የኢትዮጵያን አግሮ ፓስቸራሊስት ዴቨሎፕመንት አሶሴሽን ዳይሬክተር ናቸው። በቅርቡ ደግሞ የአዲስ አበባና ዙሪያዋ ንግድ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ሆነው አገራቸውን እያገለገሉ ይገኛሉ።ልጆቻቸውን አባትም እናትም ሆነው አሳድገዋል።የዛሬው የሕይወት ገጽታ ተጋባዥ አቶ ኤልያስ ጉዮ። የዝግጅት ክፍላችን ከሕይወት መንገዳቸው በብዙ እንደምታተርፉ በመተማመን እንግዳችን አድርገናቸዋል ።
«መንግሥት›› ቅፅል ስም
የተወለዱት በቦረና ዞን ተልተሌ ወረዳ ቀሎ ቀበሌ ውስጥ ነው።በባህሪያቸው ችኩል ልጅ ነበሩ። ምክንያቱ ደግሞ ከሁሉ ቀድሞ የተሻለ ማድረግ ጉጉት ስለነበራቸው ነው።ስለዚህም ሌሎች ሳይቀድሟቸው መፍጠን ይፈልጋሉ። ይህ ሳይሆን ከቀረ ይናደዳሉ፤ ይቆጣሉም።ትንሽ ከቆዩ በኋላ ግን ይረሳሉ።ደግና የዋህ፤ ታዛዥና መተባበር የሚወዱም ናቸው።
በአለባበሳቸው ሽቅርቅር የሚሉና ከከተማ ልጆች ጋር የሚመሳሰሉ መሆናቸው ደግሞ በመንደሯ ትኩረት እንዲስቡ ያደርጋቸው ነበር። የማስተባበር ተሰጥኦ ስላላቸው ‹‹መንግሥት›› የሚል ቅጽል ስም እንዲወጣላቸው አስችሏቸዋል።የተለያዩ ቦታዎች ላይ የማስተባበር ዕድሉን ያገኛሉ።ያንን ዕድል በአግባቡ ይጠቀሙበት ነበር። በዚህ ምክንያት መንግሥት የሚለው ቅጽል ስም ልዩ መጠሪያቸው ነበር።
ቤተሰቦቻቸው አርብቶ አደርና አርሶአደሮች በመሆናቸው በወተትና በማር እንክብካቤ አድገዋል።በዚያ ላይ የመጨረሻ ልጅ በመሆናቸው የሚደርስባቸው ጫና ቀላል ነበር።ይሁንና ከብት በመጠበቅና እርሻ ማረስ አልቀረላቸውም።በመንደራቸው ተወዳጅ የሆነውን የትግል ጨዋታን ያዘወትሩ ነበር።የእግርኳስ ጨዋታም ወዳጅ ናቸው።
በነፃነት ነው ያደጉት።በቤት ውስጥ ሀሳባቸውን እንዲገልጹ ይበረታታሉ።ነገ አገር ተረካቢ መሆናቸውን ስለሚረዱም ከአረጋውያን እግር ስር ቁጭ ብለው ትምህርት ይቀስሙ ነበር።ይህ ደግሞ እያንዳንዱ ችግር አዲስ እንዳይሆንባቸውና በቀላሉ መፍታት እንዲችሉ አስተምሯቸዋል።ከዚህ ውጪ ‹‹የዋህ በመሆኔ እስከዛሬ ለመኖር አብቅቶኛል።በፈተና እንዳልወድቅም ጠብቆኛል።ቅን አዕምሮ እንዲኖረኝም አድርጎኛል›› ይላሉ።
የቀለም ትምህርት
በአቅራቢያቸው ትምህርት ቤት ባለመኖሩ ወንድሞቻቸው ጋር ተልተሌ ከተማ በመሄድ ነው የጀመሩት። በቤት ውስጥ ሁሉም በፍቅር ዓይን ይመለከታቸዋልና በእንክብካቤ ተልተሌ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት እንዲማሩ አደረጓቸው። በዚህ ትምህርት ቤት እስከ ስድስተኛ ክፍል ቆይተዋል።
