የኮሮና ቫይረስ አይረሴ የሕይወት ታሪኮችን በደማቁ አስፅፏል። እናትና ልጅን፣ እህትና ወንድምን፣ ባልና ሚስትን በህመም ጊዜ እንዳይጠያየቁ አድርጓል። በሌላ ህመም የታመሙ ሰዎች እንኳን ሆስፒታል ውስጥ ተኝተው ቤተሰብ እንዳይጠይቃቸው ተደርጓል። የሕግ ታራሚዎች ከጠያቂ ተለያይተዋል። የቫይረሱ ተጠቂዎችም ሙሉ በሙሉ አገግመው እስከሚወጡ ድረስ ከሰው ሳይገናኙ ሳምንታትንና ወራትን የብቻ ሕይወት ኖረዋል። ሕፃናት ልጆች ከእናትና አባታቸው ተለይተው፤ ቤት ተዘግቶባቸው መራር ሕይወትን አሳልፈዋል። ገና ከእናት ጉርሻ ያልወጡ ታዳጊ ልጆች የኤሌክትሪክ ምድጃ ለኩሰው ምግብ ለማዘጋጀት ተገድደዋል። በአውሮፓና አሜሪካ አገራት እንዲህ ዓይነት የሕይወት ምስቅልቅሎች ተመዝግበዋል።
በኢትዮጵያ ያለው ከውጭው ዓለም ጋር ሲነፃፀር ያን ያህል አስከፊ ነው ባይባልም ብዙ የማህበራዊ ለውጦች ታይተዋል። ቀብር ላይ ወዳጅ ዘመድ አልተገኘም። ሠርግ ላይ ዘመድ አዝማድ አልተጠራም። ሰሞኑን በማህበራዊ የትስስር ገጾች ሲዘዋወሩ ከነበሩት አንዱ ‹‹የምትወዱን ከሆነ ሠርጋችን ላይ አትምጡ›› ያሉት ሙሽሮች ጉዳይ ነበር። ነገሮች እንዲህ ተገለባብጠዋል። ‹‹የምትወዱኝ ከሆነ ሠርጌን እንዳትቀሩ›› ይባል የነበረው በ‹‹እንዳትመጡ›› ተተክቷል።
ይሄ ትልቅ አይረሴ ታሪክ ነው። እነዚህ ጥንዶች ዕድሜ ዘመናቸውን አይረሱትም። እንደሚታወቀው የሠርግ ሁነቶች ተሰንደው ይቀመጣሉ። እስከ እርጅና ድረስ ‹‹የሠርጌ ዕለት…›› እየተባለ ይወራል። በዚህ በኮሮና ዘመን የነበሩ ሠርጎች ግን መታወሻነታቸው ይሄ ሆኗል።
በሌላ በኩል ደግሞ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ሰብዓዊነትም የተፈተነበት ዘመን ሆኗል። ‹‹ሰው ማለት ሰው የሚሆን ነው ሰው የጠፋ ዕለት›› የሚለው አባባል መለኪያ ሆኗል። በዚህ ወቅት ሰብዓዊ ድጋፍ ያደረጉ ሰዎች ሕይወትን ነው የታደጉ። በዚህ ወቅት ሰብዓዊ ድጋፍ ማድረግ ከሌላው ጊዜ ይለያል። ለምሳሌ ከወላጆቻቸው ጋር ያልሆኑ ጎዳና ተዳዳሪዎችና የኔ ቢጤዎች በዚህ ወቅት የበለጠ ይጎዳሉ። ምክንያቱም ጎዳናዎች ሰው የላቸውም። እንደበፊቱ የኪሱን ጣል የሚያደርግ አይኖርም። እንኳን ጠቅልለው ‹‹ጎዳና ቤቴ›› ያሉት ይቅርና የቀን ሥራ የሚሰሩት እንኳን ተቸግረዋል።
የማህበራዊ መገናኛ ዘዴዎችን በመጠቀም እንዲህ ዓይነት በጎ ሥራ የሰራ አንድ ወጣት ሰሞኑን የአማራ ብዙኃን መገናኛ ድርጅት (አብመድ) አስተዋውቆ ነበር። እኛም አብመድን ዋቢ በማድረግ ጉዳዩን እናካፍላችሁ።
‹‹አቶ ተስፋሁን ደስታ ይባላል፤ በአዊ ብሔረሰብ አስተዳደር ጓጉሳ ሽኩዳድ ወረዳ ቲሊሊ ከተማ ነዋሪ ነው። ወጣቱ ማኅበራዊ የትስስር ገጽን በተለይ ፌስቡክን በመጠቀም በሀገር ውስጥ እና በውጭ ሀገር የሚገኙ የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎችን በማስተባበር የተቸገሩ የቲሊሊ ከተማ ነዋሪዎችን እንዲያግዙ ጥረት እያደረገና በሚያገኘው ድጋፍም ሌሎችን እያገዘ ይገኛል። በፌስቡክ ገጹም ሰፊ ቅስቀሳ አድርጎ ለተቸገሩ ሰዎች የባንክ የሒሳብ ደብተር በመክፈት ገንዘብ ማጠራቀም ችሏል።
