ወቅቱ የአገሬ አርሶ አደር እረፍት አጥቶ ከአፈር የሚታገልበት፤ ሞፈር ቀንበሩን አዋድዶ ከበሬው ትከሻ የሚያኖርበት ነው። በድካሙ ውጤትም የአመት ቀለቡን የዕለት ጉርሱን የሚችልበት፤ ልጅ ለማስተማር፣ የታመመ ለማሳከም የሚያስችለውን እህል ሳይቸገር ወደ ገበያ ለማውጣት እንዲችል ጎተራውን ለመሙላት ጠንክሮ የሚሠራበትም ነው። በመሆኑም ያለንበት የበልግ ወቅት አርሶአደሩ በአንድ በኩል በዚህ መልኩ ለጎጆው መሙላት፤ በሌላ በኩል ከተሜውን ለመቀለብ የሚውል ምርትን በስፋት ለማምረት ብርቱ ትግል የሚያደርግበት፤ ለመኸር ወቅት የእርሻ ዝግጅት የሚያደርግበትም ወቅት ነው። በጥቅሉ ወቅቱ ለአርሶአደሩም፣ ለኢትዮጵያም የምርታማነት መግቢያ በር ነው ማለት ይቻላል።
ይሁን እንጂ ይሄ አርሶአደር ለዘመናት በተደራረቡ ችግሮች ውስጥ ቆይቷል። በተፈጥሮ ከሚደርሱት ድርቅ ጎርፍና መሬት መንሸራተት፣ አንበጣና ሌሎችም በሰው ሰራሽ ችግሮች ተፈትኗል። በተለይም በሰላም እጦት ክፉኛ ሲፈተን ኖሯል። የ2010ሩን አገራዊ ለውጥ ተከትሎ በተፈጠሩ ለውጥን ያለመቀበል እሳቤዎች ምክንያት ደግሞ ባለፉት አምስት ዓመታት በተለይም ባለፉት ሦስት ዓመታት በብዙ የአገራችን ክፍል ላይ ያለው አርሶአደር የሰላም ችግር ክፉኛ ፈትኖታል። በያዝነው አመትም የተፈጥሮው ችግር ጋብ ያለ ቢሆንም፤ ከሰዎች የአስተሳሰብ ልኬት የሚመነጨውና በጽንፈኝነት የሚዘወረው ሰላምና አለመረጋጋት ግን አሁንም በሚፈለገው መልኩ እልባት ያገኘ አይመስልም።
በተለይም በሰሜኑ የአገራችን ክፍል እና በምዕራብ ኦሮሚያ ለሚገኙ አርሶ አደሮች ባለፉት አመታት በሰላም መደፍረስ የአካልም የህሊናም እረፍት ያጡበት ወቅት እንደነበር ለሁላችንም ግልጽ ነው። በዚህም የተነሳ ከራሱ አልፎ ለሌላ የሚተርፈው ጥቂት የማይባል አርሶአደራችን እጁን ለምጽዋት እንዲዘረጋ የሚያስገድድ ሁኔታ ተፈጥሮበታል። ይሄ ደግሞ አርሶአደሩን ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያ እንደ አገር፣ ኢትዮጵያውያንም እንደ ሕዝብ ዋጋ የከፈሉበት ነው። ራሳችን በፈጠርነው ችግር ለረሀብና ለመፈናቀል የዳረገነውን አርሶአደር እንኳን በተዘረጋው እጁ ልክ መታደግ አልቻልንም።
ይህ እንደተጠቀ ሆኖ ግን መንግሥት ለግብርናው ዘርፍ በሰጠው ልዩ ትኩረት ሰላም ባለባቸው አካባቢዎች በኩታ ገጠምና ሜካናይዜሽን በመታገዝ አኩሪ ውጤት ተመዝግቧል፤ ትርፍ ማምረት በመቻሉም ስንዴን ለውጭ ገበያ ማቅረብ ተችሏል። ሆኖ ከሰሞኑ እየሰማናቸው ያሉ አንዳንድ ዜናዎች የመንግሥትንም ህልም የአርሶአደሩንም ልፋት እንዳያጨልሙ፤ ለአገርም የልማት ግስጋሴ እንቅፋት