ቀጣዩን ክፍል የተከታተሉት ያቤሎ ሲሆን፤ እዚያም ቢሆን የወንድሞቻቸው ድጋፍ አልተለያቸውም።በያቤሎ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤትም እስከ 11ኛ ክፍል ቆይተዋል።የተሻለ ትምህርት ፍለጋ ወደ ነገሌ ቦረና ያቀኑ ሲሆን፤ ነገሌ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የ12ኛ ክፍል ትምህርታቸውን ተምረዋል።
ቀጣዩ የትምህርት ጉዟቸው ቢሾፍቱ የወሰዳቸው ሲሆን፤ ማኔጅመንት ኢንስቲትዩት በመግባት በሥራ አመራር የትምህርት መስክ ዲፕሎማቸውን መያዝ ችለዋል። ከዚህ በተጨማሪ በቢዝነስ አድምንስትሬሽን ከሪፍት ቫሊ ዩኒቨርሲቲ ዲግሪያቸውን ያዙ።ከዚህ ውጪ የተለያዩ ሥልጠናዎችን ከመውሰድ ባለፈ ትምህርታቸውን አልቀጠሉም።ምክንያቱ ደግሞ በሙያው በሚሰሩበት ጊዜ የተለያዩ ኃላፊነቶች ስለነበሩባቸው ነው።ይሁን እንጂ ትምህርትን ማቆም እንደማይፈልጉና አሁንም ለመማር ራሳቸውን ዝግጁ እያደረጉ መሆናቸውን አጫውተውናል።
ወደ ግል ሥራ
የመጀመሪያ ሥራቸውን አሃዱ ብለው የጀመሩት በኮንሶ በመካነ ኢየሱስ የልማት ድርጅት ውስጥ ነው። ቀጥሎ ወደ ነገሌ ቦረና ተዛውረው አገልግለዋል።እዚያም ማህበረሰቡ የሚያምናቸውና የሚወዳቸው ስለነበሩ በ1983 ዓ.ም ሊበን ከተማን በምክትል አስተዳዳሪነት እንዲመሩ ተመርጠው አገልግለዋል።ብዙም ሳይቆዩ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት የኢኮኖሚ ዘርፍ ሥራ አስፈጻሚ ሆነው ተሾሙ።
በዚህ ቦታ ለአራት ዓመት ያህል እንደሰሩ የሚናገሩት ባለታሪኩ፤ ማህበረሰቡን የሚጠቅም ሥራ እንዳሰቡት ሳይፈፅሙ እንደለቀቁ ይናገራሉ።ለዚህ ያበቃቸው ደግሞ የአሠራሩ ሁኔታ የግለሰብን ኪስ መሙላት እንጂ ለማህበረሰቡ መድረስ ባለመሆኑ ነበር።በዚያ ላይ በቤተ ዘመድ የተተበተበ ሙሰኛ አሠራር የሰፈነበት ጊዜ ነበር።የብሔር ጉዳይም በዚያው ልክ ትልቅ ቦታ ይሰጠዋል።እናም ይህንን መመልከታቸው ዘወትር ያንገበግባቸው ነበር።ሆኖም እርሳቸው ከዚህ ካፈነገጡ ችግሩን ተጋፍጦ የሚኖር ሊጠፋ ይችላል በሚል ቁርጠኝነት ትግላቸውን አጠናክረው ቀጠሉ።
በትግል ሂደት ውስጥ የሚወዱትን በዳዴ ጋዱ ጋዲሳ የተባለ ጓደኛቸውን ማጣታቸውን ይናገራሉ። ‹‹ጓደኛዬ ምንም ዓይነት ፖለቲካ ውስጥ ገብቶ አያውቅም ነበር።ፍላጎትም አልነበረውም። በኦነግ በመጠርጠሩ ነበር ከቤቴ ወስደው የገደሉት።›› በዚህ ምክንያት ባለታሪካችን በዚያ መስሪያ ቤት መቆየታቸው ለቤተሰባቸውም ሆነ ለራሳቸው ስለማይበጅ ለመልቀቅ ተገደዱ። ይህን ጊዜ ሲያስታውሱ እንባ እየተናነቃቸው ነበር።
ሥራ ከለቀቁ በኋላ ለተወሰነ ጊዜ ራሳቸውን ማረጋጋት ስለነበረባቸው በቤታቸው ለሁለት ዓመታት እንደቆዩ ያጫወቱን አቶ ኤልያስ፤ ቤተሰቦቻቸው የእርሳቸው የሆኑ ከብቶችንም ያረቡላቸው ስለነበር እነርሱን እየሸጡ በሚልኩላቸው ገንዘብ ኑሯቸውን እንደመሩ ያስታውሳሉ።ቆየት እንዳሉ ግን ፓስቸራሊስት ኮንሰርን አሶሴሽን የሚል ግብረሰናይ ድርጅት ከጓደኞቻቸው ጋር ሆነው በማቋቋም መስራት ጀመሩ። በዚህ እንቅስቃሴያቸው በዋናነት በአርብቶ አደር አካባቢ ልማት ማስፋፋት ላይ ትኩረታቸውን አደረጉ።
