ለአንድ አገር የኢኮኖሚ ድቀት እንዲሁም ፖለቲካዊ አለመረጋጋት መንስኤ ሆነው ከሚነሱ ችግሮች መካከል አንዱ ሙስና ነው። ኢትዮጵያም ለዚህ ችግር ትኩረት ሰጥታ የጸረ ሙስና ትግሏን ከጀመረች ዓመታት ተቆጥረዋል። በእነዚህ ጊዜያት በሥነ ምግባርና ጸረ ሙስና ኮሚሽኗ አማካይነት በርካታ ሥራዎችን መስራቷ ይነገራል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ኮሚሽኑ ከመክሰስ። ከመቅጣትና ከማሰር ወደ ማስተማርና ግንዛቤን ወደማሳደግ ገብቷል። በእዚህ ሥራውም ምን ያህል ውጤታማ ሆኗል? የሚቀሩት ተግባራትስ ምንድን ናቸው? ተቋሙ መሆን ያለበት ደረጃ ላይ ደርሷል ወይ? ስንል ለፌዴራል ሥነ ምግባርና ጸረ- ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር አየልኝ ሙሉዓለም ጥያቄዎችን አቅርበናል።
አዲስ ዘመን፦ ተቋሙ ያለበት ደረጃ ምን ይመስላል?
ኮሚሽነር አየልኝ፦ ተቋሙ ሦስት ተልዕኮዎች አሉት። አንደኛው ኅብረተሰቡ ሙስናን የሚሸከም እንዳይሆን የማስተማርና ግንዛቤ የመፍጠር ፣ ሙስና ተፈጽሞ በሚገኝበት ጊዜ ለማጋለጥ የሚያስችል ምቹ ሁኔታን መፍጠርና የአሠራር ሥርዓት ጥናት ማጥናት ሲሆኑ ተቋማትን የማማከርና በዚህ መካከል ደግሞ የምናገኛቸውን ለሙስና በር የሚከፍቱ ቀዳዳዎች ለመድፈን የሚያስችል ሥራ እንሰራለን።
ከሁሉም በላይ ግን አሁን ተቋሙ የመንግሥት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ያፈሯቸውን ንብረቶች እንዲያሳውቁና እንዲያስመዘግቡ የማድረግ ሥራ ይሰራል። ይህንን በማድረግም ግልጽነትና ተጠያቂነት ለማስፈን ይጥራል።
የሙስና ትግል በአንድ ተቋም ብቻ የሚሰራ ሥራ ስላይደለ ሕዝቡን ለማስተባበርና በተለያየ አደረጃጀት ለማንቀሳቀስ የመንግሥት ተቋማትም የሙስና ትግልን በውስጣቸው ለማስፋት የሚያስችላቸውን ሥራ እንዲሰሩ የማስተባበርና የማቀናጀት ሥራም አንዱ ተልዕኮው ነው።
ከዚህ አንጻር የተቻለንን ያህል ጥረት እያደረግን ቢሆንም አሁን በአገር ደረጃ ያለው ያልተረጋጋ ሁኔታ ተቋማትም ላይ ተጽዕኖ የሚያሳድር በመሆኑ የማስተባበር ሥራውን በተሟላ ሁኔታ ለማስፈጸም ውስንነቶች እያጋጠሙ ነው።
አዲስ ዘመን፦ በማስተማርና በግንዛቤ ፈጠራ እንዲሁም በማማከር በኩል ምን ያህል ውጤታማ ሆኗል ማለት እንችላለን?
ኮሚሽነር አየልኝ፦ ተቋሙ የሚችለውን ያህል ጥረት እያደረገ ነው፤ ይህ ማለት ግን በሚሰራው ሥራ ኅብረተሰቡን አርክቷል። አመኔታን የሚያሳድር ሆኗል ለማለት አይቻልም፤ ምክንያቱም በጣም ብዙ የሚቀሩት ተግባራት ስላሉ፣ በመሆኑም የተቋሙን ቁመና የበለጠ ለማጠናከርና በሕዝቡ ዘንድም ተቀባይነት ለማግኘት እንዲቻል አሁን ያለውን የለውጥ አጋጣሚ በመጠቀም የማቋቋሚያ አዋጃችንን እያሻሻልን ነው፤ የከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች የሥነ ምግባር ኮድ አርቅቀን ወደ ሚመለከተው ክፍል አቅርበናል፤ አጠቃላይ አገራዊ የሆነ የጸረ ሙስና ፖሊሲና ስትራቴጂ እንዲኖረንም በመስራት ላይ ነን። አገራዊውን የሙስና ደረጃ ለማወቅ የሚያስችል ጥናትም በዚህ ዓመት ተጀምሮ እየተሰራ ይገኛል።
አዲስ ዘመን፦ በሕዝቡ ዘንድ አመኔታን ለማጣቱና እርካታን ላለመጨመሩ በዋናነት የሚነሱ ምክንያቶች ምንድን ናቸው?
