ባለፉት ጊዜያት የሰላም እጦት፣ ያለመረጋጋት እና የህግ የበላይነት አለመረጋገጥ ችግሮች ይስተዋልባቸው ከነበሩት የሀገራችን አካባቢዎች አንዱ ምዕራብ ኢትዮጵያ ነው። የታጠቁ ኃይሎች፣ በወንጀል እጃቸው የተጨማለቁ ግለሰቦች እንዲሁም ከአጎራባች ሀገራት በሚገቡ ታጣቂዎች የሚፈጽሙት ጥቃቶች በአካባቢው ይከሰቱ ለነበሩ የጸጥታ ስጋቶች እንደመንስኤነት ይጠቀሳሉ። የዜጎች በሰላም የመኖር፣ ከቦታ ቦታ የመዘዋወርና በፈለጉበት የአገሪቱ አካባቢዎች ላይ ኑሮን የመመስረት መብትም ቅርቃር ውስጥ ገብቶ ሰነባብቷል።
የአካባቢው ነዋሪዎች ዋነኛው ምኞትና ጸሎትም በሰላም ወጥቶ በሰላም መመለስ ስጋት ሆኖ ቆይቷል። ይህን ፍላጎቱንም ለመንግሥት ሲያሳውቁ ተደምጠዋል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ መንግሥት ከህዝቡ ጋር በመሆን እያከናወነ ባለው ሥራ የፀጥታ ስጋቶችን በመለወጥ በአካባቢው የሰላም ንፋስ መንፈስ መጀመሩን የቄሌም ወለጋ፣ የካማሽ፣ የምዕራብ ጎጃም ዞን እና የአኝዋ ዞኖች የሥራ አመራሮች ይናገራሉ።
በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል የካማሽ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ታሪኩ ኩመራ እንደተናገሩት፤ የዛሬ 10 ወር ገደማ የታጠቁ ኃይሎች ጥቃት መፈጸማቸውን ተከትሎ ዞኑ ለሰላም እጦት ተዳርጓል። በዚህም ዜጎች ለህልፈትና ለመፈናቀል ተዳርገዋል። ችግሩን ለመቅረፍ ከአጎራባች ህዝቦች ጋር ተደጋጋሚ የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት መድረኮች ተካሂደዋል። በመድረኮቹ በህዝቡ መካከል የነበረው መልካም ግንኙነት እንዲመለስ አድርጓል። በአሁኑ ወቅት በአካባቢ የሰላም ንፋስ እየነፈሰ ነው ሲሉም ይገልጻሉ።
አካባቢውን ከማረጋጋት ሥራው ጎን ለጎን በተፈጠረው ችግር ምክንያት የተፈናቀሉትን የማስመለስ ሥራ መሠራቱን የሚናገሩት አቶ ታሪኩ፤ ከካማሽ ተፈናቅለው በኦሮሚያ ሰፍረው የነበሩና ለመመለስ ፈቃደኛ የሆኑ 44ሺህ እንዲሁም ከአማራ ክልል ሦስት ሺህ ወደ ቀዬያቸው ተመልሰው ኑሯቸውን መጀመራቸውን አንስተዋል። በተመሳሳይ ከአጎራባች ክልሎች ተፈናቅለው ወደዞኑ የመጡትም ወደነበሩበት መመለሳቸውን አብራርተዋል።
የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት የሚፈልጉ አካላት ግጭቱን የብሄር አስመስሎ በማቅረብ የፖለቲካ ትርፍ ለማጋበስ ጥረት ማድረጋቸው ችግሩን በመጠኑ አወሳስቦት ነበር የሚሉት አቶ ታሪኩ፤ ግጭቱ የብሄር እንዳልነበር ህዝቡ ስለሚያውቅ ግጭቱን በማርገብ አለመረጋጋቱን መቆጣጠር ተችሏል ይላሉ። ከተፈጠረው ግጭት በኋላ ህዝቡ ተመልሶ ያለ ምንም ችግር ኑሮውን መቀጠሉ ግጭቱ የህዝቦቹ አለመሆኑን አመላካች ነው ብለዋል።