ትንሽ እንደሰሩም የራሳቸውን ኢትዮጵያን አግሮ ፓስቸራሊስት አሶሴሽን በሚል ማቋቋም ቻሉ።በዚህም ብዙ ወጣቶች፣ የኤች አይቪ ህሙማንና ሴቶች ተጠቃሚ እንዲሆኑ አደረጉ።ከዚህ ጎን ለጎን ደግሞ ለራሳቸው በንግዱ ዘርፍ የሚጠቀሙበትን ሥራም ሲሰሩ ቆዩ።ይህም ማዕድናትን ኤክስፖርት የሚያደርጉበት ድርጅት ሲሆን፤ ላንድ ኢንደስትሪ ሚኒራል ኤክስፖርት ድርጅት ይባላል።
የአገር አበርክቶ
‹‹ራሴን ካወኩ ጀምሮ ለአገሬ ያልሰራሁት ነገር አለ ብዬ አላምንም።ምክንያቱም መጀመሪያ ሥራውን ስጀምር ለአገሬ ምን ይጠቅማል እንጂ ለእኔ ምን እጠቀማለሁ ብዬ ስለማላውቅ ነው›› ያሉን እንግዳችን፤ ራስን ማሸነፍና በሰው ላይ ሸክም አለመሆን ለአገር እንደመስራት ይቆጠራል ይላሉ።በዚህም በዋናነት የሚታዩትን ብቻ ሲያወሱ በድርጅታቸው አማካኝነት የአርብቶአደሮች ቀን በአገር ደረጃ እንዲከበር ካደረጉ መካከል አንዱ ናቸው።በምክርቤት ደረጃ የአርብቶና አርሶ አደሮች ቋሚ ኮሚቴ እንዲኖርም ያስቻሉት እርሳቸውና ሌሎች አጋሮቻቸው መሆናቸውን ያነሳሉ።በተመሳሳይ የተለያዩ ግብረሰናይ ድርጅቶች ውስጥ በመሳተፍና በማቋቋም በአርብቶ አደሮች አካባቢ ልማት፤ ለሴቶች፣ ለወጣቶች ብድር በማመቻቸት የሚሰሩበት አጋጣሚ በመፍጠር በርካቶች ከችግራቸው እንዲላቀቁ ማድረጋቸውም ያወሳሉ።
ኤች አይ ቪ ህሙማን ድጎማ እንዲያገኙ፤ በማንኛውም መስክ ተደራጅተው መስራት የሚችሉ ሰዎች የተለያዩ ምቹ ሁኔታዎች እንዲፈጠርላቸው በማድረግም ለአገራቸው አበርክቶ እንደነበራቸው ያስረዳሉ።የነበረውን ወቅታዊ ችግር፤ የብሔር ፈተና ተቋቁሞ የተቻለን ያህል ለአገር መስራትም አንዱ አበርክቷቸው እንደነበር ይጠቅሳሉ። ሌላው ደግሞ በቅርብ ጊዜ ወዲህ የሚሰሩበት የአዲስ አበባና ዙሪያው የንግድ ምክርቤት ፕሬዚዳንትነት ነው።በዚህ ሥራ ላይ ሆነው ነጋዴዎችን ከንግዱ ማህበረሰብ፤ ከመንግሥት፤ ከአገራትና ማህበረሰቡ ጋር አገናኝተው የሥራ አማራጮችን እንዲመለከቱ ማድረጋቸውን ይናገራሉ።
ነጋዴው ማህበረሰብ ለአገሩ የተቻለውን ሁሉ እንዲያበረክት ማስቻላቸውንም ያነሳሉ።ለዚህ በአብነት የሚጠቅሱት በኮሮና ወቅት እያደረጉ ያለውን ሲሆን፤ በቅርቡ ከኦሮሚያ ልማት ባንክ ጋር በመሆን በወረርሽኙ ምክንያት ለተጎዱ ሰዎች ከ200 ሺህ ብር በላይ ድጋፍ ማድረጋቸውን ይጠቅሳሉ።
