ዐውዳዊ ዳራ፤
“እናት ዓለም ጠኑ”፡- የተውሶ ርእስ ነው:: አዋሼ ደግሞ የአገራችን የጥበብ ዐምድ ሆኖ ለሁልጊዜም በልባችንና በታሪካችን ውስጥ እንደ አብሪ ኮከብ ሲዘከር የሚኖረው ነፍሰ ሄሩ ታላቃችን ሎሬት ጸጋዬ ገብረ መድኅን ነው:: ርእሱ የተወሰደው በ1967 ዓ.ም ለዕይታ ቀርቦ ከነበረው የባለቅኔው ቴያትር ነው:: በወቅቱ ተደራራቢዎቹን ረጃጅም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴያትር ቤትን ሰልፍ ተቋቁመው ቴያትሩን ለማየት ከታደሉት የዘመኑ ታዳጊ ወጣቶች መካከል አንዱ ይህ ጸሐፊ ነበር::
የቴያትሩ ታሪክ የቀዳሚውን የግማሽ ክፍለ ዘመን ኢትዮጵያን የሚወክል ብቻ ሳይሆን መልእክቱ ዛሬም ትኩስና “ይኼኛውን ‹የእኛ› ዘመን ጭምር እንደ መስታወት ቁልጭ አድርጎ ስለሚያሳይ እነሆ እንደ አዲስ ሊዘከር ግድ ብሏል::
“ሞት እንኳን ጨክኖ ወስዶ ከሚያስቀረው፣
ምናለ ደጋጉን ዳግመኛ ቢፈጥረው:: ”
በማለት ድምጻዊው እንዳንጎራጎረው በቴያትሩ ላይ ድርሻ የነበራቸው የዚያ ዘመን ከዋክብት ብዙዎቹ በሞት ተነጥቀውብን እስትንፋሳቸው ጨልሞ የተረፈን ትዝታቸው ብቻ ነው::
“የእናት ዓለም ጠኑን” መድረክ ካፈኩት ከዋክብት መካከል እንደ አርበኛው ዳምባል ሆኖ የተወነው ሃይማኖት ዓለሙ ከተለየን ሰንብቷል:: ወጋየሁ ንጋቱ (እንደ ጅሉ ሞሮ)፣ አውላቸው ደጀኔ (እንደ ተክልዬ አፈ ሊቁ)፣ ሰይፈ አርአያ (እንደ ኡዝባሽ ደባርቅ)፤ ዓለሙ ገብረ አብ (እንደ ሀሰን አሚሩ)፣ ተስፋዬ ሣህሉ (እንደ ነዳዩ ባዩ)፣ አስናቀች ወርቁ (እንደ አዴ ውቃው)፣ አሰገደች ሀብቴ (እንደ እናት ዓለም ጠኑ)፣ ሲራክ ታደሰ (እንደ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ)፣ ታደሰ ወርቁ (እንደ በላይ ዘለቀ)…ሌሎች በስም ያልተጠቀሱም ተካተው ሁሉም የረገፉብን አበቦችና ከዋክብት ናቸው::
ህያው ምስክር ሆኖ ትናንትን ከዛሬ ጋር ያቆራኘልንና በቴያትሩ ውስጥ እንደ “ኦርዮን ኮከብ” ደምቆ ያበራ የነበረው እጅግ የምንወደውና የምናከብረው ጋሽ ደበበ እሸቱ ነው:: ይህ የጥበብ ቀንድ አርቲስት የገራፊው ገብረየስን ሚና ወክሎ ሲጫወት እንኳን የመድረክ ጓደኞቹን ቀርቶ በብሔራዊ ቴያትር አዳራሽ ከአፍ እስከ ገደፍ ጢም ብለው ይሞሉ የነበሩትን የቴያትሩን ተመልካቾች ሳይቀር በጭካኔ የታጀበ ድርጊቱ ስሜታቸውን ያርድ እንደነበር ይህንን ጸሐፊ ጨምሮ ብዙዎች ምስክርነት የሚሰጡበት እውነታ ነው::
