የሰው ልጅ ትልቁ ፍላጎት ሰላም ነው። እንደፍላጎቱ የሆነለት ግን የለም። ለዘመናት በጦርነትና በእርስ በርስ ግጭቶች ዋጋ ሲከፍል የኖረ ነው። እውነትና ሚዛናዊነትን ባስቀደመ መልኩ ጠብ ጫሪዎች ሲቀጡና ተጎጂዎች ሲካሱ የሚያሳይ ሥርዓት እምብዛም ነው።
ይሄን የፍትህ ጥያቄ ለመመለስና ተጠያቂነትን ለማስፈን ከሚሠሩ የፍትህ ፖሊሲዎች መካከል የሽግግር ፍትህ ሥርዓት ቀዳሚው ነው። የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ አሁን ላለችው ኢትዮጵያ ከመቼውም ጊዜ በላይ አስፈላጊ የሆነበት ወቅት ነው። በጦርነትና ማንነትን መሠረት ባደረጉ አለመግባባቶች የደረሱብን በደሎች ከትናንት ወደ ዛሬ የመጡ አገራዊ ገበናዎቻችን ናቸው። እነዚህ ገበናዎቻችን እንዲታከሙ ተጠያቂነትን መሠረት ያደረገ የፍትህ ሂደት አስፈልጓል።
በዓለም ላይ በብዙ አገራት የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ተግባራዊ ተደርጓል። ከእርስ በርስ ጦርነት፣ ከግጭትና ከብሔር ፖለቲካ እንዲሁም በፖለቲካና በዴሞክራሲ ግንባታ ሂደት ላይ ትርጉም ያለው ውጤት ያመጡ አገራት ጥቂት የሚባሉ አይደሉም። የትግበራ ሂደቱ ሰላምና ተጠያቂነትን ከማስፈን አንጻር እውቅና የተሰጠው ሲሆን የተባበሩት መንግሥታትን ጨምሮ በአፍሪካ ኅብረት በኩል ይሁንታን ያገኘ የተሀድሶ ንቅናቄ ነው።
በ2011 ዓ.ም በመዲናችን አዲስ አበባ የጸደቀው የአፍሪካ ኅብረት የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ማዕቀፍ አገራት የተለያዩ የፖሊሲ እርምጃዎችን እና ተቋማዊ አሠራሮችን በመጠቀም የመብት ጥሰቶችን ጨምሮ ክፍፍሎችንና አለመግባባቶችን እንዲሁም ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ለውጥ ለማምጣት አስፈላጊ ሂደት እንደሆነ ገልጸዋል።
ሁለተኛውን የዓለም ጦርነት ታትኮ መነቃቃት የጀመረው የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ተዓማኒነትና ይሁንታን አግኝቶ በተለያዩ የዓለም አገራት በተለያየ ይዘት ተግባራዊ ተደርጓል። ፍትህንና ተጠያቂነትን እንደመርህ አንግቦ ሲንቀሳቀስ የነበረው የፍትህ ሥርዓት ለብዙዎች የነፃነት እና የዴሞክራሲ ጥያቄ መልስ የሰጠ ሆኗል።
ባለፈው ጊዜ በአገራችን ኢትዮጵያም በተለያዩ ጊዜያት የሽግግር ፍትህ ሂደት አላባዎችን ተግባራዊ ለማድረግ ሙከራ ተደርጓል። ነገር ግን፣ ከስልቶቹ በተጨማሪ አላማና ግቡን የሚቃኝ የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ በበቃና በነቃ መልኩ ስላልነበር የሚፈለገውን ውጤት ማምጣት አልተቻለም።