‹‹ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል›› እንዳይሆን ነገሩ የኦሮሚያን መሬት በእጅህ አድርገህ አጃቢዎችህ ሳይቀሩ ብዙ ነገር ሲያደርጉ አንተ ለምን የራስህን ነገር አታመቻችም የሚሏቸው ብዙዎች እንደነበሩ የሚያስታውሱትእንግዳችን፤ እጄ ንጹህ በመሆኑ እንደፈለገኝ እንድንቀሳቀስና ዛሬም በሕዝብ ዘንድ እንድወደድ ሆኛለሁ በማለት ሙስናን እንደሚፀየፉ ይናገራሉ።ከሰው ደም፤ ከአገር ንብረት ስርቆትም ነፃ ሆኜ ስላለሁ አሁንም ለአገሬ በዚህ መልኩ አበርክቶዬን የምቀጥል ይሆናል በማለት ቃል ይገባሉ።
የትግል ሕይወት
እርሳቸው ሞፈርና ቀንበር እንጂ ጥይትና መሰል የጦር መሣሪያ አይተውም ነክተውም አያውቁም።ግን ግዳጅ ሲሆን የማይገባበት የለምና ሁሉንም በሦስት ወር ውስጥ ለመሞከር ተገደዋል።ወቅቱ ኢህአዴግ አዲስ አበባን የተቆጣጠረበት ጊዜና አካባቢያቸው ደግሞ የጎሳ ግጭት የተነሳበት ነበር።በዚህም ቤተሰቦቻቸው ተፈናቀሉ፤ ብዙ ፈተናም እየደረሰባቸው ነበር።እናም ይህንን የመከላከሉና ቤተሰቡን የመታደጉ ኃላፊነት የወንዶቹ በመሆኑ ወደ ጫካ ገቡ።
የትግል ሕይወታቸው ከዚህ ነበር የጀመረው።በጊዜው ስለ ኢህአዴግ የሚሰሙት ነገር ተቃራኒ ነበር።መጥፎ እንደሆነና አገርን እንደሚያፈራርስ ጭምር።እናም ከቤተሰብና አካባቢን ከማዳን ባለፈ ለአገር ጠንቅ የሆነውን ኢህአዴግን መዋጋት አላማቸው አደረጉ።የጫካ ሕይወትንም ተለማመዱት። ነገር ግን ያሰቡት ነገር በአሰቡት መልኩ አልተጓዘም።ፖለቲካ የማያውቁት እንግዳችን የደርግ ኮሎኔል ነው ተባሉ።ስለዚህም ከዚያ ሁሉ ጫካ ከገባው ታጋይ እርሳቸው ተነጥለው መፈለግ ጀመሩ።
ምንም ቢመጣ በቀላሉ እንደማይረቱ የሚያውቁት አቶ ኤልያስ አንድ ቀን ግን ሁሉንም ሀሳባቸውን ድባቅ የሚመታ ችግር ገጠማቸው።ጫካ ከገቡት ጓደኞቻቸው ጋር እየተዟዟሩ እያለ መሸሸጊያቸው ሳይደርሱ እግራቸውን እንጨት ወጋቸው።መንቀሳቀስም ተሳናቸው። እናም በወቅቱ ብዙ ሠራዊት ተከታትሏቸው ኖሮ ሌሎቹ ወደ መከላከሉ ሲገቡ ባለታሪኩ ግን ከመያዝ ውጪ አማራጭ አልነበራቸውም።ተፈላጊው እርሳቸው በመሆናቸውም ጓደኞቻቸውን ትተው እርሳቸውን ብቻ ወደ ማረሚያ ቤት ወሰዷቸው።
ትንሽ እንደቆዩ ለጥያቄ ተፈልገው ቀረቡ።‹‹ኮሎኔል ለምን ትወጋናለህ›› የሚለው ጥያቄም ተጠየቁ።እርሳቸውም ስለሚናገሩት ነገር ምንም እንደማያውቁና ኮሎኔል እንዳልሆኑ አስረዱ። ስላልታመኑ ‹‹በቃ ጀነራል ነህ›› አሏቸው።አሁንም እንዳልሆኑ ገለጹ።ግን ሰሚ አላገኙም ነበር።በመጨረሻ ግን በማረሚያ ቤት ከነበሩ እስረኞች አለመሆናቸውን ማረጋገጥ ቻሉ።
ይህ ሲሆን ደግሞ ጥያቄው ተቀየረ ‹‹ለምን የእኛን ሠራዊት አትቀላቀልም›› ተባሉም።እርሳቸውም ቆፍጠን ብለው ‹‹እናንተ ማን ናችሁ፤ ብዙዎቻችሁ ከሌላ ወገን ትመስላላችሁ፤ ለምን ብዬ ከእናንተ እቀላቀላለሁ›› አሉ።እነርሱም የዚህ ትግል ሠራዊት የሁሉም ብሔር ተከታይ እንደሆነና ከእርሳቸው ወገንም ኦፒዲኦ እንዳለ አስረድተው እቅዳቸውን ሰጥተው ለቀቋቸው።