እንደ አቶ ታሪኩ ማብራሪያ፤ የአመራር ድክመት ለተፈጠሩት ችግሮች የራሳቸውን አስተዋጽኦ አበርክቷል። የአመራር ችግሮችን ለመቅረፍ ድክመት ያለባቸውን አመራሮች ለመለየትና ለማብቃት ከክልል እስከ ወረዳ ውይይቶችና ግምገማዎች ተካሂደዋል። ክፍተት ያለባቸው በአጭር ጊዜው ውስጥ ከኃላፊነት እንዲነሱ ተደርገዋል።
በተለይም በሀገሪቱ ውስጥ ያለውን ብዝሃነት ተገንዝበው መምራት ያልቻሉ አመራሮች ከኃላፊነታቸው እንዲነሱ መደረጉን ጠቁመዋል። በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ በግጭቶች ተሳትፎ የነበራቸው አመራሮች ላይ ፖለቲካዊና አስተዳደራዊ ዕርምጃዎች ተወስዶባቸዋል። ይህ ሥራ አሁንም ተጠናክሮ ይቀጥላል ባይ ናቸው አቶ ታሪኩ።
የአካባቢን ሰላም ዘላቂ ለማድረግ የህዝቦችን አብሮነት የማጠናከር ሥራው በትኩረት እየተሠራ ነው የሚሉት አቶ ታሪኩ በተለይም፤ የምዕራብ ኦሮሚያ ዞኖች ከቤንሻንጉል ዞኖች ጋር ግንኙነታቸውን የሚያጠናክሩበት ሥራዎች እየተሠሩ ነው።
ሁለቱ ክልሎችና በሁለቱ ክልሎች የሚገኙ የታችኛው አስተዳደር እርከኖች የጋራ ልማትና ሰላም ሥራዎችን ትኩረት ሰጥተው እየሠሩ ይገኛሉ። አጎራባች ህዝቦችን የሚያስተሳስሩ መንገዶች ግንባታ እየተፋጠነ ነው። የአካባቢው ወረዳዎች፣ ዞኖችና ክልሎች የጸጥታ ሥራዎችን በጋራ እያከናወኑ መሆኑንም ጠቁመዋል።
በኦሮሚያ ክልል የቄሌም ወለጋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ምትኩ ኤሬሳ በበኩላቸው፤ ካለፉት ሦስት ዓመታት ወዲህ በዞኑ የሰላም እጦት እንደነበረበት ያስታውሳሉ። በሰላም እጦቱ ምክንያት አርሶ አደሩ በአግባቡ ማረስ የማይችልበት፤ ነጋዴው መነገድ የማይችልበት እንዲሁም ተማሪው ትምህርቱን በአግባቡ መከታተል የማይችልበት ሁኔታ ተፈጥሮ ቆይቷል። በዚህም ህዝብ ክፉኛ ተጎድቶ ነበር። የጸጥታ ችግሮች እንዲፈቱለት አጥብቆ እንደሚሻ በተለያዩ መንገዶች ሲገልጽ መቆየቱን ያነሳሉ።
የህዝቡን ጥያቄ መሰረት በማድረግ መንግሥት በአካባቢው ሰላምን ለማስፈንና የህግ የበላይነትን ለማስከበር መንግሥት በትኩረት መሥራት መጀመሩን የሚያነሱት አቶ ምትኩ፤ መንግሥት ከታጠቁ ኃይሎች ጋር ባደረገው ውይይትና ህዝቡ ባሳደረው ጫና አብዛኞቹ ታጣቂዎች ትጥቅ ፈትተዋል። ከጥቂት ሽፍቶች በቀር አብዛኞቹ ትጥቅ እንዲፈቱ ማድረግ መቻሉንም አብራርተዋል።
አብዛኞቹ ታጣቂዎች ትጥቅ ፈትተው ወደ ካምፕ ከገቡና ወደ ህብረተሰቡ ከተቀላቀሉ ካለፉት ሦስት ወራት ወዲህ በአካባቢው የጸጥታ መሻሻል ታይቷል። ተስፋ ሰጪ ሁኔታም ተፈጥሯል ይላሉ። አሁንም ጥቂት ትጥቅ ለመፍታት ፈቃደኛ ያልሆኑ ሽፍቶች እንቅስቃሴ አለ። እነዚህን ትጥቅ ለማስፈታት የሚደረገው ጥረትም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
እንደ አቶ ምትኩ ማብራሪያ፤ ፈርሰው የነበሩ ከቀበሌ እስከ ዞን ያሉ የመንግሥት መዋቅሮችን ባለፉት ሦስት ወራት መልሶ የማደራጀት ሥራ ተሠርቷል። አንድ ወረዳ ብቻ ሲቀር ሁሉም የመንግሥት መዋቅር ወደነበረበት ተመልሷል።