በአቶ ተስፋሁን ደስታ እገዛ ከተደረገላቸው ሰዎች መካከል ሕፃን እሱባለው አዳነ አንዱ ነው። ሕፃን እሱባለው በሕፃንነቱ ጀምሮ በእናቱ ወይም በአባቱ እቅፍ የማደግ ዕድሉን አላገኘም። ይልቁንም በሕፃንነቱ ከተወለደበት አካባቢ ተነስቶ ወደባሕር ዳር በመሄድ የጎዳና ኑሮን እንደተጋፈጠ ነግሮናል። የተከሰተው የኮሮና ወረርሽኝ ደግሞ ለእርሱና መሰሎቹ የጎዳና ኑሮንም ነፍጓቸዋል። በዚህ የተነሳም ታዳጊው እሱባለው ወደ ትውልድ ቦታው ጓጉሳ ሽኩዳድ ቲሊሊ ከተማ መሄዱን ተናግሯል።
ቲሊሊ እንደገባም የሚበላውና የሚጠጣው እንዳልተቸገረ፣ ከኅብረተሰቡ ድጋፍ እንዳገኘ ተናግሯል። ሕይወቱን በዘላቂነት ለመምራት እንዲችልም ቅን አሳቢው አቶ ተስፋሁን ደስታ በማኅበራዊ ሚዲያ ከሰዎች ጋር በመነጋገር ገንዘብ አሰባስቦ የሊስትሮ ዕቃ በመግዛት ሥራ እንዲጀምር አድርጎታል። አሁን ላይ ታዳጊው እሱባለውም ‹‹በሥራው ደስተኛ ነኝ፤ ለትልቅ ቁምነገር ለመብቃት ጠንክሬ እሠራለሁ›› ብሏል። የባንክ ሒሳብ ቁጥር ከፍቶ በሁለት ሳምንት እስከ 220 ብር መቆጠብ እንደጀመረም ተናግሯል።
ወይዘሮ እመቤት ተሰማ ደግሞ ሌላኛዋ በአቶ ተስፋሁን ደስታ ማኅበራዊ የትስስር ገጽ በተሰበሰበ ድጋፍ ተጠቃሚ የሆኑ የቲሊሊ ነዋሪ ናቸው። ወይዘሮ እመቤት በመልሶ ማልማት ከድሮ ቤታቸው ሲነሱ ምትክ ቦታ ብቻ እንደተሰጣቸውና የገንዘብ ካሳ እንዳልተከፈላቸው ይናገራሉ። ምትክ የተሰጣቸውንም 200 ካሬ ሜትር የመኖሪያ ቤት መሥሪያ ቦታ ገንዘብ ባለማግኘታቸው ለሰባት ዓመታት ሳይሠሩት ቆይተዋል። ጧሪ የሌላቸው አዛውንት ለሰባት ዓመታት ፈታኝ ኑሮ ማሳለፋቸውን ያስታውሳሉ።
ከዚህ በፊት ወረዳ አስተዳደሩ ዝቅተኛ ነዋሪ መሆናቸውን በማረጋገጥ በወር 300 ብር ድጋፍ እያደረገላቸው ከዚህ ውስጥም 220 ብር ለቤት ኪራይ እየከፈሉ እንደነበር ነግረውናል። አሁን ግን አቶ ተስፋሁን ደስታ ከ35 ሺህ ብር በላይ ገንዘብ አሰባስቦ 33 ዚንጎ ቆርቆሮ ቤት፣ መጸዳጃ ቤት፣ የቧንቧ ውኃና ሌሎችም ለመኖር የሚያስፈልጉ ጉዳዮችን የተሟላ ቤት እንዳሠራላቸው ገልጸዋል። ‹‹ተስፋሁንን ከእጄ እና እግሬ አስበልጬ እወደዋለሁ፤ ጤና እና ዕድሜ ይስጠው›› ሲሉም ምሥጋና አቅርበዋል። ሌሎች ወጣቶችም መልካም ሥራን ከተስፋሁን መማር አለባቸው ብለዋል።