ኮሚሽነር አየልኝ፦ አንዱ ተቋሙ በራሱ የአቅም ውስንነት ያለበት መሆኑ ነው። ብቃት ያለው የሰው ኃይል ችግር ደግሞ ሌላው ማነቆው ነው። ለሥልጠና የምናገኛቸው ሰዎች ትልልቅና ከፍተኛ የመንግሥት ተቋማትን የሚመሩ ኃላፊዎች፣ ዳይሬክተሮች፣ የሃይማኖት አባቶች ከመሆናቸው አንጻር እነሱን ለማሰልጠን ብቁ የሆነ የሥልጠና ባለሙያ አለመኖር ይጠቀሳሉ።
በሌላ በኩልም ኅብረተሰቡ የሙስናን ችግር ተቋሙ በመቋቋሙ ብቻ የሚያስወግደው ወይንም ደግሞ የሚከላከለው አድርጎ ስለወሰደ በየአካባቢው የሚፈጠሩ የሙስና ወንጀሎችን በሙሉ አላስወገደም አልተከላከለም ብሎ ብዙ ዓይነት ስሞታዎችና ቅሬታዎች መቅረባቸው እንደ ችግር እንወስዳቸዋለን።
የምንሰራቸው የአሠራር ሥርዓት ጥናቶችም ቢሆኑ ብስለት የጎደላቸው ከመሆናቸውም ባለፈ እነሱን ወስደው ተግባራዊ ያደረጉ ተቋማት ምን ያህል በምክሩ ወይም በአሠራር ሥርዓቱ ተጠቅመው ተለውጠዋል የሚለውን የምናይበት አግባብም ውስንነት ያለበት መሆኑ ሌላው ችግራችን ነው።
በአሁኑ ወቅት ተቋሙ ትኩረት ሰጥቶ የሚሰራው ማስተማር ላይ ነው፤ ኅብረተሰቡ ደግሞ እርምጃ ይፈልጋል፤ ብዙ ነገር ከሚነገረው ይልቅ አንድ ሙሰኛ ላይ እርምጃ ተወስዶ ማየት ያምረዋል፤ እኛ ደግሞ ጠቁም፣ ራስህ ታገል ፣አጋልጥ ሙስና ተፈጽሞ ስታገኝ ወደፖሊስና አቃቤ ሕግ ሂድ የሚል ማስተማር ስለሆነ የምንሰራው ከዚህ አንጻር ሲታይ ሥራው የሕዝቡን ፍላጎት የሚያረካ አይደለም። ይህ ደግሞ ተቀባይነቱንና ተዓማኒነቱን ዝቅተኛ አድርጎታል።
ኮሚሽኑ ባለፈው የሥልጣን ዘመኑ የመክሰስም ሆነ የመመርመርም ሥራ በእጁ የነበረው ቢሆንም ትልልቅ ባለሥልጣናትና የፕሮጀክት መሪዎች ላይ በወቅቱ እርምጃ መውሰድ አልቻለም። እንዲያውም የፖለቲካ ጥገኛ ነበር የሚል አስተሳሰብና አመለካከት በሕዝቡ ውስጥ መኖሩ አሁን ላይ አመኔታን እንዲያጣ አድርጎታል።
አዲስ ዘመን፦ ኮሚሽኑ በማስተማር ሥራው ኅብረተሰቡን ቀይሬያለሁ ብሎ ያስባል?
ኮሚሽነር አየልኝ፦ የማስተማር ሥራው ተደራሽ እንዲሆን ከፍተኛ ጥረት እያደረግን ነው። በዚህም የህትመትና የኤሌክትሮኒክስ መገናኛ ብዙኃንን እንጠቀማለን ። በተለይም ለወጣቶችና ሕፃናት ተደራሽ ለመሆን እንሞክራለን ። በሌላ በኩልም ከፍተኛ ትኩረት ሊያገኙ የሚገባቸው እንደ ገቢዎች ሚኒስቴር፣ ተደጋጋሚ የኦዲት ግኝት የሚገኝባቸው ተቋማት ፣ ከፍተኛ ሀብት የሚያንቀሳቅሱ ተቋማት ላይ ያሉ የግዢና ፋይናንስ ባለሙያዎችን ጨምሮ ከሌሎችም ጋር ፊት ለፊት የሙስና ጽንሰ ሀሳቦችንና ሙስናን እንዴት መከላከል እንደሚገባቸው ሕጎቹም ላይ ስህተት ፈጥረው ቢገኙ ምን ዓይነት እርምጃ ሊወሰድባቸው እንደሚችል በማስተማር በኩል እየሰራን ነው ያለነው።
የክልል ሥነ ምግባርና ጸረ ሙስና ኮሚሽኖችን በማግኘት በወረዳና በዞን ደረጃ ያለውን ማህበረሰብ እንዲያስተምሩ የጋራ እቅድ ይዘን የምንሰራበት ሁኔታም አለ።
አዲስ ዘመን፦ እርስዎ ውጤቱን እንዴት ይገመግሙታል?
