በአሁኑ ወቅት አገርን ማሻገር እና የተሻለ ብርሃን ለመፈንጠቅ የሚታትር አመራር ያስፈልጋል:: የምስራቅ አፍሪካ ቀንድ ብዙ ፈተናዎች የተጋረጡበትና ለማየትም ሆነ ለመስማት የሚከብዱ ክንውኖችን እያስተናገደ ያለ ቀጣና ነው:: በየዕለቱ የዜጎች መፈናቀል፤ ሞትና ስደት በሰፊው የሚዘገብበት ቀጣና መሆኑ ነገሮችን የበለጠ ውስብስብ እያደረገው ነው::
ኢትዮጵያም በዚህ ቀጣና እንደመገኘቷ መጠን ብዙ ጥንቃቄ ማድረግ ይጠብቅባታል:: ለዚህ ደግሞ ”ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል” በሚል ብሂል ሳይሆን ”ሲሾም ያልሠራ ሲሻር ይቆጨዋል” በሚል እሳቤ የተቃኘ አመራር ያስፈልጋል::
በእርግጥ ”ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል” የሚል ብሂል ይዞ ወደ ሥልጣን መንበር የመጣን ሹመኛ ”ስትሾም ካልሰራ ስትሻር እንዳይቆጭህ” ቢባል ስላቅ ሊመስል ይችላል:: ዋ! ለህሊናህ ብለህ ስራ ብትለው የዘመኑ ምርጥ ምፀት ሊመስለው ይችላል:: ለመብላት መሾም አግባብ አይደለም። ለመስራት ነው መሾም፣ ህዝብ ለመካስ ነው መሾም፣ ለበለጠ ትጋትና ብርታት ነው ሹመት።
አገር የምትቃናው ለመብላት በተሾሙት ሳይሆን ወገባቸውን አስረው ለመሥራት ለሚተጉት ነው። ሹመት ትልቅ ኃላፊነት ነው፣ ሹመት ዕዳ ነው። አሁን ያለንበት ወቅት የሽግግር ወቅት ነው። የሽግግር ወቅት አመራር ባህሪ ደግሞ በማንኛውም ሁኔታ ችግሮችን በመጋፈጥ ለመፍትሄ የሚታትር ልበ ሙሉነት ነው።
የሚያጋጥሙ ፈተናዎችን ወደ መልካም አጋጣሚ መቀየር፣ መስመር የለቀቁ ትችቶችን በአመክንዮ ፈር የሚያስይዝ መሆን አለበት:: በሆይ! ሆይታ! ሳይሆን መረጃዎችን ግራ ቀኝ በማጣቀስ እና ከአስተውሎት የሆነ አመራር እና አሰራርን ማስኬድ ይገባል:: ሽግግር በባህሪው ሆደ ሰፊ፤ ልበ ቀና መሆን ይፈልጋል:: የሚወረወሩ የትችና ክፋት ጠጠሮችን በአየር ላይ መቅለብ ወደ ጠንካራ የመሰረት ድንጋይ የሚቀይር አስተሳሰብ ይፈልጋል::
በሽግግር ወቅት ብዙ ፈተናዎች አሉ:: የሥራ ዕድል ፈጠራም ሽግግር ወቅት ፈተና መሆኑ ይታመናል:: በአሁኑ ወቅት አገር በርካታ አበረታች ክንውኖች ቢኖሩም ብዙ የሚቀሩ ነገሮች አሉ:: ለአብነት በየዘርፉ በየዓመቱ 100ሺ የሚደርሱ ወጣቶች ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በመመረቅ ላይ ናቸው:: በተመሳሳይ ከኮሌጆችም በመቶ ሺዎች እየተመረቁ ነው:: እነዚህ ነገ ጥዋት ሥራ ካላገኙ፣ ለአገር ፈተና ነው የሚሆነው::
