ታሪኩን፣ ባህሉንና አገራዊ እሴቶቹን የማያውቅ፣ አውቆም ለህብረተሰብ ዕድገት የማይጠቀምበት ቢኖር እርሱ ዕውቀትና ታሪክ ጠል ዜጋ ለመሆኑ ከድርጊቱ በላይ ማረጋገጫ ሊኖር አይችልም፡፡ ኢትዮጵያ በየማህበረሰቡ የሚከወኑ ቀደምት የሥነ-ፅሑፍ ፣የኪነ-ሕንፃ፣የሙዚቃ፣የሽምግልናና እርቅ፣ እንዲሁም ሌሎች ባህላዊ እሴቶችና ትውፊቶች መገኛ ነች። ለዚህም ይመስላል ሀገሪቱ በታሪክና በባህል ተመራማሪዎች ዘንድ « የባህል ሙዚየም» የምትባለው።
ኢትዮጵያ በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት የሳይንስና የባህል ድርጅት (UNESCO) የተመዘገቡ በርካታ የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ ተፈጥሯዊና ባህላዊ ቅርሶች ባለቤትም ነች። በኢትዮጵያ በብዙ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች የሚከናወኑ የማህበራዊ ፣የኢኮኖሚያዊና የፖለቲካዊ አስተዳደር፣ የሥነ-ምግባር፣የስነ-ልቡና፣የቋንቋ፣የታሪክ፣የስነ-ቃል፣የምግብ አዘገጃጀት፣የአመጋገብ ስርዓት ፣ቤት አሠራር፣ አልባሳት ፣ጌጣጌጦች፣ባህላዊ እምነቶች፣ ሃይማኖቶችና ሌሎችም እሴቶች የህዝቦች የባህል አካል ተደርገው ይወሰዳሉ።
ይህ የባህል ዓውድ ከወሊድ፣ ከጋብቻና ከሞት ጋር የተያያዙ ስነ ስርዓቶችና ጉርብትናን የመሳሰሉ ማህበራዊ የትብብር መርሆዎች ፣ባህላዊ የጤና አጠባበቅ ዘዴዎች፣የማህበረሰብ አስተዳደሮችና ሌሎች የማህበረሰብ ገፅታዎችንም ያጠቃልላል።
የባህል ዓውዱ ቃላዊ ሀብትን፣እደጥበብን፣ኪነ-ሕንፃን፣ አልባሳትን፣ምግብና መጠጥን በማካተት ቁሳዊ የባህል ዘርፍ፤ ሙዚቃን፣ ውዝዋዜንና ድራማዎችን ሲያካትት ሀገራዊ ክዋኔ ዘርፍ፤ ክብረ በዓላትንና የህይወት ዑደትን የሚያካትተው ሀገረሰባዊ ልማድ ዘርፍ፤ የቁጥሮችን፣ የቀለሞችንና የምልክቶችን ትርጓሜና አንድምታ ሲይዝ ማህበረሰባዊ ውክልና ዘርፍ፤ እንዲሁም የእርቅ ፣የአውጫጭኝና የገዳ ስርዓቶችን በስሩ ሲያጠቃልል ደግሞ ማህበረ ፖለቲካዊ ባህሎች ዘርፍ፤ በሚል በስድስት ዋና ዋና ክፍሎች ተመድቦ የሚገኝ ነው።
ይህንን ዘርፍ ለማበረታታትና ለመደገፍ ሀገራት የባህል ፖሊሲ ቀርፀው በሥራ ላይ አውለው ውጤታማ ሆነዋል። ይህ ፖሊሲያቸው የአንድን ሀገር የኪነ ጥበብ ሥራዎችና በባህል ውስጥ ያሉና ከፈጠራ ውጤቶች ጋር የተያያዙ እንቅስቃሴዎችን ለመቆጣጠር፣ ለመጠበቅ፣ ለማበረታት፣ በገንዘብም ሆነ በሃሳብ ለመደገፍ ረድቷቸዋል።
በአገራችንም ስለ ቅርስ ጥናትና አጠባበቅ የሚደነግግ አዋጅ ቁጥር 209/1992 ማውጣቷ ይታወሳል፡፡ ይህንን አዋጅ ተከትሎም የኢትዮጵያ የባህል ፖሊሲ ከታኅ 2008 ዓ.ም ጀምሮ ማሻሻያ እንደተደረገበት ይታወቃል። ይሁን እንጂ ኢትዮጵያውያን የራሳቸው ታሪክና ባህል ያላቸው ብዙ ብሄር ብሄረሰቦችና ሕዝቦች የሚገኙባት፣ ሕዝቦቿም ባሳለፉት የረጅም ዘመን ታሪክ በዓለም የባህል ቅርስነት የተመዘገቡትን ጨምሮ የበርካታ ቅርሶች ባለቤት መሆን ቢችሉም፤ ተተኪው ትውልድ ስለ ማንነቱ መገለጫ ለሆነው ታሪኩና ባህሉ በሚፈለገው መጠን ጥልቅና ሰፊ ግንዛቤ ለማስጨበጥ በጥንካሬ ባለመሠራቱ በተለይ ከወጣት እስከ ጎልማሳ ያለው የህብረተሰብ ክፍል ባህላዊ ማንነቱን እንዳይጎናፀፍ አድርጎታል፡፡