ኮሚሽነር አየልኝ፦ የማስተማር ሥራ ውጤት የሚታየው በረጅም ጊዜ ነው፤ አንድን የክፍል ተማሪ ዛሬ አስተምረሽው ነገ ፈተና በመስጠት ውጤቱን መለካት ትችይ ይሆናል ግን የኅብረተሰብን ግንዛቤ የማሳደግ ሥራ ውጤቱ በረጅም ጊዜ የሚታይ በመሆኑ ውጤቱ እዚህ ላይ ነው ለማለት ያስቸግራል።
ሆኖም ግን ብዙ የማህበረሰብ ክፍሎች ስለ ሙስና አስከፊነት በአገር ላይ የሚያስከትለውን ጠንቅ እንዲገነዘቡ በማድረግ በኩል ውጤት አልመጣም ለማለት አይቻልም። በዘንድሮ ዓመት ደግሞ የኅብረተሰቡ ግንዛቤ ምን ላይ ነው? የሚለውን ስለምናጠና የበለጠ በጥናት የተደገፈ መረጃ መስጠት ይቻላል።
አዲስ ዘመን፦ ስለ ሙስና አስከፊነት ግንዛ ቤው ዳብሯል የምንለው የኅብረተሰብ ክፍልስ ድርጊቱን በማጋለጥና ጥቆማ በመስጠት በኩል ተሳትፎ እያደረገ ነው? በዚህስ ተሳክቶልናል ይላሉ ?
ኮሚሽነር አየልኝ፦ አዎ አሁን ላይ ሙስናን በመጠቆም በኩል ተሳትፎው ከፍተኛ ነው፤ ጥቆማውንም ወደእኛ፣ ወደ ፖሊስና አቃቤ ሕግም ይመጣል፤ ግን ኅብረተሰቡ በሚጠቁመው ልክ ምላሽ አለማግኘቱ አላበረታታ እያለው ነው ፤ በሌላ በኩልም በየአካባቢው ያሉ የትምህርት፣ የጤና፣ የውሃ ፕሮጀክቶች በሚጓተቱበትም ጊዜ ምክንያታቸውን ፈልፍሎ በማውጣትና በመታገል በየመድረኮቹ በማንሳት ባለሥልጣናቱን እየሞገተ ነው። ይህ እንግዲህ የግንዛቤ ፈጠራው ሥራው ውጤታማነቱን ያሳያል።
አሁን ላይ በአገሪቱ የሚፈጸሙ የሙስና ወንጀሎች ከእውቀት ማነስ የመጡ ናቸው አልልም። በቂ የሆነ ግንዛቤ አለ ግን ደግሞ ወደ ሙስና እንድንገባ የሚገፋፉ የመልካም አስተዳደር ችግሮች ደግሞ ብዙ ናቸው። ለምሳሌ አንድ ሰው መንጃ ፈቃድ ለማውጣት ቢሄድ ለፈታኙ ካልከፈለ ዘላለሙን ይመላለሳል እንጂ አያልፍም። የትም ሄዶ አቤቱታ አቅርቦ ደግሞ መፍትሔ ማግኘት አይችልም፤ ስለዚህ ልገላገል ብሎ ሳይፈልግ ሳይወድ ይከፍላል። ሌሎችም አገልግሎት ሰጪዎች ላይ ያለውም ነገር ተመሳሳይ ነው ።
አዲስ ዘመን፦የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርቱ ውጤት ቢያመጣም ቅሬታ ተቀባዩ አካል ምላሽ መዘግየት ትግሉን ወደኋላ እየጎተተው ነው እያሉ ነው?
