አዲሱ ገረመው
በየትኛውም የመንግሥት መስሪያ ቤት የአለቃና ሠራተኛ /ምንዛር/ ተግባር ለየቅል መሆኑ አያጠያይቅም፤ማዶ ለማዶ አይተያዩም፤ሥራ ያገናኛቸዋል። ሁሉም የተሰጣቸው ኃላፊነት አለ፤ሁሉም ግዴታና መብት አላቸው።
አለቃና ሠራተኛ ተግባራቸው ፍጹም ለየቅል ቢሆንም ፣በአንዳንድ የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች ግን በሠራተኛ መተዳደሪያ ህጉ ከተቀመጠው ውጪ አለቃ አዛዥ አናዛዥ ፣ሠራተኛ ደግሞ ታዛዥ፣ብድግ ቁጭ ባይ ሲሆን ይስተዋላል።የእነዚህ መስሪያ ቤቶች አለቆች ሠራተኞችን ልክ እንደግላቸው ንብረት ማለትም ልክ እንደ ካራቫት፣ ካልሲ፣ ጫማ፣ ሸሚዝና ሱሪያቸው የሚያዩበት ሁኔታ ያጋጥማል፤በመሆኑም ለሠራተኞቹ የሚሰጠው ስያሜ በአለቆቹ ትርጉም አሰጣጥ ላይ የሚያርፍ ይሆናል። ምክንያቱም ሠራተኞቹ የመንግሥት ሠራተኞች አይደሉም፤የአለቆቻቸው ሠራተኞች እንጂ። ሲቪል ሠርቪስ ሠራተኛ ለሚለው የሰጠውን ትርጉም ለማን ለማን አውለውት ይሆን የእኔ ጥያቄ ነው ።
የሠራተኞች ስራ ብዛት በመንግሥት ሰራተኛው የስራ ድርሻ መዘርዘሪያ ጥራዝ ላይ በግልጽ መቀመጡ እውነት ነው። በአንዳንድ የመንግሥት መስሪያ ቤቶች አለቃ ትርጉም መሰረት ሠራተኞች የአለቆቻቸው እንጂ የመንግሥት ስላልሆኑ መመሪያውና ደንቡ እንደማይመለከታቸው ነው የሚያውቁት።
እናም ክዋኔያቸው በአለቃቸው መልካም ፈቃድ ብቻ የሚወሰን ይሆናል። በአንድ ግለሰብ ስልጣን ብቻ በመንግሥት ሠራተኛው ላይ ለምን ይወሰናል ተብሎ የሚነሳ ጥያቄ ካለ መልሱ ሠራተኛው የመንግሥት ስላልሆነ ነው የሚል ይሆናል።
አለቆች በጣም የሚታወቁት የስራ ሰዓትን በማስከበር ነው። በእነርሱ አሰራር አንድ ሠራተኛ ሁለት ሰዓት ተኩልን አሳልፎ መግባት በምንም አይነትና ምክንያት ምህረት የለውም። ሠራተኛው መብቱ ሳይሆን ግዴታው ብቻ እየተነበበለት እንዲሰራ የሚፈረድበት ከዚህ ጀምሮ ነው።
ልብ በሉልኝ ማርፈድ ተገቢ ነው እያልኩ አይደለም፤በተለይ ትጉህ የሆኑ ሠራተኞች ከዕለታት አንድ ቀን ባይሞላላቸው በአጋጣሚ አርፍደው ቢገቡ የጽሁፍ ማስጠንቀቂያ ጭምር ሲሰጣቸው መስማት ስለሚያሳምም ነው። እነዚህ ሠራተኞች እኮ በአንድም በሌላም መንገድ ለመስሪያ ቤቱ ለውጥ ትልቅ አስተዋጽኦ አበርክተው ይሆናል። አንዳንዴም ከመንግሥት የሥራ ሰዓት ውጭ ጊዜያቸውን ሰውተው ሰርተው ይሆናል። ታዲያ በትራንስፖርት እጥረት፣ በመንገድ መዘጋጋት፣ በአጋጣሚ በተፈጠረ ችግር ምክንያት ቢያረፍዱ ስለምን የአለቃቸው አፍ ማሟሻ ይሆናሉ?