ከዚህ ልምድ በመነሳት፣ ዓለም አቀፍ ተሞክሮዎችን እና ሂደቶችን ባገናዘበ መልኩ ያሉና የነበሩ፤ ወደ ፊትም የሚኖሩ ፖለቲካዊና ማህበራዊ ችግሮቻችንን ለመቅረፍ እንደአዲስ እየተንቀሳቀስን ያለንበት ሂደት ነው ያለው። ይህ አላማ እንደ አገር ግቡን እንዲመታና የሚፈለገውን የፍትህና የተጠያቂነት ውጤት እንዲያመጣ ጥናት ባደረጉ ባለሙያዎች የመነሻ ጽሑፍ ተዘጋጅቶ ውይይት ተደርጎበታል።
ውይይት ከተደረገባቸው የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ አማራጮች መካከል መጀመሪያ ላይ የተቀመጠው የሽግግር ፍትህን ታሪካዊ አመጣጥ እና አገራችን ካለችበት ወቅታዊ ችግር አንጻር የፖሊሲውን አስፈላጊነት የሚቃኝ ነው። ቀጥሎ በባለሙያ ውይይት የተደረገበት ምክረ ሀሳብ የሽግግር ፍትህ ፖሊሲን በተመለከተ በአገራችን ያሉትን አማራጮች እና ምክረ ሀሳቦች ያቀፈ ሲሆን በመጨረሻም የፍትህ ፖሊሲው ሊመራባቸው የሚገቡ መርሆችና የአደረጃጀት አማራጮችን የቃኘ ነበር።
ሦስቱን የመወያያ ሀሳቦች ብንመለከት አሁን ላሉብንም ሆኑ ወደ ፊት ለሚፈጠሩብን ችግሮች የመፍትሄ አካል ሆነው እናገኛቸዋለን።
በተደጋጋሚ እንደ ጠቀስነው፣ የሽግግር ፍትህ አስፈላጊነት የሚያጠያይቅ ጉዳይ አይደለም። በተለይ እንደ እኛ አገር ባሉ፣ ብሔርን መሠረት አድርገው ለሚነሱ ግጭቶችና አለመግባባቶች ከዚያም አለፍ ሲል በፖለቲካው በኩል ለምናየው የመብት ጥሰት ተጠያቂነትን የሚያሰፍን ሆኖ እናገኘዋለን።
የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ተጠያቂነትን ከማስፈን አንጻር «የተሻለ» ያለውን አማራጭ ይዞ ብቅ ባለበት በዚህ ሰሞን በበዳይና በተበዳይ መካከል ሚዛናዊ ዳኝነትን ይሰጣል ተብሎ ይታመናል። ከዚህ በፊት በነበረው ሥርዓት ክስና ቅጣት ላይ የተመሠረተ አሠራር ሲኖረው ይህን ተግባር እንዲያቀላጥፉ ጊዜያዊ ፍርድ ቤቶችና ዓለምአቀፍ ተቋማት የተቋቋሙ ሲሆን፣ ይህ ዓይነቱ አጥፊዎች ላይ ብቻ የተመሠረተው የፍርድ ሂደት መሠረታዊ ጉድለት እንዳለው በመረዳት አዲስ አሠራር መከተልን ግድ ብሏል።
አጥፊዎች ላይ ብቻ በማተኮር አገር ለማዳን፣ ዴሞክራሲ ለመገንባት አለመቻላቸው፣ ስለሕግ ጥሰቱ በቂና መረጃን መሠረት ያደረጉ ማስረጃዎችን አለማዘጋጀታቸው ከዚህ ከፍ ሲልም ማህበረሰቡን የመከታተል አቅማቸው ውስን መሆኑ አዲስ አቅጣጫን እንዲከተሉ አስገድዷቸዋል።
ከዚህ ጎን ለጎን ሌሎች መሠረታዊ ጉድለቶችንም መጥቀስ ይቻላል። ሁሉንም አጥፊዎች ለፍርድ ማቅረብ የማይቻል መሆኑና የተወሰኑትን ብቻ የሚቀጣ የፍትህ ሥርዓት በመሆኑ የተሻሉ አማራጮችን እንዲያይ ዕድል ፈጥሮለታል። ክስ ላይ ብቻ የተመሠረተው የፍትህ ሂደት ከክስና ከቅጣት ከካሳም ባሻገር ለዘላቂ ሰላምና ለዴሞክራሲ ግንባታ ቅድሚያ የሚሰጥ ዘመናዊ አሠራርን ይዞ ብቅ ብሏል።