ኮሚሽነር አየልኝ፦ በትክክል በየደረጃው ያለው ኃላፊ ተገቢውን የማጣራትና ለሁኔታው አግባብነት ያለው ምላሽ ባለመስጠቱ ምክንያት ሰዎች ያለ አግባብ ወደ ሙስና እየገቡ ናቸው። ይህ ደግሞ የግንዛቤ ፈጠራ ሥራችንን ውጤታማ ከማድረግ አንጻር የራሱ የሆነ አሉታዊ ተጽዕኖን ያሳድራል።
አዲስ ዘመን ፦በተለይም በተቋማት ደረጃ የሚፈጸሙ የሙስና ወንጀሎችን ሊከታተሉ ጥቆማም ሊቀበሉ የሚገባቸው የሥነ ምግባር መኮንኖች የተሰጣቸውን ኃላፊነት በአግባቡ ተወጥተዋል ማለት ይቻላል?
ኮሚሽነር አየልኝ፦ በየተቋማቱ ያሉ ቅሬታ ሰሚዎችም ሆኑ የሥነ ምግባር መኮንኖች የመስሪያ ቤቶቹ የበላይ ኃላፊዎች አማካሪ ናቸው እንጂ ወሳኝ አይደሉም። አንዳንድ ጊዜ አለፍ ብለው አንዳንድ ጉዳዮችን ለማጣራት የሚያደርጓት ትንሿ ጥረታቸው እንኳን በማያገባችሁ ገባችሁ አስብላ እርምጃ ታስወስድባቸዋለች ።
ሌላው በቦታው ላይ የሚመደቡት ሰዎች እንዲህ ዓይነት ትልቅ ኃላፊነት፣ ቁርጠኝነት፣ አልፎም አደጋ ያለውን ሥራ ተከታትለው በተለያየ መንገድ ፈልገው አግኝተው መርምረው ተጠያቂ ለማድረግ የሚያስችል አቅምም ብቃትም ፍላጎትም ያላቸው አይደሉም። አንዳንድ ጊዜ በሥራው ደከም ያለ ሠራተኛን ቦታ ተሰጥቶታል ለማለት ብቻ የሚመደብበት የሥራ ዘርፍም ነው።
ከዚህ አንፃር የሙሰኞቹን ተንኮል ብልጠት አውቆ በዚያው ልክ ተዘጋጅቶ ይህንን ለመዝጋት የሚችልና ቀድሞ ለመከላከልም የሚያስችል አቅም ያላቸው አይደሉም።
አዲስ ዘመን፦ ይህ የሚያሳየው ተቋማት ለጉዳዩ ትኩረተ አልሰጡትም የሚለውን ይመስለኛል፤ እርስዎ በዚህ ሃሳብ ይስማማሉ?
ኮሚሽነር አየልኝ፦ ተቋማት ሙስናን ለመከላከል ሥራው የሰጡት ትኩረት እጅግ አናሳ ነው። የሌላ አካል ሥራም አድርገው ወስደውታል። ለምሳሌ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አገልግሎት አሰጣጥ ላይ በርካታ ሰዎች ቅሬታ ያሰማሉ። ከላይ ያሉት ኃላፊዎች ግን ነጋዴው ስለሚያነሳውና ተጠቃሚው ስለሚያማርረው ጉዳይ ግድ አይሰጣቸውም። ይህ በሆነበት ሁኔታ ደግሞ የእኛ ተቋም በውጭ ሆኖ የሚፈታው ችግር ሊኖር አይችልም። ምክንያቱም ተቋማት የራሳቸውን ችግር መፍታት ያለባቸው የአሠራር ሥርዓትን በመዘርጋት ስለሆነ።
ሌላው ተቋማት ጉዳዩን ችላ የማለታቸው ምልክት ኮሚሽኑ ስብሰባዎችን ሲጠራ እንኳን ትክክለኛውን ሰው ከመላክ ይልቅ ዝም ብለህ ታይተህ ና በሚል መንፈስ አንድ ሰው ይልካሉ።በዚህ ሁኔታ ወደፊት ምን ሊሆን እንደሚችል የምናየው ይሆናል።
አዲስ ዘመን፦ ከለውጡ በኋላም ይህ ሁኔታ መሻሻል አላሳየም ይላሉ ?