መንግስት በዚህ ላይ በጥልቀት ማሰብ አለበት:: ይህ በወቅቱ መፍትሄ ያገኝ ዘንድ ደግሞ ስትራቴጂክ አመራር ያስፈልጋል:: ለውጥ ከሚፈልጋቸው ጉዳዮች አንዱ ወቅቱን የዋጀ እና ህብረተሰቡን አንኳር ጥያቄዎች በአግባቡ የሚረዳ እና እንደቅደም ተከተላቸው ወይንም አንገብጋቢነታቸው እልባት የሚያበጅ ነው::
ሌላው አሳሳቢ ነገር የሙስና ጉዳይ ነው:: ሰው የሚታዘበው እና እውነታው ልዩነት አለው:: በሙስና የተዘፈቀ ማህበረሰብ ዘላቂ ልማት ያመጣል ብየ አላስብም:: ሰው በሚለው ከሄድን ከመሪዎች ጀምሮ እስከ ወረዳ ያሉት በሙስና ተዘፍቀዋል፤ ምንም እንኳን ሙሉ ለሙሉ ሙሰኞች ናቸው ባይባልም:: ፍርድ ቤት፣ ቀበሌ፣ መሬት አስተዳደር፣ ታክስ፣ ፍትህ አካባቢ ያለው ችግር እጅግ አሳሳቢ ደረጃ መድረሱም ይነገራል::
ታዲያ እነዚህ ችግሮች አገር አዘቅጥ ውስጥ የሚከቱ መሆናቸውን መረዳት ተገቢ ነው:: ይህን በወቅቱ ተገንዝቦ መፍትሄ የሚሰጥ አመራር ግድ ይላል:: ሽግግር በባህሪው ብዙ በረከቶችን ይዞ የሚመጣ ቢሆንም በዚያው ልክ ለሙሰኞችና አድር ባዮችም መንገድ የመክፈት ዕድል አለው:: በዚህ ወቅት በሙሰኞች ላይ አብዝቶ የሚጨክን ልብ ይፈልጋል:: የመልካም አስተዳደር ዕጦትን በሚፈበርኩት ማናቸውም አካላት ላይ የማይራራ አንጀት፤ ሐሞተ ጠንካራ ውሳኔ ያስፈልጋል::
በዚህ ዘመን አመራር ስራውን ሲለቅ እና አዲስ ተተኪ ሲመጣ የሚፈተንበት የመረጃ ክፍተት መኖሩ ነው:: መረጃን በወቅቱና በአግባቡ አለመያዝ ይስተዋላል:: መረጃ ለአገር ልማት፣ ለትምህርት ዕውቀት መስፋፋት፣ ለሳይንስና ቴክኖሎጂ መዳበር በተለይም አሁን ባለንበት በ21ኛው ክፍለ ዘመን አቻ የማይገኝለት መሣሪያ መሆኑ አጠያያቂ አይደለም:: መረጃ በአግባቡ ተሰብስቦና ተደራጅቶ ጥቅም ላይ እንዲውል ከተደረገ የህብረተሰቡን ችግር በመቅረፍ በኩል የሚጫወተው ሚና ከፍተኛ እንደሆነ ይታወቃል::
የሽግግር ወቅት አመራር እና መሪ መሆን ውሳኔዎችን ለመወሰን ሆነ ለቀጣይ አመራር የመሰረተ ድንጋይ ለመጣል አንዱ መረጃን በአግባቡን መያዝ ነው:: የሽግግር ወቅት አመራር መረጃን በአግባቡ ከያዘ እና ከሰነደ ለራሱም ለመጪው ቀላል ይሆናል፤ ጥሩ መደላድልም ይፈጥራል:: ሥራዎችም ይቃናሉ ውሳኔዎችም እንዲሁ በመረጃ ላይ የተመሰረቱ ይሆናሉ::
በተደጋጋሚ መንግስት በብዙ ዘርፍ ውስብስብ ችግሮች እንዳሉ እየነገረን ነው:: ከበርካታ የህብረተሰቡ ክፍሎችም የሚሰማው ይኸው ነው:: በርካታ ሰዎች በአገልግሎት አሰጣጥ ደስተኛ ሆነው አይታዩም:: በመሆኑም በመፈክር ብቻ ዘላቂነት እና ቀጣይነት ያለው ልማት፣ ሠላምና መረጋጋት አይመጣም:: ይህ ሊመጣ የሚችለው ለአገራችን ባለን ታማኝነት፤ በወሬ ሳይሆን በተግባር ነው::