ገራፊው ገብረየስ “ጨካኝና አረመኔ” የሚባል ብቻ ሳይሆን በሚያነበንባቸው ቃለ ተውኔቶች ውስጥ ሰብዓዊ ባህርይውም በሚገባ ስለሚገለጥ ተመልካቹ በርካታ ጊዜያት በርህራሄ ስሜት ተውጦ ከፊሉ በከንፈር መጠጣ፣ አብዛኛው በግርምት፣ ብዙኃኑ በእምባ ጭምር እየተራጨ “እህህህ” ማለቱ በየመድረኩ የተለመደ ነበር:: ጭካኔውን ብቻም ሳይሆን የሚከተለውን የገራፊውን የትካዜ ቁዘማና መብከንከን እንደ ማሳያነት ማስታወስ ይቻላል::
“…አየህ አርበኛው ዳምባል፡- እኔና አንተ አንድ ነን:: አንተ ጀርባህን በጅራፍ፤ እኔ ስሜን በአፈ ታሪክ የተገፈፍን ‹ምንዱባን› ነን:: አንተ ሕይወትህን በስቅላት ነገ ብትገደል፤ እኔም ክብሬን በባህሌ ምክንያት ቀድሞም የተገደልኩ ነኝ:: ያንተ መከራ፣ ያንተ ወህኒ ግዙፍ፤ የእኔ መከራ የእኔ ወህኒ ረቂቅ መሆናቸው እንጂ ሁለታችንም እስረኞች ነን:: አሳሪውም ታሳሪውም አንተም እኔም ነን:: እኔ መናጢ ገራፊ፤ አንተ የትናንት ጀግና፣ የዛሬ ወንበዴ፤ ቀን የጣለህ፣ ንጉሥ የከዳህ፣ የትናንት አንበሳ የዛሬ ጥምብ አንሳ ነህ – መናጢ የመናጢ ተገራፊ፤ እስረኛ የጀግና እራፊ:: ”
“አንተም እኔም ሁለታችንም አንድ ነን:: እኔ እንደ እንቆቅልሽ በየትም ባህል የምንጦሎጦል፣ አንተ ጣሊያን ማርከህ፣ ንጉሥ ያከበረውን ባንዳ ደፍረህ፣ የአፍ እልፊት አልፈህ፣ ከስደተኛ አርበኛ ይበልጣል ብለህ፤ ትናንት ገንነህ፣ ዛሬ ቀለህ፣ ክብርህንና ስምህን ተነቅለህ…ልጆችህን፣ አሮጊት እናትህን ጫንቃህ ላይ ጥለህ፣ ሚስትህን ለእብደት ዳርገህ… እንደ እኔ ስምህን ተገፈህ፣ አርበኛው ዳምባል አየህ እኔና አንተ አንድ ነን:: ስም የሌለን፣ እኮ ስለምን እንጨካከን? ዳሩ ብንከፋፋ ምን ሊጠቅመን?”
ገራፊው ገብረየስ፡- የታወራውን አንድ ዐይኑን በሰባራ የመነጽር መስታወት ሸፍኖና በተቃርኖ የተሞላውን ስብእናውን አጀግኖ የመግረፊያ ጅራፉን ግራ ቀኝ እያወነጨፈ በባንዳዎች የግፍ ብያኔ በወገቡ ላይ አርባ ጅራፍ እንዲያርፍ ከተፈረደበት ዳምባል ጋር ሲወያዩ ሩቅ አገር ለመሄድ የሚሰነባበቱ የልብ ወዳጆ እንጂ የግፍ ዋንጫ አስጎንጪና ጎንጪ በፍጹም አይመስሉም ነበር::
የምስክሩ ቃል፤
“የያኔውን ‹የእናት ዓለም ጠኑ› መድረክህን 48 ዓመት ቢያልፈውም ወደ ኋላ ዞረህ እንዴት ትገልጸዋለህ?” ጋሽ ደበበ እሸቱን ስልክ ደውዬ የጠየቅሁት ጥያቄ ነበር:: በስልክ ውስጥ በሚደረግ ውይይት ስሜትን መጋራት ባይቻልም በመልሱ መሃል “ኡፍፍፍ…እህህ” እያለ ያወጣ የነበረው የትንፋሹ ወላፈን ከቋንቋና ከአካላዊ እንቅስቃሴ የበለጠ ትርጉም ሰጥቶኛል::
“በጠንካራ ቃለ ተውኔት ተጽፎና ተዘጋጅቶ በወቅቱ ትንታግ ተዋንያንና ተዋንያት ለመድረክ የበቃው ያ ዘመን አይሽሬ ቴያትር ከውጭ ቋንቋ የተተረጎመ ነው የሚሉ ሰዎች አጋጥመውኝ እንደነበር አስታውሳለሁ:: እውነት ነውን?” ለአንጋፋው አርቲስት ያስከተልኩት ሁለተኛ ጥያቄ ነበር::