እቅዱን በመያዝም ብዙም ስላልተማመኑባቸውና በውስጣቸው የቀደመው ጥርጣሬ ስለሞላ ሽማግሌዎችንና አባገዳዎችን በመሰብሰብ አማከሯቸው።በዚህም እንደ እነርሱ ዓይነት ታጋይ ይህንን ድርጅት መቀላቀል ካልቻለ ብሔረሰቡ ምንም ዓይነት ጥቅም እንደማይኖረውም ሀሳባቸውን አጋሯቸው።በዚህም ድርጅቱን ተቀላቅለው መስራት እንደጀመሩ አውስተውናል።
አገሬ ብትሆን
‹‹ለአገሬ ሰላም፤ ልማትና ብልጽግና ሁል ጊዜ እመኛለሁ። አገሬ እንድትሆን የምፈልገው የሌሎች አገሮች ተምሳሌትና መሪ ነው።ለዚህ ደግሞ ትክክለኛ መስመር ላይ ያለች ይመስለኛል›› የሚሉት ባለታሪኩ፤ አንዳንዶች ልትፈርስ ነው፤ መስቀልኛ መንገድ ላይ ነች፤ ገደል ጫፍ ቆማለች የሚል የተሳሳተ ምልከታ እንዳላቸው ይናገራሉ። አሁን የተያዘውን መንገድ ተከትለን መጓዝ ከቻልን የድልን ፍሬ እየቀመስን መጓዝ እንችላለን።ወደፊት በተያዘው መስመር ከተጓዝን ብሩህ ነገር ከፊታችን አለ ይላሉ።ተስፋና የሚናፈቅ፤ መጨበጥ የሚችል ነገር ይገኛል።ትናንት ቤት ተቃጥሏል፤ የሰው ሕይወትም በዘግናኝ ሁኔታ ጠፍቷል።ግን መናገር ስለማይቻል አልታየም።እናም የትናንትም የዛሬም መጠፋፋቱ ይቅርና ወደፊት የሚያስገሰግሰንን እንመልከት ይላሉ።
እንደ ባለታሪካችን ሃሳብ፤ ኢትዮጵያውያን በብሔር መከፋፈል የማይሆላቸው ሕዝቦች ናቸው። አበጣባጮች እንደሚፈልጉት እየሆነላቸው አይደለም።ምክንያቱም አብሮነቱ ከውስጡ ያለና ወንድሙን አሳልፎ መስጠት የማይሆንለት ሕዝብ ነው።አብሮ መብላትና መጠጣቱን ያስታውሳል፤ ለእርሱ ፈጥኖ ደራሹ ጎረቤቱ እንጂ ብሔሩ እንዳልሆነ ያምናል።የሥጋ ወይም የብሔር ዝምድና ሳይሆን ሰውነት አብልጦ የሚወደውና ሊያተርፈው የሚፈልገው ነው።
በባህሉ፤ በሃይማኖቱ የማይፈቀደውን ነገር ሊጥስም አይወድም።እናም በትንሽ እንዝላሎችና ጨካኞች ብዙኃኑን መውቀስ መቆም አለበት።ማንነቱ ባያግደው ኖሮ ዛሬ አገር ይጠፋ ነበርና የነበረውን ችግር በመረዳዳት አሸንፎ አሁንም ወደፊት መጓዝ ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል።ከተደረገው የንብረት ማጥፋትና የሰው ሕይወት ማጣት በላይ ሕዝቡ ያተረፈው ይበልጣልና አሁንም መንቃትና ለአገራችን መቆም ያስፈልጋል።
አሁን እየተደረገ ያለው ተግባር አላማ ሳይሆን ጥቅምና ሆዳምነት፤ ስግብግብነት መሆኑን ተረድተን መታገል መጀመር ይገባናል።ሆዳሞች መልካሙን የመመልከቻ ዓይን የላቸውም።ስለዚህም ትውልዱን በማስተማርና አዕምሮውን በመገንባት አንድም ሆዳሙን አልታዘዝም እንዲሉት አንድም ዓይኑን ገልጦ መልካሙን እንዲያይ እንዲያደርጉት ማስቻል ይገባናል ሲሉ ይመክራሉ።
