብሎ ይታሰባል።
ቀበሌ ላይ ያለው አስተዳደር ድክመት ሌላው ቀበሌን ያስጠላው ጉዳይ ነው።ለጉዳይ ቀበሌ መሄድ መጉላላት ነው የሚል ስጋት በባለጉዳዮች ዘንድ አድሯል።ተገልጋዮች ቀበሌ መጉላላት አለ የሚል ሥነ ልቦና ስለተቀረጸባቸው ቀበሌን ገና ሲያስቡ ይደክማቸዋል፣ ይሰለቻቸዋል፣ ያማረራሉ፣ ወዘተ. አሁን ላይ ወረዳ ተብለው የተሰየሙና በቀድሞ ስማቸው ቀበሌ የሚል እውቅና ያላቸው ተቋማትን ጓዳ የፈተሸ ሰው ብዙ ነባርና እንግዳ የሆኑ ችግሮችን ፈልፍሎ ማውጣት ይችላል። በተለያዩ ሀገር አቀፍ መድረኮች ማዘጋጃ ቤቶች ህዝብ እያማረሩ መሆናቸው እየተጠቀሰ ነው።ህዝቡ የግድ ሆኖ ነው እንጂ ማዘጋጃ ቤት ባይሄድ ይመርጣል።
በሰው ስነ ልቦና ቀበሌ ትንሽ ነው። ትልቁ ሥልጣን ያለው ግን ቀበሌ ውስጥ ነው። በዚህ የመንግስት መዋቅር የአብዛኛው ሰው ቅሬታ የአገልግሎትና ፍላጎት አለመጣጣም ችግር ነው። ለምሳሌ መታወቂያ የሚፈልግ ሰው ብዙ ነው፤ አቅርቦቱ ግን ትንሽ ነው። በዚህ ምክንያት ወረፋ ሲበዛ ሰው ይማራራል። ለዚህም ነው ቦሌም ሄድክ ጉለሌ ቀበሌ ያው ቀበሌ ነው እስከመባል የደረሰው።
የቀበሌው ሹም ወይም ሥራ አስፈጻሚ የሚሆነው ሰው ባለጉዳይ የሚያነጋግረው በሳምንት ሁለት ቀናትን ብቻ ነው። ሌላውን ቀን ለሌላ የመንግስትና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ያውላል ብለን እንውሰድ፤በገራሙ።ከዚህ ውጪ ደግሞ ይህን ተገን አድርጎ ዝም ብሎ ማዘጥዘጥ ወይም ሌላ የኪራይ ሰብሳቢነት ስራ መስራትም ሊኖር ይችላል።
ከቀኑ ውስንነት አኳያ ሲታይ ቀበሌ ውስጥ ከሚገኙ ጽህፈት ቤቶች አቅም በላይ የሆኑ ጉዳዮች ለሥራ አስፈጻሚው ተመርተው ባለጉዳዮች ጉዳያቸውን የሚያስረዱት በእነዚህ ቀናት ብቻ ነው።እነዚህ ቀናት በእርግጥም ለእዚህ አላማ ብቻ ተመድበው ከሆነ ነው።ከእነዚህ ቀናት ላይ ስብሰባ፣ጉብኝት፣ወዘተ የሚወሰዱት ጊዜም ይኖራል።የባለጉዳዮቹ አቤቱታ መልስ የሚያገኘው ከብዙ ቀጠሮ በኋላ ነው። በዚህም መጉላላት ይፈጠራል። ሰውም ምሬት ውስጥ ይገባል።
ቀበሌ በሚባለው የአገልግሎት ሰጪ ተቋም ውስጥ ከሚያሰሉቹ ጉዳዮች አንዱ የአመራር የግል ባህሪ ነው። አንዳንዱ አማራር ራሱን እንደ ሚኒስትር አድርጎ ይቆጥራል። አንዳንዱ መናገር እንጂ ማድመጥ የሚባል ነገር አልፈጠረበትም። እቅጩን እንነጋገር ከተባለ በቀበሌ አገልግሎት ባለ ጉዳይ ጆሮ እንጂ አፍ የለውም፤ አመራሩ ደግሞ አፍ እንጂ ጆሮ አልፈጠረበትም። መናገር ለቀበሌ አመራሮች የተሰጠ መብት ሲሆን መስማት ግን የምስኪኑ ተገልጋይ ግዴታ ነው።