እንዳይሆኑ ትልቅ ስጋት አለኝ። ምክንያቱም፣ ዘንድሮ ዝናቡም ጥሩ ሆኖ፤ የማዳበሪያና የምርጥ ዘር አቅርቦትን ለማሟላትም መንግሥት ደፋ ቀና እያለ ባለበት፤ አርሶአደሩም ከጦርነት ዜናና ሰቆቃ ተላቅቆ መልካም አጋጣሚውን ተጠቅሞ ደፋ ቀና በሚልበት በዚህ ጊዜ፤ በአንዳንድ አካባቢዎች እየተከሰተ ያለው ነገር ግን ዛሬም እንደ ትናንቱ አርሶአደራችንን ለከፋ ሰቀቀን የሚዳረግ እንዳይሆን ነገ ሳይሆን ዛሬ ጥንቃቄ ልናደርግ ይገባል።
«አንድ ሰኔ ያጠፋውን አስር ሰኔ አይመልሰውም» እንዲሉ፤ አንድ ገበሬ የአንድ አመት ምርቱን ሲያጣ የሚጎዳውም የሚቀጣውም በሚበላው ብቻ ሳይሆን አመት ሙሉ በሚኖረው ሕይወቱ ነው። የልጆች ትምህርት ቤትና ቀለብ … ግብር… የእንስሳት መኖ … የማህበራዊና ሃይማኖታዊ ክዋኔዎች ብቻ … ብዙ ነገሮችን በሕይወቱ ለማጣት ይገደዳል። ከምንም በላይ ደግሞ ለአመታት ተንከባክቦ ያሳደጋቸው ልጆቹን ሲያጣ ሊሰማው የሚችለውን ነገር መገመት ለማንም የሚከብድ አይሆንም።
አሁን እየሆነ ላለው ነገር እኛ ኢትዮጵያውያን ከራሳችን ችግር ውጪ ማንም ላይ ጣታችንን የምንቀስርበት ወቅት አይደለም። በትንሹ የውጭ ጣልቃ ገብነት እንዳለ እንኳን ብናምን በሩን ወለል አድርገን የከፈትነውም፤ እየከፈትን ያለነውም እኛው ራሳችን መሆናችንን መገንዘብ አለብን። ከዚህ አንጻር ሰላም ለሁላችንም ከምንም በላይ የሚያስፈልገን ቢሆንም፤ በዚህ ወቅት ግን ከማንም በላይ አርሶአደራችን፤ በጥቅሉም ለኢትዮጵያችን ምርታማነት ያስፈልጋል፤ የጦርነት እረፍት ያሻቸዋል። ስለዚህ ከየትኛውም ጥያቄያችን በፊት ለሰላም የሚዘረጋ እጅ ሰላም የሚሻ ልቡና ያሻናል።
እዚህ ላይ ጥያቄ አይኑረን ልዩነት አይፈጠር እያልኩ አይደለም። ምንም ጥያቄ… ምንም ልዩነት… ቢኖረን የነገራችን አልፋና ወኦሜጋ ሰላም ይሁን እያልኩ ነው። ይህም ሆኖ «የእኔን መኪና ካለመካኒክ ማንም እንዳይነዳት» እንዳሉት አባት ችግራችንን ብቻ ሳይሆን ያለንበትን ወቅታዊ ሁኔታ የሚመጥን አመራርን መከተል እንደሚጠበቅብን ይሰማኛል። ይሄን ለመገንዘብ «የእኔን መኪና ካለመካኒክ ማንም እንዳይነዳት» ያሉትን አዛውንት የሃሳብ መነሻ ልጠቁም፤ አዛውንቱ አብራቸው ያረጀች የድሮ ስሪት ኦልድ ሞዴል መኪና አለቻቸው።
የእርሳቸው እርጅና ከመኪናቸው ይቀድምና ማሽከርከር በማቆማቸው ወደፈለጉበት እንዲያደርሳቸው ለሹፌር ይሰጧታል። ሹፌር ከያዛት በኋላ ግን መኪናዋ ከወትሮው በተለየ መልኩ ወደጋራዥ መመላለስ ታበዛለች። የመጀመሪያ ሰሞን የችግሩ መደጋገም የመኪናዋ ዕድሜ መጨመርና የመለዋወጫ ዕቃ ጥራት መጓደል እየመሰላቸው ችግሩን ተቀብለውት ነበር። ሰንበትበት ሲሉ ግን አንድ ነገር ለማስተዋል ቻሉ። መኪናዋን ያደሳት መካኒክ ለሙከራ ሲነዳት ምንም ድምጽ አይፈጠርም ምንምም ችግር አይኖርም። ጣጣ የሚፈጠረው ሹፌር ሲይዛት ብቻ ነው። አዛውንቱ ይህንን ካስተዋሉ በኋላ ነገሩን ለመረዳት ጊዜ አልወሰደባቸውም።