እኔ የማምነው መሪነት በተግባር እና በአርያነት ሲታጀብ ነው:: በመሆኑም አንድ ሹመኛ እነዚህን ነገሮች ሁሉ ታሳቢ ያደረገ እንቅስቃሴ ማድረግ ይጠበቅበታል:: በተለይም ደግሞ በሽግግር ወቅት ያለ አመራር በብዙ የሚፈተንበት ሁኔታዎች አሉ:: በተመሳሳይ እውነተኛ እና ጠንካራ መሪም የሚታወቀው በዚህ ወቅት ነው:: በመሆኑም መሾም ችግር የሚፈታበት እንጂ ኪስ የሚደልብበት አለመሆኑን ማወቅ ተገቢ ነው::
ሃሳቤን ሳጠቃልል ህብረተሰቡ ለለውጥ መሥራት አለበት:: መንግስትም ለውጥ በሚፋጠንበት ላይ አፅንኦት ሰጥቶ መስራት ግድ ይለዋል:: ስለዚህ ሁሉም ኃላፊነት አለበት:: አመራሮች የህብረተሰቡ አገልጋይ መሆን ይጠብቅባቸዋል:: እውነተኛ መሪዎች የህዝብ አገልገይ መሆን አለባቸው:: ለሚመጣው ትውልድ ማሰብ እና ህዝቡ እንዴት ያስታውሰኛል የሚለው መቅደም አለበት::
ሩጫው የፖለቲካ ሃብት ለማጋበስ ወይም ለስልጣን ከሆነ አግባብ አይደለም:: ስለዚህ እዚህ ላይ ጠንካራ አቋም ያስፈልጋል:: ‹‹ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል›› የሚለውን አስተሳሰብ ህብረተሰቡ መቃወም አለበት፤ አመራሩም ሊፀየፈው ይገባል:: ”ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል” የሚለው ሃሳብ በሁላችንም ውስጥ መስረፅ አለበት:: ለልጆቻችን የምንናገረውና የምናሳየው ትውልድን የሚቀርፅ መሆን አለበት::
በመሆኑም ሙስናን የሚፀየፍ የአገርን ወቅታዊ እና ሁለተንተናዊ ሁኔታዎችን በመረዳትና በመገምገም የመፍትሄ አካል የሚሆን እንጂ ‹‹በቁስሉ ላይ እንጨት ስደድበት›› የሚል አካሄድ አያዋጣም:: ለዚህ ደግሞ አመራርነት ትልቅ ሚና አለው:: በቀና አመራሮች እሳቤና ፍልስፍና የተቃኘች አገር ህልሟ ትልሟም መሰረት ያያዘ እና ሩቅ አሳቢ ዜጎች የሚፈሩባትም ትሆናለች::
እኔም ለሀገሬ ለኢትዮጵያ እና ለህዝቧቿ የምመኘው ይህን ነው:: ሩቅ አሳቢ ቅርብ አዳሪ አመራር አያስፈልግም:: ሹመት የግለሰብ ኪስ ማድለቢያ እና የራስን ኔትወርክ መሰብሰቢያ ሳይሆን አገርን ወደ ከፍታ ማማ እና ብልጽግና የሚያስፈነጥር መሆን አለበት::
ይህ አምድ በተለያዩ ፖለቲካዊ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ዜጎች ነፃ ሀሳባቸውን የሚሰጡበት ነው። በዓምዱ ላይ የሚወጡ ጽሁፎች የዝግጅት ክፍሉን አቋም አያመለክቱም።
ዶክተር ጀኔኑስ
አዲስ ዘመን ግንቦት 13/2015