ኮሚሽነር አየልኝ፦ መሻሻል መጥቷል አልመጣም የሚለውን ማየት የሚቻለው ለውጡ ትንሽ ጊዜ ከተጓዘ በኋላ ነው።አሁን ለጊዜው በጣም ረጅም ጊዜ የቆዩና ትስስራቸውን የዘረጉ የሥራ ኃላፊዎች ስለተወገዱ ለጊዜው ከላይ አካባቢ ችግሮች እየታዩ አይደለም። ግን ይህ ነገር ካልተጠናከረና በአሠራር ሥርዓት ማስተካከል ካልተቻለ ነገም እንደገና ተመልሶ አይፈጠርም ማለት አይቻልም። ወደታች ደግሞ ችግሩ እየሰፋ ነው፤ በዝቅተኛ የሙስና ተግባርም ብዙ ችግሮች እንዳሉ ነው እየሰማን ያለነው። በመሆኑም ይህ ነገር አድጎና ጎልብቶ ከባድ ደረጃ ላይ እንዳይደርስ የመገናኛ ብዙኃንም ያሉትን ችግሮች በመጠየቅ በማጋለጥ መንግሥትን በመግፋት ሚናቸውን ሊወጡ ይገባል።
አዲስ ዘመን፦ ተቋሙ አሁን እያስተማረ ያለው የሥነ ምግባር ትምህርት በተለይም ልጆችና ወጣቶች ከታች ጀምሮ አውቀውት እንዲወጡ በሥርዓተ ትምህርት ውስጥ ማካተት ለምን አልተቻለም?
ኮሚሽነር አየልኝ ፦ ባለፈው ዓመት አንድ ትልቅ ሥራ የሰራነውና ከትምህርት ሚኒስቴር እንዲሁም ከተለያዩ የሃይማኖት ተቋማት ጋርም እየተነጋገርንበት ያለነው ነገር ነው። በእርግጥ አሁን ትልልቁንና በተለያየ የሥራ ኃላፊነት ላይ ያለውን ሰው መለወጥ በጣም ከባድ ቢሆንም ሥራውን እናቆማለን ማለት አይደለም። የአሠራር ሥርዓቱን ማጠናከር፣ የመከላከል ሥራውን መስራት እንደተጠበቀ ሆኖ አዲሱ ትውልድ ላይ ግን ትኩረት ማድረግ አለብን ብለን «የሕፃናትና ወጣቶች የስነ ምግባር ግንባታ» የሚል አገራዊ ስትራቴጂ ቀርጸናል። ይህ ስትራቴጂ እንዲተገበር የሚፈለገው በቤተሰብ፣ በትምህርት ቤት ደረጃም ነው።
ለምሳሌ እንደ ቬትናምና ቻይና ያሉ አገሮች ይህንን አካሄድ ይጠቀሙበታል፤ እነርሱ ጋር በአንደኛና በሁለተኛ ደረጀ እንዲሁም ከዚያም ከፍ ባለው የትምህርታቸው እርከን የሥነ ምግባር ግንባታ ትምህርቶችን ያስተምራሉ፤ እኛም የእነሱን ልምድ ቀምረን ተዘጋጅተናል አብረውን ከሚሰሩ አካላት ጋርም ተፈራርመናል።
በተያዘው የትምህርት ዘመን ትምህርት ሚኒስቴርም በኅብረተሰቡ ግፊት ፍኖተ ካርታ (ሮድ ማፑን) በማዘጋጀት ቀድሞ የነበረውን የሥነ ምግባርና ሥነ ዜጋ ትምህርትን ሥነ ምግባር ላይ ትኩረቱን እንዲያደርግ በማድረግ ሥርዓተ ትምህርት እየከለሰ ነው፤ በዚህ አካሄድም በቅርቡ ትምህርት ይሰጣል ብለን እናስባለን።
ሌላው የሃይማኖት ተቋማትም በወጣቶች የሥነ ምግባር ትምህርት ላይ ቢሰሩ አገር ላይ የሚያበረክቱት ገንቢ ሚና ትልቅ መሆኑን በማመን ከተቋማቱ ጋር ስምምነት ተፈራርመናል እነሱም የግብረ ገብና ሥነ ምግባር ትምህርት አካተው ለመስጠት ተስማምተዋል። ይህ ሥራ ምናልባትም በአጭር ጊዜ ውጤቱ የሚታይበት ባይሆም የዛሬ 20 እና 30 ዓመት ግን ከፍተኛ ውጤትን የሚያመጣ መሆኑ ምንም አያጠራጥርም።
አዲስ ዘመን፦ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ሀብታቸውን እናንተ ጋር ያስመዘግባሉ፤ ኅብረተሰቡ ሲጠይቅ ደግሞ እናንተ ታሳያላችሁ፤ አሁን ላይ ግን ሥራው የተቀዛቀዘ ይመስላል ምክንያቱ ምን ይሆን?
