የአገራችን የፌደራል ስርዓት ተከትሎ በአገራችን ባለው የፖለቲካ አሰላለፍ ራሳቸውን የፌደራሊስት ኃይል ብለው የሚገልጹ ያሉትን ያህል ራሳቸውን የአንድነት ኃይል ብለው የሚገልጹ ኃይሎች ያቀፈ የፖለቲካ አሰላለፍ ይታያል፡፡ ሆኖም የፌደራሊስት እና የአንድነት ኃይል የሚለው ስያሜ ከፌደራል ስርዓት መሰረታዊ መርሆዎች እና ከአገራችን ማህበረሰባዊ ውቅር ጋር በማያያዝ ስያሜዎቹን ዝርዝር አድርጎ ማየት በማህበረሰቡ ውስጥ ከፌደራል ስርዓት ጋር ተያይዞ እየተፈጠሩ የመጡትን እና አሁንም የቀጠሉትን ብዥታዎች ለማጥራት እና ስያሜዎቹ በርግጥ ገላጭ ናቸው ወይ ብሎ ለመጠየቅ ያስችላል ፡፡
የፌደራሊዝም አስተሳሰብ ሁለት መሰረታዊ መርሆዎች አሉት፤ እነርሱም የራስ አስተዳደር እና የጋራ አስተዳደር ሲሆኑ የራስ አስተዳደር ከባቢያዊ የሆኑ አቅሞችን እና ፍላጎቶችን መሰረት አድርጎ ራስን የማስተዳደር፤ ቋንቋን ባህልን የማሳደግ፤ በቅርበት መንግስታዊ አገልገሎቶችን ማግኘትን የመሳሰሉትን የሚያጠቃልል ነው። የጋራ አስተዳደር ደግሞ አገራዊ እና የጋራ በሆኑ ጉዳዮች ላይ መሳተፍን፤ ለአገራዊ ልማት፤ ደህንነት፤ ሰላም፤ ሰባዊ መብቶች መከበር አስተዎጽኦ ማድረግ የመሳሰሉትን ያጠቃልላል፡፡
ከነዚህ ሁለት መርሆዎች ጋር ተያይዞ ከባቢያዊ ማንነት እና አገራዊ ማንነትን አስተሳስሮ መሄድን ይጠይቃል፡፡ እንግዲህ ፌደራሊዝም ሁለቱ መርሆዎች ተሳስረው እና ሁሌ ሚዛን ጠብቀው መሄድን ታሳቢ የሚያደርግ ፍልስፍና ነው፡፡ የፌደራሊዝም ፍልስፍና መነሻው የጋራ ፍላጎትና ጉዳይ መኖር እና በጋራ በአንድነት ለመቀጠል መወሰን ነው፡፡ በመሆኑም ፌደራሊዝም የራስ አስተዳደርን ወይም የጋራ አስተዳደርን በተናጠል ይዞ የሚሄድ ፍልስፍና ሳይሆን ሁለቱን አስተሳስሮ ሁሌም ሚዛን እየጠበቁ መሄድን መሰረት ያደረገ ነው።
በውጤቱም ጠንካራ ኢኮኖሚ የገነባች፤ ሰላም እና ዴሞክራሲ የሰፈነባት፤ አካታች እና የሁሉም መብት አኩል የሚከበርባት፤ ሁሉም ማህበረሰብ የእኩል ተጠቃሚነት እድል የሚያገኝባት፤ የራሱን መብትና ነጻነት የሌሎችን መብትና ነጻነት ባከበረ መልኩ እኩል የሚከበርባት አንድ ትልቅ አገር መገንባትን ታሳቢ የሚያደርግ ፍልስፍና ነው፡፡ በመሆኑም ከፌደራሊዝም እሳቤ ስንነሳ የራስ አስተዳደር እና ከባቢያዊ ፍላጎት እና ማንነት ብቻ የሚያቀነቅን ኃይል ፌደራሊስት ኃይል ሊሆን ያለመቻሉን ያህል የጋራ ጉዳይ ላይ ብቻ የሚያቀነቅን ኃይል የአንድነት ኃይል ሊሆን የሚችልበት አጋጣሚ በፌደራል ስርዓት ውስጥ ጠባብ ነው፡፡
ምክንያቱም በፌደራል ስርዓት ሁለት ኃይሎች አንድ ወደ መሀል የሚስብ እና አንድ ወደ ውጭ የሚስብ ቢኖሩም ትክክለኛው የአንድነት እና የፌደራሊስት ኃይል የሁለቱን ሚዛን ጠብቆ መሄድ የሚችለው ኃይል መሆኑ ከፍልስፍናው መሰረታዊ መነሻዎች የሚቀዳ ነው፡፡ በዚህ መነሻነት እንደ ፀሃፊዉ እይታ ቢያንስ በንድፈ ሃሳብ ደረጃ ትክክለኛ የፌደራሊስት ኃይል የአንድነት ኃይል የመሆኑን ያህል ፌደራል ስርዓትን ታሳቢ ያደረገ የአንድነት ኃይልም የፌደራሊስት ኃይል ነው ብሎ መውሰድ ይቻላል፡፡
በመሆኑም የፌደራል ስርዓቱን መሰረት አድርገው የፌደራሊስት እና የአንድነት ኃይል በሚል ስያሜ የሚገለጹ የኃይል አሰላለፎች የፌደራሊዝም ፍልስፍና መሰረት ያደረጉ መሆናቸው አጠራጣሪ ነው፡፡ ዋናውን የስበት ማዕከል የራስ አስተዳደር ጋር ብቻ የተያያዙ ጥያቄዎች፤ መብቶች ወዘተ.. ብቻ አድርጎ የጋራ ጉዳዩን ረስቶ የሚንቀሳቀስ ኃይል የፌደራሊስት ኃይል ሊያሰኘው የሚችል አንድም ፌደራላዊ አመክኒዮ አይኖርም መነሻውም በፌደራሊዝም ላይ የያዘው እሳቤ የተሞላ አለመሆን ወይንም ፌደራሊዝምን በተሳሳተ መልኩ ለራስ ፍላጎት መጠቀሚያ ለማድረግ መፈለግ ሊሆን ይችላል፡፡
በሌላ በኩል ብዝሃነት ባለበት ሀገር ውስጥ ለብዝሃነቶች የፖለቲካ፤ ኢኮኖሚ፤ ባህላዊ፤ ማህበራዊ፤ አስተዳደራዊ ፍላጎቶቻቸውን የሚያከናውኑበትን አውድ የሆነውን የራስ አስተዳደርን በረሳ መልኩ የጋራ አስተዳደርን እና የጋራ ