ለመግባባት ቢያግዘን፤
“ባይተዋር” እና “ባእድ” የሚሰኙት ሁለት ቃላት ገራገር ድንጋጌ በሚሰጡ የቋንቋዎቻችን መዛግብተ ቃላት ውስጥ የሚበየኑት “አንድ አካል፤ አንድ አምሳል” እንዲሉ፤ ተመሳሳይ ፍቺ እየተሰጣቸው ነው:: እርግጥ ነው አንዱ ቃል ሌላኛውን እየተካ፤ አንዱ ሲጠራ ሌላኛውን እያስታወሰ ግልጋሎት ላይ መዋል የጀመሩበትን ዘመን እንመርምር ብንል ተዛምዷቸው ትናንት ከትናንት ወዲያ ወይንም አምናና ካቻምና የሚባል ሳይሆን ሺህ ዓመታት ወደ ኋላ ሊቆጠርላቸው ይችል ይሆናል::
እውነቱ ግን “ባይተዋርነት” እና “ባእድነት” ተመሳሳይ የጽንሰ ሃሳብ እስትንፋስ የተጋሩ ይምሰሉ እንጂ ጠለቅ ብለን ስንፈትሻቸው ከተመሳስሏቸው (Synonyms) ይልቅ የላቀና የጠለቀ ትርጉም እንዳላቸው መገንዘብ አይገድም:: ለምሳሌ፤ ከራሱ ምህዳር ርቆ በቋንቋ፣ በባህል፣ በሥነ ልቦና፣ በወግና በልማድ በተለየ አካባቢ ድንገት በእንግድነት የሚገኝ አንድ ግለሰብ እርግጥ ነው ባእድነትና ባይተዋርነት ሊሰማው ይችል ይሆናል::
ነገር ግን ያ ግለሰብ በቅቡል አስተሳሰቡ፣ ወይንም በእውቀቱና በሀብቱ፣ አለያም በዝነኛነቱና በተሰሚነቱ፣ ከፍ ሲልም በእንግድነት የተቀበለው ማኅበረሰብ በሚያጎናጽፈው የአንቱታ ቅቡልነት “የተሻለ” የሚባል ደረጃ ላይ የሚገኝ ከሆነ በተገኘበት ማኅበረሰብ ውስጥ የሚኖረውና የሚመላለሰው በአክብሮትና ነዎሩ እየተሰኘ ስለሆነ ለእርሱ ባእድነትም ሆነ ባይተዋርነት ትርጉም አይኖረውም::
“ባይተዋርነት” ግን በትርጉም ይዘቱ ኮምጠጥና ጠነን የማለት ባህርይ ይስተዋልበታል:: እንበልና ሌላ ሰው በእንግድነት በሚገኝበት ሥፍራ የማኅበረሰቡ ኑሮ ከእርሱ የአኗኗር ዘይቤ፣ ባህሉና ወጉ፤ ከባህላቸውና ከወጋቸው አጠቃላይ ሥሪት ጋር ስለማይገጥም ብቻ ሳይሆን በማኅበረሰቡ መለኪያና መስፈርት መሠረት እንደ መጤ ስለሚቆጠር መገፋቱና መገለሉ ሊጠነክርበት ይችል ይሆናል:: ስለዚህም ለእርሱ/ለእርሷ ባይተዋርነት ስሜትን ጥላሸት ቀብቶ የመኖር ያህል የከፋ መሆኑ አይቀርም:: ባይተዋርነት መገለል ብቻም ሳይሆን ኑሮውና ውሎውም እንግልት ስለሚበዛበት ሰብእናን ማጉበጡ አይቀሬ ይሆናል::
እንኳንስ ከአሁን ቀደም በማያውቁት አካባቢ እንግዳ ሆኖ መገኘት ቀርቶ በራስ አካባቢም እየኖሩ በባእዳን መከበቡ ሲበዛና የእኔ የሚባለው ሁሉ እየተሸረሸረ በከባቢዎቹ አተያይ “የእኛ ብቻ ይበልጣል” ወደ መባል ደረጃ የሚሸጋገር ከሆነ ባይተዋርነት ነፍስ ዘርቶ በመንቀሳቀስ ማንነትን የኀዘን ጥቀርሻ ማልበሱ አይቀርም:: ባእድነት አልፎ አልፎም ቢሆን “ከሩቁ ወንድሜ ባእዱ ጎረቤቴ” እንዲሉ በአወንታዊ ትርጉም መጠቀሱ የተለመደ ነው:: በአንጻሩ፡- “ባይተዋርነትና ጨለማ አንድ ነው” የሚል ተዘውታሪ ብሂል መኖሩም አይዘነጋም::