ኮሚሽነር አየልኝ፦ አሁን ላይ የሀብት ምዝገባው እየተካሄደ ነው። ሆኖም ወቅቱን ጠብቆ ማሳደስ ላይ ችግሮች አሉ። ለዚህ ሁኔታ መፈጠር ደግሞ ዋናው ምክንያት ሕጉ ላይ ክፍተት ያለ መሆኑ ነው። ይህም ሲባል ያላስመዘገበ ወይም ያላሳደሰ 1 ሺ ብር ገደማ ቅጣት ይጣልበት ይላል፡፡ ከዚያ ካለፈ ደግሞ ወደ አቃቤ ሕግ ወይም ወደ ፖሊስ ጉዳዩ ተልኮ ክስ ይመስረት ነው የሚለው እዚህ ላይ ግን ሁለቱም አካላት ካሉባቸው ሌሎች ተደራራቢ የሥራ ኃላፊነቶች አንጻር ጫና የሚፈጥርና የማያስኬድ ስለሆነ እስከ አሁን ተግባራዊ ማድረግ አልተቻለም።
ሌሎች አገሮች ላይ ግን በተለይም ሀብታቸውን ያላስመዘገቡ የሥራ ኃላፊዎች ሲኖሩ የሚደረገው የሥነ ምግባር ክስ መመስረት፣ ከኃላፊነት ማንሳት፣ የማስጠንቀቂያ ደብዳቤ መጻፍ፣ መገናኛ ብዙኃንን ተጠቅሞ ሀብታቸውን አላሳወቁም በሚል ለሕዝቡ ይፋ ማድረግና ማሳጣትን ይከተላሉ። የእኛ አገር ሕግ ይህንን እንድናደርግ አይፈቅድም። አሁን ግን እነዚህን ተሞክሮዎች በመቀመር ሕጉን ለማሻሻል ሥራዎች እየተሰሩ ነው።
ሕጉ የሥራ ኃላፊዎቹ ያስመዘገቡት ሀብት ለሕዝብ ይፋ ይሆናል። በደብዳቤ ለጠየቀ ሰውም ይሰጥ ይላል፤ ለሕዝብ ይፋ የሚሆነው የነማን ሀብት ነው የሚለው ግን በግልጽ አልተቀመጠም፤ በሌላ በኩልም ኮሚሽኑ ይህንን ሥራ በአግባቡ ለመስራት የሀብት ምዝገባ ማህደሩ በተገቢው ሁኔታ አልተጠናቀቀም። በአጠቃላይ እነዚህና ሌሎች ውስንነቶች ቢኖሩም ምዝገባው እየተካሄደ ሲሆን ለኅብረተሰቡም ክፍት ነው።
አዲስ ዘመን፦ ግን እኮ ኮሚሽነር ይህ የባለስልጣናቱን ሀብት መጥቶ ለጠየቃችሁ እያሳያችሁ ቢሆንም በእኔ እምነት ተደራሽነታችሁ ውስንነት ያለበት ይመስለኛል እርስዎ ምን ይላሉ?
ኮሚሽነር አየልኝ፦ አሁን ያላደረግነው እሱን ነው። እስከ አሁን በጋዜጣ፣ በመጽሔት ወይንም በድረ ገጽ ይፋ አድርገን ኅብረተሰቡ በያለበት ሆኖ እንዲያየው አልሆነም። ምክንያቱ ደግሞ ይህን ለማድረግ የሚቀሩ የሕግ ድንጋጌዎች በመኖራቸው ነው። የሕጉን ነገር ስናጠናቅቅ ደግሞ የተወሰኑ ባለሥልጣናትን ሀብት በይፋ የምንገልጽ ይሆናል።
አዲስ ዘመን፦ እስከ አሁንም ሀብት እየተመዘገበ ነው የመጣው ወደፊትም ይቀጥላል። ግን በእኛ አገር ሙስናን ተከላክሎ ውጤቱን እናይበታለን ብለው ያስባሉ?
ኮሚሽነር አየልኝ ፦ ይህ በጣም ጥሩ ጥያቄ ነው፤ በሌሎች አገሮች ይሰራል በእኛ አገር ግን ጥሬ ገንዘብ ላይ የተመሰረተ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ የምናደርግ በመሆናችን ፣ ያልተመዘገቡ ብዙ ነገሮች ስላሉን፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ የሰዎች ታማኝነት ጥያቄ ምልክት ውስጥ ስለወደቀ ውጤታማነቱ በጣም ዝቅተኛ ነው።
አዲስ ዘመን፦ ስለዚህ እኮ አስፈላጊም አይደለም ማለት ነው ?