የቀበሌ ሊቀመንበር ያልነበራቸው ቀበሌዎች ሊቀመንበር እንዲኖራቸው ተደርጓል። ሚሊሻዎችን የማደራጀት ሥራም ተሠርቷል። በዞኑ አካባቢዎች የነበረውን ግጭት በመሸሽ ግብርናቸውን ትተው ወደ ከተሞች የገቡትን ህዝቦች ወደ እርሻቸው የመመለስ ሥራ ተሠርቷል።
በአማራ ክልል የምዕራብ ጎጃም ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ አበባው አንተነህ እንደሚሉት ባለፉት ጊዜያት በዞኑ አንጻራዊ ሰላም የነበረ ቢሆንም በአጎራባች የአማራ ክልል ዞኖች እንዲሁም የኦሮሚያና የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልሎች አጎራባች ዞኖች የተከሰቱ ግጭቶችና መፈናቀሎች በዞኑ አሉታዊ ተጽዕኖ ፈጥሯል። ችግር ካሉባቸው አካባቢዎች የተፈናቀሉ የዞኑ ተወላጆች መጥተው ተጠልለው ቆይተዋል።
ነዋሪዎቹ ከተፈናቀሉባቸው ዞኖች ጋር በመነጋገር ተፈናቃዮችን ወደ ቀዬያቸው የመመለስ ሥራ መሠራቱን የተናገሩት አቶ አበባው፤ ከዞኖቹ ጋር በተደረገው ውይይት ተፈናቃዮቹ ወደ ቀዬያቸው በመመለሳቸው በአካባቢው የነበሩት የጸጥታ ስጋቶች ቀንሰዋል። አሁንም ጥቂት የማይባሉ ተፈናቃዮች በመጠለያ ውስጥ ይገኛሉ። እነዚህን ሙሉ በሙሉ ለመመለስም በትኩረት እየተሠራ ነው ብለዋል።
እንደ አቶ አበባው ማብራሪያ፤ ከኦሮሚያ ሆሮ ጉዱሩና ምሥራቅ ወለጋ ዞኖች፤ ከቤንሻንጉል ጉሙዝ መተከልና ካማሽ ዞኖች ጋር የተለያዩ የምክክር መድረኮች በማካሄድ በቅርበት ሲሠራ እንደነበር ተናግረዋል። መድረኮች ላይ በአካባቢዎቹ ያሉ እውነተኛ ችግሮች ምን እንደሆኑ እየቀረቡ በመሆኑ መፍትሔ ለማስቀመጥ እገዛ እያደረገ ነው። የጋራ አቋም ወስዶ በጋራ በመሥራት ዳግም ግጭት እንዳይከሰት እገዛ ይኖረዋል። በቀጣይም ተቀራርቦ መሥራት ትኩረት የሚሰጠው ነው።
ህገ ወጥ የመሳሪያ ዝውውርና ከደቡብ ሱዳን የሚገቡ የታጠቁ ኃይሎች የሰላም ስጋት ሆነው መቆየታቸውን የሚናገሩት በጋምቤላ ክልል የአኝዋ ብሄረሰብ አስተዳደር ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ኡጉላ ኡጁሉ በበኩላቸው፤ የጦር መሳሪያ ዝውውርን ለመግታትና ድንበር ተሻግረው የሚገቡ ታጣቂዎችን ለመከላከል የክልሉ መንግሥት ከፌዴራል የጸጥታ መዋቅር ጋር በቅርበት እየሠራ መሆኑን ገልጸዋል።
በአካባቢው ሲዘዋወር የነበረው የጦር መሳሪያ ዝውውር በአሁኑ ወቅት ቆሟል። የደቡብ ሱዳን ሙርሌ ታጣቂዎች ይፈጽሙ የነበረው ጥቃትም ቀንሷል። አሁንም ከቀበሌ እስከ ዞን ያለው የመንግሥት መዋቅር ከፌዴራል የጸጥታ መዋቅር ጋር እጅና ጓንት ሆኖ እየሠራ ነው። በተከናወኑ ተግባራት በአካባቢው ይስተዋል የነበረውን የጸጥታ ችግር መቆጣጠር ተችሏል ብለዋል።
በአጠቃላይ ከዚህ ቀደም በምዕራብ ኢትዮጵያ ይስተዋል የነበረው የሰላም እና የፀጥታ ችግር በህዝብ እና በፀጥታ ኃይሎች የተቀናጀ ሥራ መልኩን ቀይሯል። በመሆኑም አካባቢው ዛሬ ሰላም በመሆኑ ባለሀብቶች ትተውት የሄዱትን ቦታ ተመልሰው በማልማት ትልቅ ሥራ እየሠሩ መሆኑን አስገንዝበዋል።
አዲስ ዘመን ነሃሴ 23/2011
መላኩ ኤሮሴ