ስለዚህም በባይተዋርነት ላለመጠቃት ወይንም ለመፈወስ አዲሱ ከባቢ እስኪለመድ ድረስ ብርቱ ትዕግሥት፣ ተስፋ ያለመቁረጥ፣ ጽናትና ትዕግሥትን ይጠይቃል:: ያለበለዚያ ለባይተዋር ግለሰቡ “ትኖር እንደሆን አርፈህ ኑር፣ መርሃችንን ትተገብር እንደሆነ ተግብር ያለበለዚያ ዋ!” የሚል የፈረጠመ ውሳኔ የሚተላለፍ ከሆነ ባይተዋሩን ግለሰብ እንዲያገነግንና ተስፋውን አሟጦ የላሸቀ ሰብእና እንዲላበስ ከማድረግ ውጪ ምንም ፋይዳ ሊኖረው አይችልም::
አብዶ እያሳበደን ባይተዋር ያደረግን የቴክኖሎጂ ዜና መዋዕል፤
የቴክኖሎጂው ፈጣን ግስጋሴ የእያንዳንዱን ዜጋ ሩጫና ፍጥነት፣ ነፍስና ሥጋ፣ መንፈስና አቅል እያሳተ በወጀብና በአውሎ ነፋስ በሚመሰል ቱማታ ዘፍቆ በባይተዋርነት ማንገላታት ከጀመረ ሰነባብቷል:: የአሜሪካ የመከላከያ ሚኒስቴር (ፔንታገን) እ.ኤ.አ በ1950ዎቹ የመጨረሻ ዓመታት ገደማ በአንድ ትልቅ አዳራሽ ውስጥ የተተከለ IBM ሠራሽ ኮምፒዩተር መጠቀም እንደጀመረ ነበር “ዓለማችን እየጠበበች ነው” የሚለው አባባል ከብዙኃን ጆሮ መድረስ የጀመረው::
ይህ አባባል ይበልጥ ጎልቶ እንዲደመጥ “Global Village” በሚል ስያሜ እ.ኤ.አ በ1960ዎቹ የመጀመሪያ ዓመታት ገደማ በመጻሕፍቱ ውስጥ በበቂ ትንታኔ ያስተዋወቀው ካናዳዊ የሚዲያ ቲዎሪ ቀማሪው ማርሻል ማክላኸን ነበር:: የእንግሊዝኛው ሀረግ በእኛ ቋንቋ የተተረጎመው “ዓለም እንደ አንድ መንደር ጠባለች” ተብሎ ነው:: በዚህ አባባል አፉን ያላሟሸ፣ ወይንም ስለቴክኖሎጂ ግስጋሴ በተነገረበት መድረክ ሁሉ ብሂሉ እንደ አዝማች ተደጋግሞ ሲነገር ያላደመጠ ይኖራል ተብሎ አይገመትም::
የዓለማችን ጥበት ከትንሽ መንደርነት ወደ ቤታችን የሳሎን ስፋት ያህል ዝቅ ማለት የጀመረውና አባባሉም ተሻሽሎ “ዓለም የቤታችንን ስፋት ያህል ጠበበች” ተብሎ መነገር የጀመረው የቴሌቪዥንን መስፋፋት ተከትሎ ሲሆን ቀስ በቀስም ከቤት ሳሎን ወደ ጠረጴዛ ወርድና ስፋት ልክ “ዓለም ጠበበች” ማለት የተጀመረው ደግሞ የዴስክ ቶፕ ኮምፒዩተሮች መስፋፋት ሲጀምሩ ነበር:: ውሎ ሳያድር እ.ኤ.አ በ1981 አዳም ኦስበርን የተባለ ተመራማሪ ጭናችን ላይ የምናስቀምጠውን ላፕቶፕ ኮምፒዩተር ከፈጠረ በኋላ (Lap = ጭን ማለት እንደሆነ ልብ ይሏል) በቶሺባ ኩባንያ በኩል ለተጠቃሚው መቅረብ ሲጀምር “ዓለማችን ብላ ብላ ወደ ጭናችን ቀረበች” ተብሎ አድናቆቱ ተዥጎደጎደ::