“ልክ ነህ! ይወራ ነበር:: ምክንያቱ ደግሞ በወቅቱ የነበረው መንግሥታዊ ሣንሱር ቴያትሩን በአጭሩ ቀጭቶ እንዳያመክነውና በተዋናዮቹም ላይ ችግር እንዳያስከትል ታስቦ የተዘየደ ዘዴ ሳይሆን አይቀርም:: የጀርመኑን የናዚ ሥርዓት ይተች ከነበረው ቴያትር የተተረጎመ ነው እየተባለ በስሚ ስሚ መዛመቱ ስለዚሁ ምክንያት ሆን ተብሎና ታቅዶበት የተደረገ ይመስለኛል:: ” ከውይይታችን ተመጥነው የተወሰዱት ሃሳቦች እነዚህ ሁለቱ ብቻ ሳይሆኑ በርከት ያሉ ናቸው፤ ለጊዜው እነዚሁ ለአብነት ይበቁ ይመስለኛል::
ጭብጡና እውነታችን፤
የ“እናት ዓለም ጠኑ” ቴያትር ከፋሽት ኢጣሊያ ወራሪ ሽንፈት በኋላ የድል ማግሥቷን ፊውዳል ኢትዮጵያ (1933/4 ዓ.ም) ከወታደራዊው የደርግ መንግሥት ጨቅላ ዕድሜ (1967 ዓ.ም) ጋር የጉስቁል አገሬን ታሪክ አቀራርቦ የሦስት አሠርት ዓመታት ጉዞዋን በተምሳሌታዊ ጥበባዊ አቀራረብ ፍንትው አድርጎ ያመላከተ ድንቅ የፈጠራ ሥራ ነው:: የዛሬይቱ ኢትዮጵያም በዚህ የቴያትር መስታወት አማካይነት አንገቷን ቀና አድርጋ የፊቷን እድፍ እንድታይበት ብንፈቅድላት ሊጠቅማት እንደሚችል እናምናለን::
ከቴያትሩ ቃለ ተውኔት ውስጥ ጥቂት ማሳያዎችን በመጠቋቆም የዛሬ እኛነታችንን የሚገልጹ አንዳንድ አገላለጾችን እንመልከት:: ተክልዬ አፈ ሊቁ (አውላቸው ደጀኔ) የተባለው ገጸ ባህርይ ያነበነበውን የሚከተለውን ገለጻ ከራሳችን ዙሪያ ገብ ወቅታዊ ሁኔታ ጋር እያነጻጸርን ራሳችንን እንፈትሽበት፡- “አየህ አርበኛው ዳንባል አንተና እኔ ህመም ነን:: ያውም ድንገተኛ ህመም:: ለምክርም፣ ለመቀጣጫም፣ ለአርአያነትም አናመችም:: አንኳን ለአገራችን፣ ለቤታችን፣ ለልጆቻችን፣ ለሚስቶቻችንና ለእናቶቻችን ቀርቶ ለራሳችንም አናውቅም:: ለሥጋችን እንዳናውቅ በራሳችን አናምንም:: ለነፍሳችን እንዳናውቅ ዓላማችን ከቀን በኋላ ወደ ጥፋት አመራ:: ”
ስሙን ደግመን ደጋግመን ብናነሳም፤ “ይሙት ይኑር” ግራ ያጋባንና እርማችንን በአግባቡ እንኳን ማውጣቱ ተስኖን “በአሉ ተባባሉ” መላ ምት ስንወዛገብበት አራት አሠርት ዓመታትን የተቆጠረበት ባለ ትብ ብእሩ በዓሉ ግርማ ግራ የተጋባበትን ወቅታዊ ስሜቱን በመጽሐፉ ውስጥ የገለጸው የሚከተሉትን ስንኞች በማዋቀር ነበር::
እምባ እምባ ይለኛል፤ ይተናነቀኛል፣
እምባ ከየት አባቱ፤ ደርቋል ከረጢቱ፣
ሳቅ ሳቅም ይለኛል፤ ስቆ ላይስቅ ጥርሴ፣
ስቃ እያለቀሰች፤ መከረኛ ነፍሴ:: ”
