በኢትዮጵያ ከቅርብ አመታት ወዲህ በተለይም በመዲናችን አዲስ አበባ እና በትላልቅ ከተሞች የጫትና የአደገኛ አደንዛዥ ዕጽ ዝውውርና ተጠቃሚነት በእጅጉ ጨምሯል። በቤት ውስጥ በጎጆ ኢንዱስትሪ ከሚመረት ጠላና አረቄ ጀምሮ በፋብሪካ እስከ የሚመረቱ ቢራና ሌሎች የአልኮል ይዘት ያላቸው መጠጦች ምርት ሲጨምር እንጂ ሲቀንስ አይስተዋልም።
ቢራን ብቻ ብንወስድ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ ባልደረባ የሆኑት ፕሮፌሰር ሰለሞን ተፈራ ሰሞኑን ይፋ ባደረጉት አንድ ጥናታቸው እንደጠቆሙት፣ እኤአ በ2000 በየዓመቱ 100 ሚሊዮን ሊትር አካባቢ ይመረት ነበረ ሲሆን በየዓመቱ ከ15 እስከ 20 በመቶ እያደገ አሁን ዓመታዊ ምርቱ 1 ነጥብ 4 ቢሊዮን ሊትር ደርሷል። በአማካይ ለእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ 12 ሊትር ይደርሰዋል።
አምራች ፋብሪካዎቹም በእጅጉ ተስፋፍተዋል። ሁላችንም እንደምናስተውለውም ቢራ ሸቀጣ ሸቀጥ መደብሮች ሁሉ ገብቶ ይቸረቸራል። የሸቀጣ ሸቀጥ ንግድ ፈቃድ ያላቸው እነዚህ መደብሮች ፈቃድ ባይኖራቸውም በይፋ ከመኪና ላይ ቢራ ያወርዳሉ።
ከ21 ዓመት በታች ላሉ ወጣቶች ማናቸውም የአልኮል ይዘት ያላቸውን መጠጦች መሸጥ በአገራችን ሕግ የተከለከለ ቢሆንም እነዚህ መደብሮችም ሆኑ ትላልቅ ቡና ቤቶችና ሌሎች ቢራን ከ21 ዓመት በታች ላሉ ይባስ ብሎም ለ12 እና ለ15 ዓመት ታዳጊዎች ሁሉ ሲሸጡ ይስተዋላል። ጠጅ እንዲሁ ያለ ዕድሜ ገደብ ገንዘብ ለከፈለና ለመጠጣት ለፈለገ ሁሉ ሲቸበቸብ ማየቱ የአደባባይ ምስጢር ነው።
ጠላና አረቄ (ካቲካላ)ም እንዲሁ በቤት ውስጥ በጎጆ ኢንዱስትሪ በየሥርቻው ሳይቀር በስፋት እየተመረቱ ለመጠጥ በሽያጭ የሚቀርቡበት ሁኔታ አለ። የእነዚህም ተጠቃሚ ቁጥር ቀላል አይደለም።
እነዚህ መጠጦች በሚቸበቸቡባቸው ቤቶች በአብዛኛው በማስከር፤ ዱላ በማማዘዝ ሲያደባድቡ፤ ሲያጯጩሁና ሲያጋጩ በየአካባቢያችን የምናስተውለው ታዳጊውንና ወጣቱን የኅብረተሰብ ክፍል ነው።
ከእነዚሁ ጎን ለጎን በአገራችን በብዙ አካባቢዎች በተለይም በመዲናችን አዲስ አበባ፤ ሌሎች አካባቢዎች ጫት መቃሚያ ቤቶች ከዕለት ወደ ዕለት እየጨመሩ ናቸው። በለጬ፤ የአወዳይ፤ የባህር ዳር፤ የጅማ ጫት አለ እየተባለ በሚሸጥባቸው በእነዚህ ጫት ቤቶች ስንገረም በተለይ በከፍተኛ ትምህርት ተቋምና በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ዙሪያ የሻይ ቡና እና የምግብ አገልግሎት ለመስጠት ነው የተቋቋምነው የሚሉት ቤቶች በድብቅ በየጓዳቸው ጎዝጉዘው የተማሪውን አእምሮ ሲያናውዙ ይስተዋል። ፡