ቤት ለፈረሰባቸው እናት 15 ሺህ ብር በመሰብሰብ ቤታቸው እንዲጠገን፣ ፍራሽና ብርድ ልብስ፣ 150 ኪሎ ግራም በቆሎ ድጋፍ አድርጎላቸዋል። በከተማዋ በተለያየ ምክንያት ተጥለው የሚገኙ ሕፃናትን አንስተው ለሚያሳድጉ እናት ደግሞ 10 ሺህ ብር አሰባስቦ ለግሷል። ይህንን መልካም ሥራ እያከናወነ የሚገኘው ወጣት ተሰፋሁን ደስታ የማኅበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚዎች የማኅበራዊ ገጽ ትስስርን ለመልካም ሥራ እንዲጠቀሙበት መክሯል፤ ሌሎች ወጣቶችም አቅም ለሌላቸው ሰዎች እገዛ በማድረግ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ መልዕክት አስተላልፏል። በቀጣይም በቲሊሊ ከተማ ከሚገኙ ከምግባረ ሰናይ የወጣቶች ማኅበር ጋር በመቀናጀት ለተቸገሩ ዜጎች እገዛ እንደሚያደርግላቸው ተናግሯል››
እንዲህ ዓይነት በጎ አድራጊ እንዳለ ሁሉ በተቃራኒው ደግሞ አስከፊና አስነዋሪ ድርጊቶችም ታይተዋል። ባለፈው ሳምንት ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ስለቤት ውስጥ ጥቃት ተናግረው ነበር። ይሄ አስነዋሪ ድርጊት የተመዘገበው ደግሞ በአፍሪካ አገራት ውስጥ ነው። በነገራችን ላይ የሰለጠኑ በተባሉት የአውሮፓና የአሜሪካ አገራትም በወረርሽኙ ምክንያት ከፍተኛ የስርቆት ወንጀሎች ተመዝግበዋል። የቤት ውስጥ የሴቶች ጥቃት ግን ከስርቆትም በላይ አስነዋሪ ወንጀል ነው። የቢቢሲን ዘገባ ዋቢ በማድረግ በተለያዩ የአፍሪካ አገራት የተፈፀሙ ጥቃቶችን እንመልከት።
የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት መረጃ እንደሚያስረዳው የኮሮና ቫይረስ ስርጭትን ለመግታት ዜጎች ከቤት እንዳይወጡ መወሰኑን ተከትሎ የቤት ውስጥ ጥቃት ጨምሯል።
የበርካታ የአፍሪካ አገራት መንግሥታት፣ ፖሊስና የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች እንደገለጹት፣ ከቤት ያለመውጣት ሕግን ተከትሎ በርካቶች በፍቅር አጋራቸው አልያም በቤተሰብ አባላቸው ጥቃት ይደርስባቸዋል። ጥቃት ከሚደርስባቸው ሰዎች መካከል ደግሞ አብዛኛዎቹ ሴቶችና ሕፃናት ናቸው።
‹‹ጥቃት የሚፈጸምበት ዓይነት ግንኙነት ውስጥ ካላችሁ ምን እየሆነ እንዳለ መገንዘብ ይቻላል›› ትላለች ለብዙ ዓመታት በባለቤቷ አካላዊና ሥነልቦናዊ ጥቃት የደረሰባት ኤስተር። ‹‹የሳምንቱ መጨረሻ ቀናት ሁሌም አስቸጋሪ ነበሩ፤ ምክንያቱም ሁሉም ሰው ወደየቤቱ ይሰበሰባል። በቤት ውስጥ ሲውል ምንም የሚሰራው ነገር ስለሌለው ይደብረዋል። ሰበብ እየፈለገ እኔን ለማበሳጨትና የሆነ ነገር እንድናገር ወይም እንዳደርግ ይገፋፋኛል። ሁሌም መጨረሻው የቃላት ውርጅብኝና አንዳንዴም ዱላ ነበር። ልክ የታሰርኩ ያክል ነበር የሚሰማኝ፤ በሁለት ቀን ውስጥ የሰው ልጅ ይህንን ያህል ከደበረው ለወራት ቤት ውስጥ ሲቀመጥ ደግሞ ምን ሊፈጠር እንደሚችል መገመት ከባድ አይደለም›› ትላለች ኤስተር።
የእንቅስቃሴ ገደብ በተጣለበት በዚህ ወቅት ደግሞ ሴቶች አጋሮቻቸውን ጥለው እንዳይሄዱ እንኳን ሕግ ጣሳችሁ ተብለው በፖሊስ ቁጥጥር ስር ይውላሉ። እንደምንም እሱን ቢያመልጡ እንኳን ወደፈለጉበት የሚሄዱበት የሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት የለም።