የቴክኖሎጂው ፍጥነት የሩጫውን ዙር እጅግ በማክረር እ.ኤ.አ በ1980ዎቹ የመጨረሻ ዓመታት ግድም በመዳፋችን የምናሽሞነሙናት የእጅ ስልክ (Palme top computers) ቀስ በቀስ በሁሉም እጅ መግባት ስትጀምር “ዓለም በመዳፋችን ውስጥ ገባች” ተብሎ ዕልልታው ቀለጠ:: ይህን መሰሉ ጮቤም የሰነበተው ለጥቂት ጊዜ ነበር:: በጣቶቻችን መሃል አድርገን የምናፍተለትላቸው የእጅ ስልኮች መጠናቸው እጅግ አንሶ በሁለት ጣት ውስጥ በሚያዙ ሚጢጢዬ “ሞባይሎች” (Finger top computers) መተካት ሲጀምሩ ደግሞ “ቁርጡን እውቁት” እንዲሉ “ዓለም በሁለት ጣታችን ወጥመድ ውስጥ ገብታለች” እየተባለ ቴክኖሎጂው “መመለክ” ጀመረ:: ለወደፊቱስ ምን ይፈጠር ይሆን? እንጃ:: ለጊዜ ጊዜ ሰጥተን የሚመጣውን መጠበቁ ይበጅ ይመስለናል::
የእኛ የሶምሶማ እርምጃና የቴክኖሎጂው የፍጥነት ሽምጥ፤
ቴክኖሎጂው ለእኛ ብቻም ሳይሆን ለራሷ ለትልቋ ዓለማችን ዜጎች ጭምር “በረከተ መርገም” መሆን ከጀመረ ውሎ አድሯል:: ወይንም ቀለል አድርገን ሃሳቡን በብሂላችን እናጎላምሰው ካልን ቴክኖሎጂው ለእኛ “ላም እሳት ወለደች፤ እንዳትልሰው ፈጃት እንዳትተወው ልጅ ሆነባት” ይሉት ብጤ ሆኖብናል:: “ያለቴክኖሎጂው መኖር እንደማይቻል፤ ከቴክኖሎጂውም ጋር መኖር እንደሚያዳግት” ከተረዳን ሰነባብቷል:: ቢቸግረን በዕለት ተዕለቱ ንግግራችን ሳይቀር ባይተዋርነታችንን የተቋቋምን እየመሰለን “ዲጂታል ኢትዮጵያን እንፈጥራለን” በማለት መፈክር ማሰማት የጀመርነውም በቅርቡ ነው::
ለማሳያነት እንዲረዳን ከሰባት ዓመታት በፊት የተፈጸመን አንድ እውነታ እናስታውስ:: አንጋፋውና የአገር ኩራት የሆነው የአየር መንገዳችን ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ሙሉ ለሙሉ ሥራችንን የምናቀላጥፈው “በዲጂታል ቴክኖሎጂ ነው” በማለት ማረጋገጫውን ለኢትዮጵያ ሕዝብ ይፋ ለማድረግ የሞከሩት በሚዲያ ሠራዊት ተከበው “ወረቀት ሰብስበው በእሳት በማቀጣጠል” ምሳሌያዊ ድራማ በመተወን ነበር::