ቢራና የአበሻ አረቄ (ካቲካላ)ም በዚያው ጓዳ ሲያቀርቡ ማስተዋሉ የተለመደ ነው። ይሄም ብቻ ሳይሆን በእነዚህ በትምህርቱ ተቋማት ዙሪያ ያሉ ቤቶች ውስጥም ጫት ብቻ ሳይሆን ኮኬን፤ ሄሮይንና ሌሎች አደገኛ ዕጾችም በስውር ይቀባበላሉ። ይዘዋወራሉ። ቶባኮ ያስጨሳሉ።
አብዛኛው በእነዚህ አካባቢዎች የሚኖርም ሆነ የሚማርና የሚያድግ ታዳጊና ወጣት የኅብረተሰብ ክፍል የአደገኛ አደንዛዥ ዕፆች እና የአልኮል ይዘት ያላቸው መጠጦች የሱስ ተገዢ ለመሆን ተገድዷል። በቅርቡ ይፋ በሆነ አንድ ጥናት አሁን በአገራችን ካለው አጠቃላይ ወጣት 4 ነጥብ 4 በመቶ የሚሆነው በእነዚሁ የአደገኛ ዕፆችና የአልኮል ይዘት ያላቸው መጠጦች ሱስ የተፀናወተው መሆኑ ተረጋግጧል።
ጥናቱ በዚህ ምክንያትም በተለይ እነዚህ ቤቶች ባሉበት በሁለተኛ ደረጃና ከፍተኛ ትምህርት የሚማር ተማሪ በትምህርቱ ውጤታማ መሆን አለመቻሉን ጠቁሟል። ባህርይው መቀየሩና ባህላዊና ማህበራዊ እሴቱ መሸርሸሩ ተጠቅሷል። በአንዳንድ ሱሰኛ ወጣቶች ላይ እንደምናስተውለው ሱስ የሆነባቸውን ባጡ ጊዜ በጣም ይበሳጫሉ፤ ቁጡና በጥቂት ነገር የሚናደዱ ይሆናሉ።
ሱሳቸውን ለማርካት ወደ ስርቆት ከማምራት ባሻገር እስከ መደባደብና ሁከት መፍጠር፤ አስገድዶ እስከ መድፈርም ይደርሳሉ። ላልተፈለገ ተግባር የሚጋለጡበትም ጊዜ ብዙ ነው። ግለ ወሲብ ለመፈፀም ይገደዳሉ። በተለይ በፖርኖግራፊ ሱስ ተጠቂ የሆኑ ወጣቶች ብዙ ሰዓታትን በዚሁ ላይ ከማሳለፍ የተነሳ በአግባቡ ሥራቸውን ለማከናወን ይቸገራሉ። የእንቅልፍ መዛባትም ይገጥማቸዋል። የቤተሰብ፤ የማህበራዊና መንፈሳዊ ኃላፊነቶችን መወጣትም ይሳናቸዋል።
በአጠቃላይ በሱሰኝነቱ ምክንያት ወጣቱ የሥራ አቅሙ በእጅጉ ቀንሷል። የጤናው ሁኔታም ሲታይ በእጅጉ የተቃወሰ ለመሆን በቅቷል። ውጫዊ ማንነቱን (ፊዚካል ማንነቱ ወይም የፊቱ ገጽታ ቃሚና ጠጪ ሰካራም በመምሰል) ተቀይሯል። እየተገለለና ሰካራሙ፤ ቃሚው፤ ጠጪው በመባል በመጥፎ ስም እንዲጠራም ሆኗል። እንዲህ ዓይነቱ ወጣት ጭራሽ አገር ለመረከብም የሚታመን ዜጋ ሆኖ መገኘት የሚችልበት ሁኔታ ጠቧል።
ዕምቅ አቅማቸውን በመጠቀም በዕውቀት፤ በአመለካከትና በክህሎት ዳብረውና ስብዕናቸው ተገንብቶ ለአገር የሚያበረክቱት አስተዋጽኦ አዘቅዝቋል። በተለይ ባለፉት ዓመታት በሱሰኝነታቸው ሳቢያ በቀላሉ ለችግር በመጋለጥ ወደ ጥፋትና አፍራሽ ድርጊቶች የመግባት ዕድላቸው ሰፍቷል። ለልማትና ለሠላም ሊያውሉት የሚገባ ዕምቅ ኃይል፤ ዕውቀት፤ ጊዜና ገንዘብ በከንቱ እየባከነ ይገኛል። ይሄ ሁሉ በሱሰኝነታቸው ምክንያት እየደረሰባቸው ያለ ችግር ነው።
ይሄንኑ የጥናት ግኝት ተከትሎም ጉዳዩ በበላይነት የሚመለከተው የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር እንደ አገር ሱስ የተፀናወተው ከጽንውቱ እንዲያገግም፤ ያልገባውም ወደሱስ ጽንውተኝነት እንዳይገባ ለመታደግ እንደ አገር ለአንድ ዓመት የሚዘልቅ የንቅናቄ መድረክ ይፋ በማድረግ ጥሪውን ሲያቀርብ ተደምጧል።
በዚህ ከሚያዝያ 2015 እስከ ሚያዝያ 2016 ዓ.ም የሚዘልቅ መድረክ ወጣቶች ወደዚህ የአደንዛዥ ዕፅ ሱስ እንዳይገቡ የገቡትም በፍጥነት እንዲወጡ የተለያዩ የንቅናቄ ተግባራት እንደሚከናወኑም ታውቋል።
ይሄን ንቅናቄ በመተግበር ግቡን ከስኬት ለማድረስ በአገራችን አሁን ላይ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ምቹ ሁኔታዎች መኖራቸውን ሁላችንም የምናውቀው ነው። ዛሬ በመላው ኢትዮጵያ እጅግ አስደሳች ሰላም ሰፍኗል። ከጦርነት ነጋሪት ፉከራ፤ ጥፋት ወጥተናል። ሰላም መልሶ ግንባታን የምንነጋገርበትን አጀንዳም አንስተናል።
ይህን የሰላም አየር ለማስቀጠልም በዚህ ሳምንትም የሁሉም ክልል ርዕሳነ መስተዳድሮች ወደ መቐለ አቅንተዋል። በብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አደም ፋራህ እየተመራ ወደ መቐለ የተጓዘው ልዑክ አላማም ያነቡ ዓይኖችን ለማበስ፤ የተበላሹ -የፈረሱ ቦታዎችን ለመጠገን ለክልሎች እንደ ወንድም ሕዝቦች ካላቸው ለማጋራትና ይሄን የሰላም ጅማሮ በተግባር ለማስቀጠል ነው።
ከኦነግ ሸኔ ጋር የሚደረገው ድርድር በታንዛንያ መጀመሩም ለዓመታት ሰላም ተጠምቶ ለመኖር የተገደደው ሕዝብ ትልቅ እፎይታ ነው። በዚህ ድርድር የሚሳተፉ ወገኖች ከግጭት፤ ከጦርነት ትርፍ እንደሌለ በመረዳት በሕግና ሥርዓት እንዲሁም በይቅርታ አገራቸውን በጋራ ለማነፅና ለመገንባት ከስምምነት እንደሚደርሱም ይጠበቃል።
ይሄን መሰሉ በአገራችን የተፈጠረ ምቹ ሁኔታና ዕድል ከጦርነት ጋር በተያያዘ ባለፉት አራትና በላይ ዓመታት የገጠሙንን አገራዊ ችግሮች ብቻ ሳይሆን በአደገኛ አደንዛዥ ዕጽና የአልኮል ይዘት ባላቸው መጠጦች የሱስ ተገዥ ለመሆን የተዳረገውን አምራች ወጣት የኅብረተሰብ ክፍል ችግር ለመፍታትም ይመቻል።