ኮሚሽነር አየልኝ ፦ ችግር ቢኖርም ምዝገባው አስፈላጊ ነው፤ ባህሉን ከአሁኑ እየፈጠርን እያለማመድን ካልሄድን ከዚህ የባሰ አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ነው የምንገባው። ይህንን ያልኩት ለምን መሰለሽ? አንድ ባለሥልጣን ሀብትህን ታስመዘግባለህ ስትይው የሚፈጠርበት ተጽዕኖ አለ በዚያው ልክ መጠንቀቅም ይጀምራል፤ ወደ ሌላ ሰው አዘዋውራለሁ ቢል እንኳን የመካካድ ሁኔታን ስለሚፈራ አያደርገውም ስለዚህ ሳይወድ በግድ የራሱ ያልሆነን ሀብት ከመሰብሰብ ይቆጠባል ማለት ነው። ስለዚህ መመዝገቡ ሙስናን በመከላከል በኩል የራሱ የሆነ አስተዋጽዖ ያለው ነው።
አዲስ ዘመን፦ ተቋሙ በመኖሩ ይህን ነገር ማዳን ተችሏል፤ባይኖር ኖሮ በዚህ መልኩ እንጎዳ ነበር የሚሉት ነገር አለ?
ኮሚሽነር አየልኝ ፦ ተቋሙ በመኖሩ አገሪቱ ሙስናን እየተከላከለች ነው በሚል በዓለም አቀፍ ደረጃ አመኔታን እንድትገነባ አድርጓል። ለዚህ ማሳያው ደግሞ ባለፈው በዓለም አቀፍ ደረጃ ሁለት አገሮች ተመድበው የሕግ መሠረቶቻችንን፣ ሙስናን ለመከላከል የምናደርገውን የማስተማር ሥራ አይተው ሕጉ ጠንካራ መሆኑን ተረድተው አድናቆትና ድጋፋቸውን ሰጥተውናል ፤ ይህ ደግሞ ቀላል አይደለም።
ሌላው በተለይም በአፍሪካ አገሮች ያልተደረገ የዓለም ባንክ 7መቶ ሚሊዮን ዶላር በላይ ገንዘብ ለትምህርት፣ ለጤና፣ ለውሃና ለኃይል አቅርቦት ድጋፍ አድርጓል፤ ይህ ገንዘብም በአግባቡ ለታለመለት ዓላማ መዋል አለመዋሉን እንከታተላለን፣ እናጣራለን ለባንኩም ሪፖርት እናደርጋለን። ችግሮች ተፈጥረው ሲገኙም ለሕግ አካል እናቀርባለን። ከዚህ አንጻር ተቋሙ ከፍተኛ ሚና እየተወጣ ነው።
በአገር አቀፍ ደረጃ ኮሚሽኑ ሥራው ከጀመረ ጊዜ አንስቶ በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ያለአግባብ ከሕዝብ የተነጠቁ መሬቶች እንዲመለሱ ሆኗል፤ በጣም ብዙ የሙስና ወንጀለኞች ለሕግ ቀርበዋል። በማስተማርና ግንዛቤን በማሳደግ በኩልም ቢሆን ኅብረተሰቡ ግንዛቤው እንዲያድግ የራሱን ሚና ተጫውቷል። በአጠቃላይ ተቋሙ በመኖሩ ብዙ ሥራዎችን ሰርቷል አሁንም እየሰራ ነው። የተቋሙ መኖርም ለጸረ ሙስና ትግሉ በጣም አስፈላጊ ነው።
አዲስ ዘመን፦ ስለዚህ የሥነ ምግባርና ጸረ ሙስና ኮሚሽን የለም ለሚሉ አካላት አለን ነው መልስዎት?
ኮሚሽነር አየልኝ፦ ኮሚሽኑ የለም የሚሉት እኮ ከአንድ አቅጣጫ ብቻ ስለሚያዩት ነው። ይህም ምንድን ነው መሰለሽ መክሰስ፣ መቅጣት አለበት ብሎ ከማሰብ የመነጨ ነው። ይህ ኃላፊት ደግሞ አሁን ሙሉ በሙሉ ተወስዷል። ይህም ቢሆን ግን ሰዎች ኮሚሽኑ የለም የሚሉት ከዚህ ቀደም የሰራቸውን ሥራዎች ካለመቀበል አይመስለኝም።
አዲስ ዘመን፦ ሕዝቡ ሊያደርግለት ከሚፈልገው ነገር አንጻር ግን ተቋሙ አሁንም ውስንነቶች አሉበት ብለው ያምናሉ?
ኮሚሽነር አየልኝ፦ ብዙ ጊዜ መድረክ ስንፈጥር ከዚህ ቀደም ተግባራዊ እርምጃን ስለምትወስዱ መረጃ ለመስጠት በጣም ተደፋፍረንና ፈልገን ነበር ከእናንተ ጋር የምንሰራው አሁን ላይ ግን ችግሮቻችንን እየፈታችሁ አይደለም ይሉናል። ኮሚሽኑ ድሮም ድክመት ነበረበት አሁንም ባለው ሁኔታ ጠንካራ ነው ለማለት አይቻልም።
አዲስ ዘመን፦ ኮሚሽኑ እስከ መቼ ነው ከድክመቱ ጋር የሚቀጥለው? መቼስ ነው የሕዝቡን እንባ የሚያብሰው?