አመራሩ ጆሮ አለው ቢባል እንኳን ጆሮው ያልተገረዘ (ቆላፋ) ስለሚሆን ከሚሰማው ይልቅ የማይሰማው ያመዝናል። ቆላፋ ጆሮ የሚሰማው ግራ ግራውን ብቻ እየመረጠ ነው ይባላል ፤ ይኸውም እንደ ገደል ማሚቶ የሚያስተጋባ የራሱ ንግግር ነው። ስለራሱ እርሱ ራሱ ይናገራል ፤ እርሱ ራሱ በሌላኛው ጆሮው ንግግሩን መልሶ ይሰማዋል።
ተገልጋዩ ቀበሌ ሲደርስ የመናገር እድሉ በሰዓት ስለሚገደብ የአመራሩንም የሰራተኛውንም ድምጽና ጩኸት ለመስማት ይገደዳል። መቼም የምስኪን ህዝብ ጆሮና ቤት ለሁሉም ክፍት ነው ይባል የለ።
በቀበሌ ቋንቋ ተገልጋዩ ማህበረሰብ ሰሚ አገኘ ቢባል እንኳን በአንድ ጆሮ የሚሰማውን ሲያገኝ ነው። በአንድ ጆሮ ሳያጠሩ ከመስማት ደግሞ ጭራሽ አለመስማት ይሻላል። ይህ ደግሞ ሰዎች በሚሰነዝሩበት ትችት፣ ሂስና አስተያየት አመራሮቹን ተማረው ተስፋ ወደ መቁረጥ ጉድጓድ ውስጥ ሊያስገባቸው ይችላል። እናም በዚህ ምክንያት የቀበሌ አመራር ልናጣ ነው? ከዚህ ሁሉ ጥርት አድርጎ ባለጉዳዩን በመስማት ሁለቱም ጆሮዎች ይሰሙ ዘንድ መክፈት፤ በኩክም ከመደፈን መጠበቅ ይሻላቸዋል።
አመራሩ ይህን የሚያደርገው ሥልጣኑን ማሳየት ስለሚሻ ነው። የሚቻለውን ነገር አይቻለም የማለት አባዜ አለበት። በመሠረቱ አመራር የማይቻለውን ነገር እንዲቻል አድርጎ ችግር ሲፈታ ነው ጥንካሬው የሚታየው።
አንድን የቀበሌ ሥራ አስፈጻሚ ሹም ማነጋገር የሚቻለው በሳምንት ሁለት ቀናት ብቻ ነው ተብሎ ከተጻፈው ማስታወቂያ በላይ ምን የሚያናድድ ነገር አለ? በመንግስት ሠራተኞች የስነ ምግባር ኮድ የሥራ ሰዓትን ማክበርና ማስከበር አንዱ ነው። ቢሆንም በአሁኑ ዘመን በመንግስት ቢሮዎች አገልግሎት በሚሰጥበት ወቅት የመንግስት ሹማምንት የሆኑ ኃላፊዎች በቢሮ ውስጥ የሚገኙት በሳምንት ጥቂት ቀናትን ብቻ ነው። እርሱም ለሥራ ከሚውለው ሰዓት አብዛኛው በስብሰባና መሰል ጉዳዮች ይባክናል።
በከተማችን ውስጥ ባሉት ቀበሌዎች ወይም በአዲሱ “የዳቦ ስማቸው” ወረዳ ውስጥ የሚካሄዱ ስብሰባዎች ቁጥር ኅልቁ ቢስነት ሳስብ አገራችን ባለሁለት አሀዝ ዕድገት አስመዘገበች መባል ሲያንስባት ነው እላለሁ። የስብሰባው ፍሬ ግን ያው ስብሰባ ብቻ ቢሆንም ቅሉ።
በየቀኑ ባለ ብዙ አሀዝ ጥያቄዎች የሚስተናገዱባት አገር ዛሬም ስብሰባ ላይ ነች። በኢህአዴግ ዘመን የተጀመረው የአንድ ለአምስት ጥርነፋን ጨምሮ የለውጥ ቡድን፣ ፕሮሰስ ካውንስል፣ ህዋስ፣ መሠረታዊ ድርጅትና መሰል ስብሰባዎች በመንግስት የሥራ ሰዓት ውስጥ በእነዚህ ተቋማት ውስጥ ይደረጋሉ። ታዲያ ተገልጋይ በእነዚህ ስብሰባዎች ሰበብ አገልግሎት ሳያገኝ ሲቀር መማረሩ ትክክል አይደለም ትላላችሁ?