በነገራችን ላይ ሠራተኞች እንጂ አለቆች ሰዓት የማክበር ግዴታ የለባቸውም። ሆኖም የማስከበሩ ስራ ቀድሞ መገኘትንና ኋላ መውጣትን ስለሚጠይቅ እግረ መንገዳቸውን ለማስከበር ሲሉ ብቻ ሳይገደዱ የስራ ሰዓት ያከብሩ ይሆናል።
ግዴታን እንጂ መብትን ማሳወቅ የማይወዱት አለቆች እጅጉን ሰነፎች ናቸው፤የተቀመጡበትን ወንበር እንኳን አይመጥኑም። በዚህ ላይ ከታችኛው የመንግሥት መስሪያ ቤት እስከ ላይኛው ያለው በእጅጉ ሲተች ይሰማል። በተለይ ከሁለት ዓመታት በፊት በነበሩት 20 ምናምን ዓመታት በየመስሪያ ቤቱ የተቀመጡ አለቆች (ምናልባትም ዛሬም ድረስ በእልቅናቸው የዘለቁ ይኖሩ ይሆናል) ፈጽሞ ፍትሐዊነት የጐደለው ህሊና የነበራቸው በስንፍና የታሪክ ምዕራፍ የሚታሰቡ ናቸው።
ሰነፍ አለቆች የተቋማቸውን የሥራ መግለጫ በተገቢው የማያውቁና የተቋሙን አፈጻጸም በውሸት ሪፖርት ያንቆለጳጵሳሉ።መልከ ጥፉን በስም ይደግፉ እንደሚባለው። “ዘንድሮ ድርጅታችን ጊዜውን በአግባቡ በመጠቀም አንድም ተገልጋይ ባለማስከፋት ከእቅዱ በላይ 700በመቶ በተሳካ ሁኔታ ፈጽሟል።” ሊሉህ ይችላሉ፤ለዚያም በአደባባይ ምንም ይሉኝታ ሳይዛቸው፤ተሀድሶ ነው የሚባለው ያንን እያደረጉ፤እያስደለቁ፤አይ ተሃድሶ።
እኔን የሚያበሳጩኝ ግን የተባለው ሁሉ ሳይገባቸው ሌላው ሲያጨበጭብ አብረው የሚያጨበጭቡት ናቸው። ጎበዝ እስከ መቼ ነው ባልሰማነው ነገር ስናጨበጭብ የምንኖረው? ቆይ ሁሉ የተሟላና የተሳካ ቢሆን እንኳን እንደ“ያኔው”ምርጫ መቶ በመቶ እንከን አልባ ሆኖ መቶ በመቶ ይጠናቀቃል እንጂ እንዴት በ 700 በመቶ ይጠናቀቃል?
ይሄ የሚያሳየው መጀመሪያም እንዳልታቀደ ነው። ይህ ግራ ሲገባኝ አንድ ቀን ከስበሰባው በኋላ አለቃ ተብየው ሪፖርት አቅራቢ ዘንድ ሄድኩና ከአምናው የዘንድሮው እንዴት ከታሰበው በላይ 700 በመቶ ከእቅድ በላይ ተሰራ ስል ጠየቅሁት። ኮራ ብሎ “አምና ያስተናገድነው ፋይልና የዘንድሮው ምን አገናኘው? ዘንድሮ እኮ እንደ ጉድ ነው የሠራነው” አለኝ።
የሌባ አይነ ደረቅ መልሶ ልብ ያደርቅ ይባል የለ ከነተረቱ።ዝንጉርጉር እውነት የሚመሰል ግን ደግሞ ነጭ ውሸት ነው። እንግዲህ መዋሸት የሚደገፍ ባይሆንም ግን ብዙኃን መገናኛ በሚገኙበት መድረክ ላይ ‹‹ጥሩ ውሸት›› ለመዋሸት ‹‹የውሸት አማካሪ›› ብትቀጥር ይሻልህ ነበር አልኩት በልቤ። ለነገሩ እርሱ ሠራተኛውን የትገባችሁ? የት ወጣችሁ? እንጂ ምን ሰራችሁ የሚለው ነገር ጉዳዩ አይደለምና አይፈረድበትም።
የዚህ የውሸት ሪፖርት አንድ ነገር አስታወሰኝ። የ9ኛ ክፍል ተማሪ እያለሁ እናቴ፣ ከአንዲት ልጅ ጋር አንድ መዝናኛ ቦታ ታይተሃል ብላ ስትጠይቀኝ ዋሸሁዋት። ጉዳዩን በተመለከተ ግልጽ የሆነ መረጃ ስለነበራት እንደዋሸኋት ተረድታ ነበር።ስለ ልጅቷ ለሦስተኛ ጊዜ ስዋሻት በጣም ተናደደች።