ኢትዮጵያ ያላት የሚዳሰሱትም ይሁኑ የማይዳሰሱት የቅርስ ሀብቶች አገሪቱ ካላት የኢኮኖሚ አቅም በላይ የገዘፉ መሆኑ ይታወቃል፡፡ እነዚህ ሀብቶች ለቱሪዝም አገልግሎት ብቻ ሳይሆን ለመልካም ማህበረሰብ ግንባታ ሥራ የጀርባ አጥንት መሆናቸው የሚያጠያይቅ አይሆንም፡፡
ከማይዳሰሱት ታላላቅ ማህበረሰባዊ እሴቶቻችን መካከል አንዱ የገዳ ስርዓት ዴሞክራሲ እንደአሁኑ ታዋቂ ባልሆነበት ዘመን ማኅበረሰቡ አምኖበት ሲጠቀምበት ዓመታት ማስቆጠሩ ለራሳችን «በእጅ የያዙት ወርቅ…» አደረግነው እንጂ ዓለምን ያስደመመ ነው፡፡
የክልል መንግሥታት የብሄር ብሄረሰቦችን ባህላዊና ታሪካዊ እሴቶች ለማሰባሰብ፣ ጠብቆ ለማቆየትና ሳይበረዙ ለትውልድ ለማስተላለፍ ዓይነተኛ መሳሪያ መሆናቸው ቢታወቅም የባህል ማዕከላት የሰጡት ትኩረት አነስተኛ በመሆኑ ከውጤታማነት ይልቅ የባህል ዝንጋታን አስከትሎ በመጤ ባህል እየተተካ ይገኛል፡፡
በአንድ ወቅት የአዲስ አበባ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ በሀገሪቱ በተለያዩ አካባቢዎች መጤ ባህሎችና ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች በከፍተኛ ፍጥነት እየተስፋፉ መሆኑን በጥናት ግኝቱ አመላክቶ ነበር። ጥናቱ በዘጠኙ ክልሎችና በሁለቱ የከተማ አስተዳደሮች ናሙናዎችን በመውሰድ የተካሄደ ሲሆን፤ ግሎባላይዜሽንን ተከትሎ የሚገቡ መጤ ባህሎችና ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች በከፍተኛ ፍጥነት መስፋፋት ለትውልድ ስጋት እንደሆኑ ተጠቅሷል፡፡ ሱስ አስያዥና አደንዛዥ እጾችን መጠቀም፣ የራቁት ዳንስ፣ ከተመሳሳይ ጾታ ጋር ወሲብ መፈጸም፣ በማሳጅ ቤቶች ወሲብ መፈጸም እየተስፋፉ ከመጡ መጤ ባህሎችና ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች መካከል ተጠቃሽ ሆነዋል።
የወጣቱ ትውልድ ከድረ ገጾች የወሲብ ፊልሞችን መመልከትና ያልተገቡ አለባበሶችን መኮረጅ እየተስፋፉ መሆኑ በተለይም «ፍሪ ዞን፣ ፍሪ ሳተርዴይ እና ኖ ሼም ግሩፕ» በሚል ወጣቶች በቡድን የሚፈፅሟቸው መጤ እና ጎጂ ልማዶች በአዲስ አበባና በአንዳንድ ክልሎች በስፋት እንደሚስተዋሉ በጥናቱ ተመላክቷል።
እነዚህ የባህል መዘንጋቶች፣ መጤ ባህሎችና ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች መስፋፋት ማህበረሰባዊ ክስረትን ከማድረስ አልፈው ለአገሪቱ ዕድገት እንቅፋት እንደሚሆኑ ይታመናል፡፡ የኢኮኖሚ ዕድገትና ባህል ጥበቃ ተደጋግፈው ካልሄዱ የህዝቡን መልካም እሴቶችና ባህል የሚያጠፋ፣ የታላላቆቹን ምክር የማይቀበል ፣ የታሪክን ምንነት የማይረዳ፣ ታሪክን ለማወቅ የማይፈልግ፣ መላው አካሉን ለመጤ ባህል ያስገዛ ትውልድ በማፍራት ለአገር የማይጠቅም ትውልድ ታቅፎ ለመቀመጥ የምንገደድ ስለሚሆን፤ ይህ የትውልድ ጠንቅ ስር ሳይሰድድ ተረባርበን ልናስወግደው ይገባል፡፡ ለዚህ ደግሞ ያሉንን መልካም ባህላዊ እሴቶችን ትውልዱ እንዲያውቃቸው መሥራት የግድ ይላል፡፡
አዲስ ዘመን ጥር 3/2011