ይህን መሰሉ ገለጻ የዘመኑ መንፈስ መገለጫ መሆኑን ጥቁምታ የሚሰጠን ተመሳሳይ ይዘት ያለው የአርበኛው ዳምባል ንግግር ነው:: እንዲህ ይላል፡- “እኔና የእኔ ብጤዎች ጥቅም በማይሰጥ ተስፋ ስንኖር በጥድፊያ፣ እንደ ሐረግ ሬሳ:: ስንጸልይ ጓሮ ጥሻ ሥር እንደ ሙጃ በጨለማ:: ስንቀነጠስ ግን በአደባባይ ነው አሉ:: …እኔ የወህኒ ኑሮዬን ተቀብየዋለሁ::
በበልግ ታጥሮ፣ ታምቆ እንደወየበ ቅጠል ነኝ:: ሳቄና እምባዬ እኩል በውስጤ ደርቆብኛል:: የሞት ስጋት የለብኝም:: ፍርሃቴ፣ የሕይወት ትዝታዬ እንዳያገረሽብኝ እንዳይመለስብኝ ነው:: ሳቅና እምባዬ በወህኒ ጭላንጭል ድንገት ሾልከው ገብተው በደቀቀ ሰውነቴ ደሞ እንደ ዝናብና እንደ ፀሐይ ዳግመኛ እንዳይፈራረቁብኝ ብቻ ነው ስጋቴ:: ” ዳምባል የውስጡን ቁስለት እየነገረን ያለው ሳቅና እምባ በተሟጠጡበት ሙት ተስፋ እየቃተተ እንደሆነ እንረዳለን:: ልክ በዓሉ ግርማ “ሳቅና እምባው” ተሟጦበት በደረቀ ስሜት እንደተንከላወሰው መሆኑ ነው::
አጽመ ታሪኩ፤
እናት ዓለም ጠኑ የደንበል እናት ነች:: ደንበል የበላይ ዘለቀ ጓደኛና አርባ ጅራፍ ተገርፎ እስከተሰቀለበት ጊዜ ድረስ ከጀግናው ጋር በሰንለት ተቆራኝቶ የሰነበተ አጣማጁ ነበር:: በላይ ዘለቀ ሲገረፍና ወደ መሰቀያው ቦታ ሲነዱት አርበኛው ዳምባል የትራዤዲ ትዕይንቱን የፊጥኝ እንደታሰረ ይመለከት ነበር:: “ጀግና ነህ” ብለው ለግርፋት ሲያዘጋጁትም እንዲህ እያለ የግፍ ደጋሾችን ይሞግት ነበር::
“አሁን ይኼ ልብ የጀግና ልብ ነው? ይይዙብኝ ነገር፣ ያስሩብኝ ይገርፉብኝ፣ ይሰቅሉብኝ ሰበብ ቢያጡ ጀግና ነህ ብለው ከጀግና ጋር አቆራኝተው ገረፉኝ እንጂ አሁን ይኼ ልብ የጀግና ልብ ነው? ቀጠቀጡኝ፣ ገረፉኝ፣ አካላቴን ጠበጠቡኝ:: መስክርበት አሉኝ፤ ያመለጥኹ መስሎኝ መሰከርኩበት:: ትፋበት አሉኝ ተፋሁበት:: እሱም በላይ ዘለቀ ጭ ጭ ብሎ አየኝ:: ሕቅ ብሎ በዓይኑ አዝኖ ተክዞ ሳያናግረኝ ሞተ:: … የዳንኩ መስሎኝ…”
እናት ዓለም ጠኑ ኑሮና ብልሃቱ አእምሮዋን ነክቶ የልጇን የዳምባልን ልጆች (አሳዳጊ ሆናለችና) በተጎታች ጋሪ ላይ ጭና ማቲዎቹን ለሽያጭ ገበያ ለገበያ፤ ጉልት ለጉልት የምታንከራትት ምስኪን ቀን የጨለመባት አያት ነች:: “ዶኬዬን ሲበላ ከርሞ ሲሰቀል አወርስሻለሁ ያለኝ የት አለ ንብረቱ? የመሬቱ የውል ሰነድስ የት አለ?” እያለች በላይ ዘለቀ በተሰቀለበት ማማ ሥር ቆማ “ያልፈጸመው ተስፋ አለ” እያለች በድኑን ትሞግታለች:: አልፋም ተርፋ በገመድ የተንጠለጠለውን በድኑን እየፈተሸች “የታለ የተስፋው ሰነድ” በማለት ትበረብረዋለች::