በዚያ ወቅት የተፈጠረብንን አገራዊ እፍረትና መሸማቀቅ ለመግለጽ የሞከርነው “ከሰደበኝ ይልቅ መልሶ የነገረኝ ገደለኝ” የሚለውን ብሂል በማስታወስ በወረቀት ላይ የዘመቱትን ኃላፊዎች ብቻ ሳይሆን ዜናውን የዘገቡትን ጋዜጠኞች ጭምር “ይብላኝላችሁ!” ብለን መታዘባችን አልቀረም:: የንባብ ባህላችን በእንፉቅቅ እየሄደ ባለበት ወቅትና ከማንበብና ከመጻፍ ባይተዋርነት ገና ሳንላቀቅ ያን የመሰለ ተግባር መፈጸሙ እጅጉን አሳዝኖን እንደነበርም ማስታወሱ አግባብ ይሆናል::
እንደ እውነቱ ከሆነ ከሰባት ዓመት በኋላ “የምናከብረው አየር መንገዳችን” ዛሬም ድረስ የወረቀት አገልግሎቱን ሙሉ ለሙሉ ማቆም ስለመቻሉ በግልጽ ቢነግረን “ቃሉን ጠብቋል” ብለን እናሞግሰዋለን:: እኛን ያስከፋን ቴክኖሎጂውን ለማስበለጥ ስለምን ወረቀት ሊኮነን እንደቻለ ግራ ስለገባን ነበር::
“ዓለም በርግጥም በሁለት ጣቶቻችን ውስጥ ገብታ” ክፉም ይሁን ደግ የፈለግነውን መረጃ፣ እውቀትም ሆነ “ዝባዝንኬና አይረቤ” ጉዳዮችን በቀላሉ በጣቶቻችን ለመፈልፈልና ለማግኘት በሚቻልበት በዚህ ወቅት ማናችንም ባይተዋር አልሆንም ማለት የዋህነት ነው:: በርካታ የዘርፉ ባለሙያዎችና በአመራር ላይ ያሉ ግለሰቦች ሳይቀሩ የዛሬ ስድሳ ዓመቱን ብሂል ደግመው ደጋግመው እየከለሱና እየደገሙ “ዓለም እንደ ትንሽ መንደር ጠባለች” ሲሉ ሳናደምጥ የቀረን አይመስለንም:: ዓለም ከመንደርነት እጅግ አንሳና ጠባ በሁለት ጣቶቻችን ውስጥ መግባቷን እንኳን በአግባቡ መረዳት እንደተሳነን ጥሩ ማሳያ ሊሆን ይችላል::
የሰሞኑ ፈተናችን፤
ባይተዋርነታችንን አጉልቶ ያሳየንን የሰሞኑን አገራዊ ፈተናችንን በተመለከተ ጥቂት ዳሰሳ እናድርግ:: ሰሞኑን በዲጂታል ቴክኖሎጂ የተጀመረው የነዳጅ ግብይት ጉዳይ አዲስ አበቤን እንዴት እያመሰው እንዳለ የምናስተውለው ነው:: ቴክኖሎጂውን በአግባቡ መጠቀም የሚበረታታ ብቻ ሳይሆን ለአገር የሚጠቅም ትሩፋት ካለው ውሳኔውን የምንቀበለው በደስታና ሃሌ ሉያ እያልን በመዘመር ጭምር እንደሆነ ይታወቅልን:: መንግሥታዊው ውሳኔ በርግጥም በኮንትሮባንድ የሚፈጸመውን የነዳጅ ሽሽት እግር ከወርች የሚያስር ከሆነና ከመንግሥት ካዝና ይወጣል የተባለውን የድጎማ ድጋፍ የሚቀንስ ከሆነ ከዝማሬም ከፍ አድርገን ውሳኔው ፈጥኖ እንዲተገበር ጸሎትም ብናክልበት ባልከፋ ነበር::