በእርግጥ ትውልዱን ለማቅናት ብዙ ትግል ይፈልጋል።ዝም ብሎ ላቃናው የሚባል ዓይነት አይደለም።ምክንያቱም ሊሰበር ይችላል።እናም ቢያንስ ቀጣዩ ልጆቹ እንዲተርፉ አቅጣጫ ማሳየትና መልካም ባህሎቻችንን ማስለመዱ ተገቢ ነው።‹‹ቤተሰብ ማታ የሚያወራውን ልጅ በጨዋታው ይተገብረዋል›› እንዲል ኦሮሞ ልጆች ፊት የሚወሩ ወሬዎች የተወሰኑ ሊሆኑ ይገባቸዋል ይላሉ።መልካምና አገር ወዳድነትን የሚያሳዩ፤ መረዳዳትን በአጠቃላይ መልካም እሴት የምንላቸውን የሚያዳብሩ ሊሆኑ ግድ ነው።ምክንያቱም ቤት ላይ ሲሰራ አገርን መገንባት ስለሚቻል ይላሉ።
ገጠመኝ
በልጅነታቸው ነበር ይህ የሆነው።አካባቢያቸው በሱማሌ ሽፍታ ተወረረ።በወቅቱ እናቶችና ሕፃናት ይህንንመቋቋም ስለማይችሉና አደጋ ይደርስባቸዋል ተብሎ ስለታሰበ ከአካባቢው እንዲሰወሩ ለማድረግ የተለያዩ አማራጮች ይፈለጉ ጀመር።አንደኛው አማራጭ በፒካፕ መኪና እነርሱን ጭኖ መውሰድ ነበር።ይህንን የሚያደርገው ደግሞ ጎረቤታቸው ሲሆን፤ የመኪናውም ባለቤትም ነበሩ።
ቤተሰቡን መጀመሪያ ሙሉ ለሙሉ አስገባ።ከዚያ ከጎረቤት የሚቀርበውን ሰው ጫነ። በመካከል እርሳቸው ሳይታዩ ሹልክ ብለው ገብተው መኪና ውስጥ ተሸሸጉ።ሰውዬ ሁሉም መግባታቸውን ለማየት በዓይኑ ሲቃኝ አቶ ኤልያስን ተመለከታቸው።ከዚያም ከሰዎች ውስጥ ነጥሎ ‹‹አንተ ውርጋጥ ማን ግባ አለህ፤ በል ቶሎ ውረድ›› ብሎ መንጭቆ ከመኪናው ላይ አስወረዳቸው።በወቅቱ የልጅነት አዕምሮ ስለነበር ወዲያው የሚገደሉ ነበር የመሰላቸው።አለቀሱ፤ ጮሁ፤ እንዲወስዳቸው ተማጸኑ ግን ሰሚ አልነበራቸውም።የሆነው ሆኖ ጊዜው አለፈና ከሰውዬው ጋር ቦታ ተቀያየሩ።እርሳቸው የኦሮሚያ የኢኮኖሚ ዘርፍ ሥራ አስፈጻሚ ሆነው በአጃቢ ይንቀሳቀሳሉ።እርሱ ደግሞ ደህይቶ ከሞያሌ በፌስቴል የተለያዩ ቅባቶችን ከኮንትሮባንድ እየተቀበለ ወደ ትውልድ ስፍራቸው እየወሰደ ነበር የሚሸጠው።እናም አንድ ቀን መንገድ ላይ በኩሩቱ ፌስታል ዕቃ ይዞ መኪና ሲጠብቅ አገኙት።
ለይተውት ነበርና ፊት እንዲገባ አደረጉት።ለሹፌራቸው ከየት እንደሚመጡ ጠይቆ ስለእርሳቸው ማውራት ጀመረ።ያሳደጋቸው እንደሆነ፤ ምን ምን እንዳደረገላቸው መጥፎውን ሸሽጎ ማውራቱን አጧጧፈው።መንገዳቸው አለቀናም መውረጃው ደረሰ።አመስግኖ ሊሄድ ሲል ግን እርሳቸው ወርደው ሰላምታ አቀረቡለት።አጃቢዎቻቸው አብረዋቸው ወርደው ስለነበርም ደነገጠ።አረጋጉትና ለምን እንደጫኑት ነገሩት።ቀደም ሲል በልጅነታቸው ያደረገውን እንደማይረሱትና ሌሎች ሰዎች ላይም እንዲህ ዓይነት ተግባር መፈጸም እንደማይገባው መከሩትና መልካም ሥራ ብለው ተለዩት።
ቤተሰብ
እናትም አባትም ሆነው ልጆቻቸውን ካሳደጉ መካከል የሚጠቀሱ ጠንካራ አባት ናቸው።ባለቤታቸው በ1993ዓ.ም በሕይወት ስትለያቸው እርሳቸው ቤቱን የመምራት ድርብርብ ኃላፊነት ነበረባቸው።የልጆቻቸውን ጸጉርና ገላቸውን ሳይቀር እያጠቡ አሳድገዋቸዋል።የማስጠናቱም ሆነ የመቆጣቱ ኃላፊነት የእርሳቸው ነበር።የቤት አስቤዛም እንዲሁ እርሳቸው መግዛት አለባቸው።እናም ይህንን ሁሉ እያደረጉ ሁለት ዓመታትን አሳልፈዋል።