ጅሉ ሞሮ “በሕጻንነቱ የአየሩ የተጠናወተው… ዛሬ ቀና ብሎ ነው እንጂ ወትሮማ በሆዱ ነበር የሚሳብ:: እንደ እባብ ልጅ:: እዚያው እተወለደበት መቃብር ቤት ነው አሉ የተጣረረው:: በአራስነቱ:: እናት ዓለም ጠኑ ነበረች የጡት ልጅ ብላ ያሳደገችው:: ጋሪ ጎትታ ያሳደገችው:: ” ተብሎ የተገለጸው ጅሉ ሞሮ ገራፊው ገብረየስ በአጥቢያ ዳኛ ችሎት ውሳኔ ግርፋት የተፈረደባቸው መከረኞች አርባ ሲገረፉ ግርፋቱን ቆሞ የሚቆጥረው እርሱ ነው:: የቁጥር ችሎታው ከአርባ አይዘልም:: ቁጥር የለመደውም ተገራፊዎቹን ደጋግሞ በሞቁጠር ስለተለማመድ ነው::
ታሪኩ እንዲህና እንዲህ እያለ ይቀጥላል:: እናት ዓለም ጠኑ የመከረኛዋ አገሬ ምሳሌ ተደርጋ ተስላለች:: ሌሎቹም እንዲሁ ከገሃዱ ዓለም የተቀዳና የተወከሉበት የየራሳቸው ባህርይ አላቸው:: ዛሬም እንደ ነዳዩ ባዩ “ክብሬን ውሰዱና ዳቦ ስጡኝ” የሚሉ ተማጻኞች በገፍ እንዳሉ ማን ይክዳል?
ነዳዩ ባዩ እጅ እግሩ በሥጋ ደዌ በሽታ የተጠቃ “ለምኖ አዳሪ” ቢሆንም የእውቀት አቅሙና ብስለቱ እጅግ የረቀቀ እንደሆነ በቃለ ተውኔቱ መረዳት ይቻላል:: “ጠቡም ትግሉም የአንተና የእኔ እንጂ የአንተ እግዚአብሔርና የእኔ እግዚአብሔር ትግል አይምሰልህ:: በዚህች የሱባዔ ከበሮ በሚንርባት ምድር፤ በዚህች በሰው ልጆች ስም፣ በእኔና በአንተ በድሆቹ ስም ሀዘንና ማቅ በሰፈነባት አገር … የካህናትና የጠምጣሚ መሲሃን የጸሎት ኡኡታ ደወል ከማንም አገር ይልቅ ጎልቶ፣ ንሮ በሚደመጥባትና በሚያስገመግምባት ምድር የሰው ልጆች ደም፣ የድሆች ደም ወዝና ጉልበትም ጎልቶና ንሮ በከንቱ ሲፈስባት የምናየው:: በዚህች የእግዜር ወኪል፣ የእግዜር ወሬ ተርጓሚ በዝቶ በተጣባት አገር ነው:: ”
የዛሬዋ የእኛይቱ እናት ዓለም ጠኑ “ጀግና አይደለሁም” እያለ የሚሸሻትን የግድ ጀግና ነህ እያለች በግድ የምታገዝፍ ይመስለናል:: በግፍ የሚፈሰው ደም አልቆም ብሎ አእምሮዋን ያናወዛትም ይመስለናል:: ልጆቿ መደማመጥ ተስኗቸው ስቃይና አሰቃይ የሆኑበት “ጠኑ” ምን ይሉት መንፈስ ቢጻረራት ይሆን የወላድ መካን ሆኖ ከትናንት እስከ ዛሬ አሳሯ እንድትበላ የተፈረደባት?
“እማማ ዓለም ጠኑ፤ የገፋሽ ዘመኑ፣
ገመናሽ ተራቁቶ፤ ክብርሽ ተሸልቶ፣
ልጆችሽ በቅርጫት፤ እንደ ውሃ ጥፋት፣
አንቺ እንደ እሳት እራት፤ መፈንገል መደፋት፣
አዬ እናት አዬ እናት፤ እናት ልበ ጽኑ የደፋሽ ዘመኑ፣
እማማ ዓለም ጠኑ:: ”
ተውኔቱ የተዘጋበት የአውራጆችና የተቀባዮች ዜማ ነው:: እኛም እያንጎራጎርን የምንቆዝምበት ጭምር:: ሰላም ለአገራችን፤ ለዜጎችም በጎ ፈቃድ::
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ግንቦት 12/2015