ከዚህ በኋላ ባለው የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ማዕቀፍ የምንዳኘው እንዳለፈው ጊዜ ቅጣት ላይ ብቻ ሳይሆን ምሉዕ በሆነና ይሁንታን ባገኘ የፍርድ ሂደት በኩል ነው። እንደ አዲስ በሥራ ላይ የዋለውና በብዙዎች ዘንድ ተቀባይነት ያገኘው የፍርድ ሂደት እውነትን መሠረት አድርጎ የሚጀምር እና በዚያ እውነት መሠረት እርቅና ካሳ፣ ቅጣትና ተጠያቂነት የሚቀጥሉበት አሠራር ነው።
በአገራችን የነበረውን የሽግግር ፍትህ ተሞክሮ ብዙ ጥያቄዎች የሚነሱበት እንደነበር የሚታወቅ ነው። ሂደቱ ነበረ፤ ይሁን እንጂ ሂደቱ እንደመነሻ አላማው የሚፈለገውን ለውጥ ያመጣ አልነበረም። በጦርነት እና በፖለቲካ ሽኩቻ፤ በመሰል ሁኔታዎች የተነሱ በደሎችንና ጭቆናዎችን፣ ጥያቄዎችንና የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን አይቶና መርምሮ እውነትን መሠረት ባደረገ መንገድ ፍትህንና ተጠያቂነትን፤ እንዲሁም፣ ከዚያ አለፍ ሲል በእርቅና በምህረት ላይ ተመስርቶ የሚንቀሳቀስ አልነበረም።
ያለፉ የፖለቲካ ሥርዓቶቻችንንና በሕዝብ ላይ ያደረሱትን መጠነ ሰፊ የመብት ጥሰት ብናነስ የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ከስም የዘለለ ምንም እንዳልነበር እንደርስበታለን። ያለፉትን ስልሳ አመታት የፖለቲካ ሂደት ብናስተውል ሥልጣን የተያዘውና ከሥልጣን የሚለቀቀው በብዙ ሞትና በብዙ የመብት ጥሰት በኩል ነበር።
የአጼው ሥርዓት ያበቃው በመንግሥቱ ኃይለማርያም በተመራ የደርግ መንግሥት ነበር። ደርግ ኃይለሥላሴን ገፍትሮ ወደ ሥልጣን ሲወጣና ከወጣ በኋላም የታሠሩትንና የተረሸኑትን እንዲሁም ደብዛቸው የጠፋን ባለሥልጣናት ትተን በሕዝብ ላይ ብዙ በደሎችን ፈጽሟል።
ከደርግ በኋላ የመጣው ኢህአዴግም የደርግ መንግሥትን ተጠያቂ ለማድረግ በ1983 ዓ.ም የሽግግር መንግሥት የመሠረተ ሲሆን፣ ሕግና መርህ ያልተከተለ እንደነበር ይተቻል። የሽግግር ፍትህ ፖሊሲው እንዲተች ያደረገው ዋናው ነገር ከላይ ከፍ ብዬ እንደገለጽኩት እውነትን መሠረት ያላደረገ መሆኑና እርቅና ምህረትን ያላካተተ ከመሆኑም በተጨማሪም ብዙኃኑን ማኅበረሰብ ትቶ ባለሥልጣናት ላይ ብቻ ማተኮሩ እንደሆነ ይነገራል።
ከዚህ ባለፈ እንዳለፈው መንግሥት ሁሉ የኢህአዴግም መንግሥት በመብት ጥሰት ስሙ ከመነሳት አልዳነም። አሁን ያለው መንግሥትም ፍጹምና እንደሌለው አንድ ፓርቲ በሽግግር ፍትህ በኩል የሚታይ ሙገሳና ወቀሳ ይጠብቀዋል ባይ ነኝ። ፖለቲካችን ጠርቶ አያውቅም።