‹‹አንዳንዴ ሳይደግስ አይጣላ የሚባለው አባባል አለ።እናት እንደሌለውና በወንድ ያደገ ልጅ እንደመሆናቸው ልጆቼ ጋጠወጦች አልሆኑብኝም።እንዲያውም በተቃራኒው ጎረቤት የሚያመሰግናቸው፣ ታዛዥና የተባሉትን የሚያደርጉ እንዲሁም ባህላቸውን የሚያከብሩና ለአገራቸው ትልቅ ክብር ያላቸው ሆነው ወጥተዋል።በዚህም ከእኔ በተሻለ ለባህሉ ተገዢ፣ የአካባቢው ሰው የሚላቸውን የሚሰሙ ስለሆኑልኝ አመሰግናቸዋለሁ።ላደረገልኝ አምላክም ምስጋና ይድረሰው›› ይላሉ።
እናት ኖራ አባት ቢሞት ብዙ የሚሰበሰቡ ነገሮች እንደሚኖሩ በእነርሱ እንዳዩ የሚናገሩት አቶ ኤልያስ፤ ልጆች የተሻለ የሚባለውን ሁሉ ከእናት ማግኘት ይችላሉ።ወንድ ልጅ ግን ብዙ ነገሮች ይበተኑበታል።ተደጋጋሚና የማይመለሱ ጥያቄዎች እንኳን ሲቀርቡለት እንዴት መመለስ እንዳለበት አይረዳም።በዚህም ልጆቹን ለተለየ ችግር ሊያጋልጣቸው ይችላል።እርሳቸው ግን እግዚአብሔር ረድቷቸው ይህ እንዳላጋጠማቸው ይናገራሉ።
አቶ ኤልያስ እናት አስተዳደግም ሆነ ወጪዎችን በአግባቡ የመመጠን አቅሙ አላት ይላሉ። በእርሷ የለመድኩትን ለሠራተኛ ሳደርግ በእጅጉ ይለያያል።በተለይ የቤት ውስጥ ወጪ ለወር የሚበቃው በሳምንት ያልቅ ነበር።እናም በቀላሉ የምቋቋመው አልነበረም።አንዳንዴ እንዲያውም ምን አለ እኔ ሞቼ እርሷ ብትቆይላቸው የሚሉበት ጊዜ እንደነበር ያስታውሳሉ።ከዚያ ግን ብዙ ነገሮች ሲመሯቸው የዛሬዋን ባለቤታቸውንና ልጆቻቸውን እንደወላድ ሆና ያሳደገችላቸውን አገቡ።
ዛሬ ባለቤታቸው ባይወልዱም ልጅ የሚሆኗቸውን የባላቸውን ልጆች ስላሳደጉ እማዬ ተብለው ተከብረውና ተወደው ይኖራሉ።ልዩ እንክብካቤም ይደረግላቸዋል።ስምንቱ ልጆችና 11 የልጅ ልጆች በእኩል ደረጃ ልክ እንደአባታቸውና አያታቸው ሳያዩዋቸው መዋልን አይወዱም።የራሳቸውን ኑሮ እየመሩ ቢሆንም አባታቸውን በሚናፍቁት ልክ እርሳቸውንም ለማየት ይጓጓሉ።
እንግዳችን በሕይወታቸው ከሚያስደስታቸው ሁሉ የመጀመሪያ ቦታ የሚሰጡት ከልጆቻቸው ጋር የሚያሳልፉትን ጊዜ ነው።እነርሱም ቢሆኑ ሳያዩዋቸው መዋል አይሆንላቸውምና ልዩ ጊዜያቸው ለአባታቸው የሚሰጡት ነው።ይሄ ጊዜ የኮሮና ቫይረስ በሀገራችን የተስፋፋበት ሆነና ብዙ ነገራቸው ተገደበ እንጂ።ይህም ቢሆን ግን በስልክ ሳይገናኙ አያድሩም።ባስ ካለባቸው ደግሞ ቤት በመምጣት ራቅ ብለው በመቀመጥ አውርተዋቸው እንደሚመለሱ አጫውተውናል።ብቻቸውን መሆንን ያልለመዱት እንግዳችን አሁንም ቢሆን እናት አባት የሞተባቸው ሁለት ልጆችን ከገጠር አምጥተው እያስተማሩ ይገኛሉ።በቤት ውስጥ ደስታ የሞላውም በዚህ ምክንያት እንደሆነ ይናገራሉ።
መልዕክት