ሹማምንቶች የመንግስትን የሥራ ሰዓት ለመንግስት አገልግሎት በማዋል በመንግስት ሰዓት አላስፈላጊ የሆኑና የሥራ ጊዜን የሚያባክኑ በማህበረዊ ሚዲያ ላይ ጊዜ ማጥፋት ተገቢ እንዳልሆነ እየታወቀ በተቃራኒው የቆሙና የተሾሙበትን ወንበር ሳይቀር የሚያሳዝኑ ብዙ አንቱታዎች ተፈጥረዋል። አገልግሎት በሚሰጡበት ወቅት ቅንነትና ታማኝነት የጎደላቸውም እንዲሁ ብዙዎች ናቸው። መስተንግዶው በመተዋወቅ፣ በገንዘብና መሰል ጥቅሞችን መሰረት ያደረገም ነው።
ህዝብን በቀናነት ያገለግላሉ ተብለው የተሾሙና ኃላፊነት የተሰጣቸው ሰዎች ያላቸውን እውቀትና ጊዜም ለተመደቡበት ሥራ በአግባብ ካላዋሉና የአገልግሎት ፈላጊውን እርካታ ማሳደግ ካልተቻለ ምን ይሰራሉ? በዚህ በኩል ያለው አሠራር አፋጣኝ ማስተካከያ እርምጃ ካልተደረገበት ያው ተቋማቱ ሲብጠለጠሉ ይከርማሉ።
ጉቦ በተባለው ማጎልመሻ ቤቶች የደለቡ አካላትስ ከቀበሌ መች ጠፉ? ከተማችን ውስጥ ያሉት የቀበሌ ሌቦች ከታማኝ አገልጋዮች ቁጥር ጋር ቢነጻጸሩ ትስስራቸው የትዬለሌ ነው። በስም አመራር በሥራቸው ግን የሚተቹ ብዙ ናቸው።
የቀበሌ አመራሮች ግን ሰውን አድምጡ! ችግሩንም ተረዱ! ለይስሙላ ብቻ ቢሮ አትግቡ! ጆሮና አይን ይኑራችሁ! የጆሮ ጥቅሙ ማየት ጭምር ነው። የምታዩት አይን ስላላችሁ ብቻ አይደለም። ጆሮአችሁ ስለሚረዳችሁ ጭምር እንጂ። ሁለቱ ጆሮዎች በትክክል የማይሰሙለት ሰው የሚያየው በድንግዝግዝ ውስጥ ስለሆነ እይታው ተአማኒ አይሆንም። በአንድ ዓይን የምታየው እይታም ተአማኒ ስለማይሆን ምንም ዓይነት ውሳኔ ከማሳለፍ በፊት በቀኝም በግራም መስማትና ማየት ይመከራል።
“ከኑግ ጋር የተገኘህ ሰሊጥ አብረህ ተወቀጥ›› እንዳይሆን ሁልጊዜም ለሌሎች አርአያ በመሆን፤ ቀድሞ ተግባራትን በመፈፀም፤ ሙሉ ጊዜን ለሥራ በመጠቀም የዘወትር ተግባራቸው የሆኑ ሰዎች በቀበሌ ውስጥ እንዳሉም ግን አይዘነጋም።
ክፉኛ እየተስፋፋ ያለውን የቀበሌ የአሰራርና የስነ ምግባር አሉታዊ ወረርሽኝ ለመቆጣጠር እንችል ዘንድ የተደራጁ ተመጣጣኝ የእርምት አቅጣጫዎች የግድ ያስፈልጉናል። ችግሩ ከቀበሌ አልፎ ወደ ክፍለ ከተማም እንዳይደርስ ሳይቃጠል በቅጠል መባልን ይሻል።
ከቀበሌ አንቀርም ፤ዞርን ዞረን ዘግይተንም ቢሆን ቀበሌ እንሄዳለን።በደርግ ዘመን ከራሺያና ከሞት አይቀርም ይባል ነበር፤ከቀበሌና ከሞትም እንዲሁ ነውና ቀበሌን አብረን እናጽዳው እናስተካክለው።
አዲስ ዘመን ታህሳስ 4/2013