በብሔር ስም መነሻውን ያደርግና መድረሻውን በሕዝብ እንባ ይደመድማል። ባልጠራ ፖለቲካ ውስጥ የመብት ጥሰት ሁሌም አለ። የሽግግር ፍትህ ያስፈለገበት አንዱና ዋናው አላማ ደግሞ ባልጠራ ፖለቲካ ውስጥ የተፈጸሙና የሚፈጸሙ የመብት ጥሰቶችን መመርመርና ፈትሾ ተጠያቂነትን ማስፈን ነው።
የቅርብ ጊዜ ትውስታችን የሆነው በ2010 ዓ.ም በአገራችን የተፈጠረውን የፖለቲካ ለውጥ ተከትሎ የመጣው የሽግግር ፍትህ እሳቤ ነው። ገዢው ፓርቲ ያለፉ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች፣ ማንነትና ዘርን መሠረት ያደረጉ ቁርሾዎችና መገፋፋቶች በእውነት ሚዛን ላይ አርፈው በእርቅና በፍትህ በዳይ እንዲጠየቅ፤ ተበዳይ እንዲካስ እውነት መር በሆነ የፍትህ ሂደት ሰላም እንዲሰፍን የሽግግር ፍትህ ርምጃዎችን እንደወሰደ አይዘነጋም።
ከዚህ ከፍ ባለ መልኩ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ብርቅ የሆነና ተሰምቶ የማይታወቅ የይቅርታ ድምጽ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ አንደበት ተሰምቷል። «ላጠፋነው ጥፋት ሁሉ ይቅርታ እጠይቃለሁ» ሲሉ በትናንት ፖለቲካ ውስጥ የነበረውን በማስታወስ ይቅር በሉኝ ብለዋል።
ይሄን የይቅርታ ድምጽ ተከትሎ የእርቀ ሰላም ኮሚሽን ተቋቁሟል። የሰላም ሚኒስቴር ተመስርቷል። እንዲሁም፣ ለውጥ የሚያመጡ የሕግና የተቋማት ማሻሻያዎች ተደርገዋል። በዚህ ሁሉ ሂደት ውስጥ ግን እንደ አገር የሚጠበቅብንን ለውጥ አላመጣንም። ዛሬም የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ስንል ዳግመኛ በምክረ ሀሳብ መጥተናል።
ካለፉት ስህተቶቻችን ተምረን በዚህ የሽግግር ፍትህ ጅማሪ ተጠያቂነትን ማስፈን የመጨረሻ ዕድላችን ቢሆን እመኛለሁ። በአገራችን እንደችግር ከሚነሱ ጉዳዮች ውስጥ አንዱ ጀምሮ ማቆም ነው። እንደ አጀማመራችን የጨረስነው የለንም። የሽግግር ፍትህ አሁን ለሦስተኛ ጊዜ መነሳቱ ነው።
እንደ አጀማመራችን ፍጻሜ ላይ የበረታን ቢሆን ኖሮ ከማንም ቀድመን ለውጥ የምናመጣ ሕዝቦች እንሆን ነበር። አብዛኞቹ ጉዳቶቻችን ጀምረን ካቆምናቸው ጉዳዮች የተሳቡ ናቸው። ችግርን በዘላቂነት ለመፍታት መጀመር ጥሩ ሆኖ ሳለ የሚፈለገው የሚገኘው ግን በመጨረስ ውስጥ ነው።
ሌላውን ትተን ለአገራችን የመጀመሪያ የሆነውን እና ብዙ ችግሮቻችንን ይቀርፍልናል ስንል እምነት የጣልንበት «የእርቀ ሰላም ኮሚሽን» እንኳን ካለምንም ትግበራ ተስፋችንን ይዞ የሥራ ዘመኑ አብቅቶ እንዲፈርስ ተደርጓል። ከተሰጠው ኃላፊነትና የሥራ ድርሻ አንጻር መፍትሄ እንደሚያመጣ የታመነበት ቢሆንም የሚጠበቅበትን ሳያደርግ እውቅናውን ተነጥቋል።