ችግሩ የተፈጠረው ውሳኔውና ባይተዋርነታችን ሆድ እና ጀርባ መሆናቸው ላይ ነው:: እንደማሳያ አገራዊ ኢንተርኔት አገልግሎቱን ማንሳት ይቻላል፤ በዚህ አካባቢ የሚታየው ችግር የክፍያ ሽግግሩ ዋነኛ ተግዳሮት እንደሆነ ነው። በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በኩል ዲጅታል የፋይናንስ አገልግሎት ለማግኘት “ኔት ወርክ ስለሌለ ነው” በሚል ምክንያት በየአገልግሎት ተቋማት እንግልት ያልቀመሰ ዜጋ ይኖር ከሆነ በዕድለኛነት ቢፈረጅ አይበዛበትም::
በአንዳንድ ቦታ ኢትዮ ቴሌኮም ካበለጸገው የቴሌ ብር ውጪ በዲጂታል ክፍያ መፈጸም አይቻልም እየተባልን እንግልት ውስጥ ነን:: ማስረጃ ካስፈለገ ኢሚግሬሽን መ/ቤት ጎራ ማለት ብቻ በቂ ይሆናል:: ልክ እንደ ዘመነ ሶሻሊዝም የግብይቱን ሥርዓት ለአንድ ወይንም ለሁለት መንግሥታዊ ድርጅቶች ብቻ ሰጥቶ ሕዝብን ማማረርስ መንግሥታችን ሆይ ደግ ይሆናል?
ለማንኛውም ቴክኖሎጂው ባይተዋር ያደረገን ለዲጂታል ግብይቱ ብቻ አይደለም:: ልጆቻችንን (ወላጆችንም ይመለከታል) ከመጻሕፍት ንባብ ጋር አቃቅሮ ባይተዋር ካደረገን ሰነባብቷል:: በአጭሩ ትውልዱ ለመጻሕፍት ባይተዋር ሆኖ የቴክኖሎጂው ምርኮኛ ሆኖ አንዳይቀር የተጠናከረ ምክክር ያስፈልግ ይመስለናል:: በዚህ አጋጣሚ መንግሥት ከሳይንስ ሙዚዬም አስቀድሞ ለአብርሆት ቤተ መጻሕፍት ግንባታ ቅድሚያ ሰጥቶ ስላስደሰትን እንደ ካሁን ቀደሙ ደጋግመን ከማመስገን አንቦዝንም::
ቴክኖሎጂው የቤተሰብ እሴታችንን ሸርሽሮም እሥረኛ ማድረጉ ሌላው የተጋረጠብን አደጋ ነው:: መደበኛ ሥራችንን በአግባቡ እንዳንከውንም ይሄው መዘዘኛ ቴክኖሎጂ ባይተዋር በማድረግ ሸብቦናል:: እውነትን ከሀሰት ለመለየትና ከኅሊናችን ጋር እንዳንቆምም በብዙ ጉዳዮች ባይተዋር አድርጎ ከጠፈነገን ዓመታት ተቆጠረዋል:: እንዲያው መጨረሻችን ምን ይሆን? በቴክኖሎጂው ሱስ የተማረኩብን የልጆቻችን የወደፊቱ ዕጣ ፈንታስ በምንና እንዴት ይወሰን ይሆን? ግራ ተጋብተናል::
ትንታግ ብዕሩን እየዘከረለት ታሪክ አግዝፎ የሚያከብረው ያ “የኮሌጅ ቀን” ገጣሚ ኃይሉ ገ/ዮሐንስ (ገሞራው) የዓለማችንን የቴክኖሎጂና የሥልጣኔ ፈረ ቀዳጆች “በበረከተ መርገም” ግጥሙ ልክ ልካቸውን እንደነገረልን ሁሉ ምነው የእርሱ መንፈስ የተጋባበት ብዕር-ወራሽ በእርሱ እግር መተካት ተሳነው ብለን መቆጨታችን አልቀረም:: ይህንን ያሳበደንንና ባይተዋር ያደረገንን ዘመነ ቴክኖሎጂ ማን ገርቶልን እንዴት ሊለዝብ እንደሚችል መጨረሻው ናፍቆናል:: ሰላም ለሕዝባችን፤ ለዜጎችም በጎ ፈቃድ::
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ግንቦት 2/2015