እንደ እንግዳችን አመለካከት፤ አሁን ያለው ትውልድ በሳልና መስመር ካሳዩት አገርን ወደ ብልጽግና ጎዳና ይመራል። አሁን እየተደረገ ያለው አፈንጋጭ እንቅስቃሴ መቆም አለበት። የአበል ተከፋይ ሽማግሌና የሃይማኖት አባቶች በአገራችን ውስጥ ሊኖሩ አይገባም። የሃይማኖት መሪዎችም ሆኑ የአገር ሽማግሌዎች ለሚያመልኩት አምላክ፤ ለእምነታቸውና ለመረጣቸው ሕዝብ ሲሉ ለአላማቸው መስራት ይጠበቅባቸዋል። መንግሥትም ቢሆን የትኛው ሰው ሕዝብ ያምነዋል፤ ይወደዋል የሚለውን አብጠርጥሮ ማውጣት አለበት።ለይምሰል እየሰበሰበ ለሪፖርትና ለአበል ወጪ ከተጠቀመበት አደጋው የከፋ ነው።ስለሆነም ሰው ፊት መቅረብ የማይችለውን ሰው ሰብስቦ ማማከሩን ሊገታ ይገባዋል።
ስለሁኔታው በጥልቀት ሲያብራሩም በአካባቢያችን ሽማግሌዎች በሁለት ተከፍለዋል።አንዱ ንጹህ ሲሆን አንዱ ሌባ ነው።ሌባው የስኳር ሽማግሌ የሚባለው ነው።ስኳር ተረክበው ለማህበረሰቡ የሚያከፋፍሉ ሲሆኑ፤ እነርሱ ለጠቀማቸው ብቻ የሚያደርጉና ወረቀት ሳይቀር በኪሎ የሚሸጡ ናቸው።እናም እነዚህን ሽማግሌዎች ችግር ይፈታሉ ብሎ ማማከር አገር ከመግደል አይተናነስምና ሁሉም የተሸሸጉትን አገር አዳኝ ሽማግሌዎችን ማምጣትና እንዲሰሩ ማድረግ ላይ ሊረባረብ ይገባል ይላሉ።
መከላከያ ሠራዊትና ጠመንጃ የያዘ ብቻ አይደለም ሰላምን የሚያመጣው።ሕዝቡ ለሰላም ዘብ ቆሞ አገሩን ማስከበር ይችላል።አሁን ድረስ በጥባጮችን እንቢ ብሎ ማንበርከክ የቻለውም ለዚህ ነው።ስለዚህም ይህንን ተግባሩን ሊያስቀጥል ይገባል።በተመሳሳይ የተጎዱትን መርዳት የመንግሥት ድርሻ ብቻ እንዳልሆነ በማሰብ እጅን መዘርጋት የሁልጊዜ ተግባራችን መሆን አለበት ሲሉም መክረዋል።
ሁኔታውን በምሳሌ እንደሚከተለው ያስቀምጣሉ። ህወሀት 27 ዓመታትን ሲገዛ ለትግራይ ሕዝብ ያደረገው ልዩ ተግባር አልነበረም።በደም ለተጋቡት ብቻ ነበርም የጠቀመው።እናም የትግራይ ሕዝብም ዛሬ አለሁልህ ቢለው የቀደመውን ተግባሩን በማየት ከወዳጆቹ እንዳይለየው መጠንቀቅ ይገባዋል።በተናጠል መጓዝ ውበታችንን ያጠፋዋል።እኛ የምናምረው ብሔሮች ብሔረሰቦች ሳንነጣጠል በልዩነታችን ውስጥ አንድነታችንን ስናሳይ ነው።ስለሆነም ማንም ሊሸሽ አይገባውም፤ ወንጀለኛም ቢሆን ብሔር ሳይለይ በሰራው ልክ ከሕግ የሚያመልጥበት ሁኔታ የለምና ይህንን አውቆ መንቀሳቀስ ለነገ ብሩህ ተስፋችን ያበቃናል በማለትም ይመክራሉ።መንግሥት ‹‹መንግሥት መንግሥት›› መሽተት አለበት።ለዚህ ደግሞ አሁን የታሰሩትን ወንጀለኞችን ለይቶ በተገቢው መልኩ መቅጣትና ማስተማሪያ ማድረግ አለበት ብለዋል።
ከጎረቤት ጋር በፍቅር መኖርንና ይቅር መባባልን ልምድ እናድርግ የሚል ጠንካራ መልዕክትም ያስተላልፋሉ።አገራችን ታሪክ ያላት መሆኗን ተረድተን ታሪኳን እንዳናበላሽና የነገ ተከሻሾች እንዳንሆን እንጠንቀቅ የሚለው የማሳረጊያ መልዕክታቸው ነው።ሰላም!
አዲስ ዘመን ሐምሌ 19 ቀን 2012 ዓ.ም
በጽጌረዳ ጫንያለው