በተደጋጋሚ እንዳወራነው የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ክስን፣ እርቅን፣ ምህረትን፣ እውነትን፣ ተጠያቂነትን፣ ካሳን፣ ዴሞክራሲን፣ ፍትህን፤ እንዲሁም፣ መሰል ሁኔታዎችን ያካተተ የፍትህ ሥርዓት ነው። የሽግግር ፍትህ ተግባራዊነት ከሚጠይቃቸው አማራጮች መካከል ታሪካዊ ሁነቶች እንዳሉ ሆነው ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ አውዶች ከፊት ይሰለፋሉ።
አገራችን በአሁኑ ሰዓት በሽግግር ፍትህ እሳቤ ውስጥ ናት። አሁን ላሉብን ወቅታዊ ችግሮች የትኛውን የሽግግር ፍትህ ስልት ብትጠቀም ይበልጥ ውጤታማ ትሆናለች የሚለው ጥያቄ ለውጤታማነቱ የአንበሳውን ድርሻ የሚወስድ ነው። ከፍ ብለን እንዳየነው የፍትህ ሥርዓቱ ራሱን የቻለ የትግበራ ሂደት ያለው ነው።
በሽግግር ፍትህ ሂደት ውስጥ ተጠያቂነትን ለማስፈን እውነትን ማፈላለግና ይፋ ማውጣት ቀዳሚው ርምጃ ነው። እውነትን መሠረት ባደረገ ሂደት ቀጣዩ ክስ ነው። ከዚህ ሂደት በኋላ እንደየአስፈላጊነታቸው እርቅና ምህረት ይከተላሉ። እርቅ ሰዎች ከመለያየትና ከደመኝነት ወጥተው ወደ ቀደመ አንድነታቸው የሚመለሱበት ሂደት ነው።
በዚህ ሂደት ውስጥ ያለፈ የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ነው ከንድፈ ሀሳብ ባለፈ ተጨባጭ ለውጥ በማምጣት ፍትህን የሚያሰፍነው። አገራችን ኢትዮጵያ አስተማማኝ ሰላምና የወንጀል ተጠያቂነትን ለማስፈን መጀመሪያ በጀመረችው የፍትህ ትግበራ መቀጠል አለባት። ሁለተኛ፣ የሽግግር ፍትህ ሂደቱ ለውጥ እንዲያመጣ በዓላማና በእቅድ የተመራ የትግበራ እንቅስቃሴ ያስፈልገዋል።
እንደአገር ለሚነሱ ፖለቲካዊም ሆኑ ሌሎች ጥያቄዎች ከመንግሥት ጎን ለጎን ከወገንተኝነት ጸድቶ ምላሽ የሚሰጥ እንደ የሽግግር ፍትህ ዓይነት ገለልተኛ አካል ያስፈልጋል። ይሄ አካል ወደ ማህበረሰቡ ጠልቆ እንዲገባና የምርመራ ሂደቱን እንዲቀጥል ምቹ ሁኔታዎች ያስፈልጉታል።
ምቹ ሁኔታዎችን ለመፍጠር እንደ መንግሥት እና እንደ ዜጋ በጥያቄና በትብብር መሳተፍ ለውጤቱ ሌላ ተጨማሪ ኃይል የሚፈጥር በመሆኑ አስተዋጽኦው የጎላ ነው። በእውነትና ፍትህ፣ በተጠያቂነትም መርህ የተጎጂዎች ጥያቄ ተመልሶ፣ ወንጀለኞች ፍርድ አግኝተው ሁሉም የእጁን እንዲያገኝ ፈረሱም ሜዳውም እነሆ።
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ሚያዚያ 30/2015