ለሁለት ሳምንት ያህል ከቤት ወጥቼ እንዳልዝናና ቅጣት ተጣለብኝ፤ ለአንድ ወር ያህል ሞባይል ስልኬን እንዳልጠቀም ተደረግሁ፤ ቴሌቪዥን እንዳላይ ተከለከልኩ። ከዚያን ጊዜ ወዲህ ወላጆቼን ዋሽቼ አላውቅም። ምናልባት ይህንንም አለቃ የበላዩ አለቃ አንዳንድ ማዕቀቦችን እየጣለበት ቢያስተምረው ብዬ ተመኘሁ፤ዳሩ የእርሱም አለቃ ሰነፍ ይሆናል።
ኧረ ጎበዝ! ለምን ፣እንዴት ማለት ያቅተናል? ይቺን ሂሳብ መስራት የማያውቅ ባለሙያ ነው እንዴ የአምናውን ከዘንድሮ የኑሮ ሁኔታ አጥንቶ ኢኮኖሚያችን በሁለት አሀዝ አደገ ሲለን የቆየው። አንዳንዴ ሲጨበጨብልህም እውነት እንዳይመስልህ ፤ዛሬ እጃቸው እሳት እስኪተፋ የሚያጨብጭቡልህ ሁሉ ነገ፣ በዚያው እጃቸው ጦር ይዘውይነሳሉ ነው መልዕክቱ።
አስተውሉ ሰው የሥራው ውጤት ነው። ማንነቱን የሚሰራው ራሱ ስብዕናው ነው። በአንዱ መዝገብ አመላላሽነት ሌላው ተጠያቂ አይደለም። ሎሬት ጸጋዬ ገብረ መድህን ከንጉሥ ተወልዶ አይደለም ሎሬት የሆነው። ጸጋዬን የሰራው ጸጋዬ ነው። ጸጋዬ የሥራው ውጤት ነው። አለቃውም በሥራው ራሱን ይገንባ፤ ደቂቁም ያላመነበትን በግድ አይቀበል።
የምር የግዴታ አንቀጾች የሚያነቡ አለቆች ሥፍር ቁጥር የላቸውም። አሁን አሁንማ፣ ሠራተኛው መብት የሚባልን ነገር በአፈ ታሪክ እንጂ በተግባር አያውቅም። በየሚዲያው ግብር ክፈሉ እያሉን ነጋ ጠባ እያስገነዘቡን ነው፤ በእርግጥም ግብር የአገሪቷ የህልውና ጉዳይ ነው። መክፈልም ግድ ነው።
ነገር ግን በከፈልነው ግብር ምን ተሰራ ብለን ስንጠይቅ ሊቀጡህ የሆነ ህግ ይፈልጋሉ፤ ኧረ ምን እሱ ብቻ፤ ቢችሉ ህገ መንግሥቱን በአመጽ ለመናድ ሞክራችኋል ብለው ወደ ወህኒ ቢያወርዱህ አይጠሉም።ለነገሩ እንዳቅማቸው ይቀጡሃል፤ ታዲያ ምነዋ አለቆች ግዴታችንን ነግረው መብታችንን ነፈጉን? በህግ አምላክ በቆረጥከው ደመወዛችን ምን እንደተሰራ አሳዩን፤ ተምች ይመስል የክብደታችሁን አስር እጥፍ እየበላችሁ አታፍጡብን።
እዚህ መዲናችን ውስጥ ስንት የመንግሥት ሆስፒታል አለ? ያኔ በንጉሡ ጊዜ ከተሠሩት ውጭ ምን ተሠራ? ግብር ከፋይ ነኝ እጄ ላይ ገንዘብ ስለሌለ ህክምና ይሰጠኝ ብትሉ ነጭ ድሃ መሆንህን ሁለነገርህና ቀዬ ሰፈሩ እያወቀው መጀመሪያ የደሃ ደሃ መሆንህን ሦስት ምስክር ይዘህ ቀበሌ አስመስክር ትባላለህ። ደመወዝህ ግን እሱ በፈቀደው እሱ ባጸደቀው አዋጅ ሲቆረጥ ምስክር ቁጠር አትባልም።
አንድ የእጅ ካቴና የሚሠራ ባለሙያ ነበር። አንድ ቀን “ቀን ጎደለበትና” በሠራው ካቴና እጁ ገባ። ይሄማ እኔ የሰራሁት ነው እፈተዋለሁ ብሎ ቢታገል በየት በኩል። በመጨረሻም ሲያቅተው አምርሮ ለካ አንድ ቀዳዳ መተው ነበረብኝ አለ። ግድ የላችሁም ለክፉ ቀን የሚሆናችሁን አንድ ቀዳዳ እንኳን አስቀሩ። ፍትህ ባይሆናችሁ ማምለጫ ይሆናችኋል።
አዲስ ዘመን ህዳር 27/2013