በርካታ አገራት ይህንን ከግምት ውስጥ በማስገባት በቤት ውስጥ ጥቃት ለሚደርስባቸው አገልግሎት የሚሰጥ ነፃ የስልክ መስመር አዘጋጅተዋል። መስመሩ ሁሌም ቢሆን እንደሚጨናነቅ ነው የሚነገረው።
በደቡብ አፍሪካ በመጀመሪያዎቹ የእንቅስቃሴ ገደብ በተጣለባቸው ሳምንታት ብቻ ፖሊስ 2 ሺህ 320 ጾታዊ ጥቃቶች እንደመዘገበ ገልጿል። ይህ ደግሞ ከሌላ ጊዜው (ወረርሽኙ ከሌለበት) 37 በመቶ ጭማሪ አሳይቷል።
በዚምባብዌ ደግሞ የጥቃቶች ቁጥር በሦስት እጥፍ የጨመረ ሲሆን በናይጄሪያም ቢሆን ከሌላ ጊዜው ከፍ ያለ ጥቃት ተመዝግቧል።
አንዳንድ የአፍሪካ አገራት ሴቶችን በዚህ ወቅት ለመርዳት በማሰብ የተለያዩ አማራጮችን እየወሰዱ ነው። ለምሳሌ ቱኒዚያ በዚህ ጊዜ ጥቃት ለሚደርባቸው ሴቶችና ሕፃናት ማረፊያ የሚሆኑ ስምንት መጠለያዎችን አዘጋጅታለች፤ በሌሎች አገራትም ተመሳሳይ መጠለያዎች ተዘጋጅተው በጎ ፈቃደኞች ጭምር እየተሳተፉ ይገኛሉ።
በዚምባብዌ የሚገኘው መጠለያ በአሁኑ ጊዜ (ዘገባው የተሰራው ግንቦት 2 ቀን ነው) 21 አዋቂ ሴቶችና ሰባት ሕፃናትን ተቀብሎ እያስተናገደ ይገኛል። የማዕከሉ ዳይሬክተር ቢየትሪስ ሳቫድዬ እንደሚሉት ሴቶቹና ሕፃናቱ አንዳንዶቹ ከቤታቸው ጠፍተው የመጡና በፖሊስ ጥቆማም የተገኙ ናቸው።
በኬንያ የምትገኛዋ የማህበራዊ አገልግሎት ሠራተኛ ዳያና ካማንዴ እንደምትለው ደግሞ እሷ የምትሰራበት ድርጅት 17 ሴቶችን ተቀብሎ በዋና ከተማዋ ናይሮቢ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል።
በናይጄሪያ ጥቃት የሚፈጸምባቸውን ሴቶች ከቤታቸው ለማስወጣት በጎ ፈቃደኞችም ጭምር በመሳተፍ ትብብር እያደረጉ ነው። በአንዳንድ አጋጣሚዎች ሴቶቹን ከአጋሮቻቸው ለማስመለጥ ቤተ ዘመድም ጭምር ይሳተፋል ተብሏል።
በጋና ያለው መጠለያ ደግሞ ከዚህ በኋላ ጥቃት የሚደርስባቸውን ሴቶች ለመቀበል እየተቸገርኩ ነው ብሏል። ምክንያቱም በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ በመምጣቱና የለይቶ ማቆያዎች በመሙላታቸው ነው።
ኤስተር በዚህ ማዕከል ውስጥ ጥቃት ለሚደርስባቸው ሰዎች በተቋቋመው የጥሪ መስመር ላይ አገልግሎት በመስጠት ላይ ትገኛለች።
‹‹የሰብአዊ መብት ተሟጋቾችን በማህበራዊ ሚዲያ በኩል ለማግኘት ጥረት አድርጉ፤ ደውሉላቸውና ያላችሁበትን ሁኔታ አስረዷቸው። ሊረዳችሁ ከሚችል ማንኛውም ሰው ጋር ከመደወል ወደኋላ አትበሉ›› በማለት ምክሯን ለግሳለች።
እነዚህ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ክስተቶች መጥፎዎችም በመጥፎነታቸው፤ በጎዎችም በበጎነታቸው ታሪክ ሆነው ይቀመጣሉ። ከቫይረሱ አስከፊነት በላይ የሰዎች ጭካኝነት ታሪክ እንዳይሆን በጎ በጎውን እንስራ።
አዲስ ዘመን ግንቦት 8/2012
ዋለልኝ አየለ