ኮሚሽነር አየልኝ፦ በኮሚሽኑ ውስጥ ያለን ባለሙያዎችና ኃላፊዎች ተቋሙ መመርመርና መክሰስ ካልቻለ በማስተማር ብቻ ችግር ልንፈታ አንችልም፤ ኅብረተሰቡም የሚጠብቀውን አገልግሎት ሊሰጥ አይችልም የሚል የተስፋ መቁረጥ ዝንባሌ ውስጥ ገብተናል። ሌላው በኅብረተሰቡ እየተደገፍን በመንግሥት ተቋማትም እየተደመጥን አይደለም፤ ከዚህ አንጻር ተቋሙ ተልዕኮውን ለመወጣት አይችልም በማለት ነባር የሆኑና የብዙ ዓመት የሥራ ልምድ ያላቸው ባለሙያዎች ሥራ እየለቀቁ ነው። ይህን እንግዲህ በአስተሳሰብ መቀየር ያስፈልጋል።
ተቋሙ የሚሰራው የማስተባበር ሥራ፣ ዓለም አቀፋዊ ግንኙነታችን በማጠናከር ተሞክሮን የማምጣት ጥረት፣ ፖሊሲ ስትራቴጂ ቀርጾ ተቋማት እንዲተገብሩት ማድረግ ትንሽ አለመሆኑን ከባለሙያው ጋር መተማመን መፍጠርና አቅሙን ተጠቅሞ ውጤታማ ሥራን እንዲሰራ ማድረግ ያስፈልጋል።
የጸረ ሙስና ትግል መከላከልን ብቻ በያዘ ተቋም ቀርቶ መክሰስና ማሰር ቢጨመር እንኳን የመንግሥት ድጋፍና ትብብር ከሌለው የትም ሊደርስ እንደማይችል በመረዳት ከፍተኛ የፖለቲካ አመራሮች ፍቃደኛና ለሥራው ቁርጠኛ በመሆን በየጊዜው እራሳቸውን የትግሉ ተሳታፊ ማድረግ ይኖርባቸዋል። ይህንን ማድረግ ከቻሉ ደግሞ ውጤቱ የሚታይ ይሆናል።
በሌላ በኩልም የጸረ ሙስና ትግሉ መንግሥት የፈለገውን ያህል ቁርጠኛ ቢሆን ሥርዓት ቢያስቀምጥ የሕዝብ ተሳትፎ ከሌለበት ውጤቱን ማየት ከባድ ነው። በመሆኑም የትግሉ ግንባር ቀደም መሪ ሆኖ መቆም ያለበት ሕዝብ ነውየዛሬ በየሰፈሩ መሠረታዊ ባልሆኑ ተራ ነገሮች ከምንበጣበጥ ይልቅ ለብጥብጥ ምክንያት የሆነውን ፍትሀዊ ያልሆነ አገልግሎት አሰጣጥ ለማሻሻልና ብንሰራና ሙስናን በጋራ ብንታገል መንግሥትም ተገዶ ተቋማቱን ሕጋዊ ሥርዓት እንዲኖራቸውና በቅንነት እንዲያገለግሉ ያደርግ ነበር።
በሌሎች አገሮች ለጸረ ሙስና ትግል ትልቅ አስተዋጽዖ የሚያደርጉት የመገናኛ ብዙኃን ናቸው፤ በእኛም አገር ሕዝቡን በማንቃት፣ በማስተማር፣ ግንዛቤን በመፍጠር፣ ሙሰኞችን በማጋለጥና እርምጃ እንዲወሰድባቸው በማድረግ በኩል በተለይ አሁን የተሻለ የሥራ ሁኔታ ስላለ የበኩላቸውን አስተዋጽዖ ማድረግ አለባቸው።
መንግሥት ተቋሙ እንዲሁ ነው መቀጠል ያለበት ወይንስ ጠንካራ ሆኖ መቆም አለበት የሚለውን አስጠንቶ ለአገሪቱ በሚበጅ መንገድ መልሶ ማቋቋም ይጠበቅበታል።
አዲስ ዘመን፦ በጣም አመሰግናለሁ።
ኮሚሽነር አየልኝ፦ እኔም አመሰግናለሁ፡፡
አዲስ ዘመን ጥቅምት26/2012
እፀገነት አክሊሉ