የሰላም አየር ተንፍሰን ወደ ልማት መዞራችንን የምናረጋግጠው ይሄን የወጣቱን ችግር በመፍታት በአገሩም ሆነ በአህጉሩ አፍሪካ ጉዳይ ላይ ቀጥተኛ ተሳታፊና ውሳኔ ሰጪ ማድረግ ስንችል ነው። ሰፊ ጊዜውንም ሆነ ትኩስ ጉልበትና ኃይሉን እንዲሁም ብሩህ አእምሮና የፈጠራና የምርምር ብቃቱን ለሰላምና ለአገር ግንባታ ማዋል እንዲችል ስናደርግ ነው። የስብዕና ግንባታ ማዕከላትን ስንገነባለትና ከአልባሌ ቦታ መዋልና ከጥፋት ስንታደገው ነው።
እንደሚታወቀው ወጣቶች ባለ ብሩህ አእምሮና የምርምርና የፈጠራ ዝንባሌ ያላቸው በመሆኑ አዳዲስ ነገሮችን የመፍጠር ብቃታቸውን በመጠቀም ለአገር ብልጽግና የሚያበረክቱት አስተዋጽኦ የላቀ ነው። ይሁንና የወጣቶችን ዕምቅ አቅም ለመጠቀም በዕውቀት፤ በአመለካከትና በክህሎት እንዲዳብሩና ስብዕናቸውን መገንባት የግድ ይላል። ይህ ሳይሆን ሲቀር በቀላሉ ለችግር በመጋለጥ ወደ ጥፋትና አፍራሽ ድርጊቶች የመግባት ዕድላቸው የሰፋ መሆኑ ይታመናል።
ለዚህ ደግሞ በተለይ በትምህርት ተቋማት ዙሪያ ያሉ ጫት ቤትና ሲሻ ቤቶች እንዲሁም በሻይ ቡናና ምግብ ሳቢያ የአልኮል ይዘት ያላቸው መጠጦች፤ ዝሙትና ሌሎች ወጣቱን ለጥፋት የሚዳርጉ ተግባራት በስውር የሚከውኑ ቤቶችን ጠራርገን ማጥፋት ይኖርብናል። በዚህ እርምጃ ሱስ በማስያዝ የወጣቱን ጊዜ በከንቱ የሚያባክኑና ከውጭ ለመጡና ከባህላችን ለሚጣረስ ተግባር የሚዳረጉ የወሲብ ቤቶችም የግድ መወገድ አለባቸው።
አገር አቀፍ የንቅናቄ ጥሪውን ተከትሎ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በዙሪያው እንዲህ ዓይነት እኩል ተግባራት በመከወን ገንዘብ የሚያካብቱ ትውልድ ገዳይ ቤቶችን በመጠራረግ ቁርጠኝነቱን አሳይቶናል። ሌሎች እንደ አገር ያሉ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማትና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት አስተዳደሮችም የዩኒቨርሲቲውን ፈር ሊከተሉ ይገባል። ሁሉም ወረዳና ክፍለ ከተማ እንዲሁም ከተማ አስተዳደሮች በየአካባቢያቸው በየዕለቱ እየተፈለፈሉ የሚያድሩትን እነዚህን እኩይ ተግባር መከወኛ ቤቶች በዝምታ ሊመለከቷቸው ፈፅሞ አይገባም። ንቅናቄው ግቡን ሊመታና ውጤታማ ሊሆን የሚችለውም በጋራ ተሳትፎ ተግባር ድምር መሆኑ ሊታወቅ የግድ ይላል።
ሰላማዊት ውቤ
አዲስ ዘመን ሚያዚያ 30/2015