ችግሩ ሁሉ የሚፈጠረው መኪናዋን የሚያሽከረክሯት ሹፌሮች የሚጠቀሙት አካሄድ በትምህርት ያገኙትን እውቀትና በሌላ መኪና የለመዱትን ብቻ ነው። መካኒኩ ግን በዚያ ረጅም ዘመን ባሳለፈ ዕድሜዋ ውስጥ መኪናዋ የተፈጠሩባትን ችግርች ከማንም በላይ ይረዳል። ስለዚህ መቼ ምን እንዴት ማድረግ እንዳለበት ያውቃል። ስትደክም ይታገሳታል፤ ቦታና ጊዜ ይመርጥላታል። ባጭሩ የሚጠበቅባትን ሳይሆን የሚጎድላትንም ይረዳታል።
ስለዚህ መኪናዋ እና መካኒኩ ሲገናኙ መንገድ ሊቀየር ፍጥነት ሊቀንስ ይችላል እንጂ ጉዞ አይቋረጥም። ዛሬ ኢትዮጵያችንም ለእኔ እንዲሁ ናት!። ብዙ አልፋለች፤ ብዙም አሳልፋለች። በመሆኑም ይህንን ታሪኳን፣ አሁን ያለችበትን ነባራዊ ሁኔታ፣ የሕዝቧን ሰቀቀንና የነገ ተስፋ በአግባቡ የሚረዱ መሪዎችም፤ ዜጎችም ያስፈልጓታል።
በመሆኑም ዛሬ እኛ ኢትዮጵያውያን የራሳችንን ችግር ብቻ የምናዳምጥበት… ፍላጎታችንን ብቻ የምንጠይቅበት እኛ ብቻ ተበደልን ብለን የምንጮህበት ሊሆን አይገባም። እኛ እንደምንጠይቀው ሁሉ ብዙ ወገኖቻችንም የየራሳቸው ጥያቄ እንዳላቸው ብዙ ዜጎች ብዙ ተበደልን የሚሉት እንዳላቸው ልንረዳ ይገባል። በአንጻሩ የአገራችን ነባራዊ ሁኔታ ደግሞ የሁላችንንም ጥያቄ በአንድ ጀንበር ለመመለስ የሚያስችል አይደለም። ከፖለቲካ እስከ ኢኮኖሚ ብዙ ምስቅልቅል ነገሮች አሉብን። በዚህም የተነሳ ሁሉም ነገር ጊዜና ትእግስት ይሻል።
ከምንም በላይ ከራሳችን በላይ ለአገራችንና ለሕዝባችን በተለይ ሳይማር ላስተማረን ሳይበላ ለሚቀልበን ሰላም እንደ ውሃ ለናፈቀው አርሶአደር ልናስብለት ይገባል። ይህ እንዲሆን ደግሞ ጦርነት በቃን፤ ከዚህ በኋላ ጥይት እንኳን በዶላር ገዝተን ይቅርና የምናመርት እንኳን ቢሆን ድምጹን መስማት አንፈልግም። እንኳን የኢትዮጵያ ሕዝብ የአገራችን ተራሮችና ወንዞች ሳይቀሩ የጥይት አረር ሽታ ሰልችቷቸዋል።
እዚህ ቦታ መንገድ ተዘጋ፤ እዚህ አካባቢ መኪና ተቃጠለ … የሚል ወሬ ከዚህ በኋላ መስማት አንፈልግም። መስማትም ማየትም የምንሻው በእርሻ ማሳ ላይ የተሰማራ ትራክተር ድምጽ እንጂ፤ በምሽግ ውስጥ የሚጮህ ክላሽ አይደለም። ምክንያቱም አርሶአደሩ እንደ ሕዝብም አገርም ቀላቢ፤ አገርም እንደ ሕዝብ አበልጻጊ አውድነታቸው ያመርቱ ዘንድ ከጦርነት ማረፍና ሰላም ያስፈልጋቸዋል።
በጋዜጣው ሪፖርተር
አዲስ ዘመን ግንቦት 1/2015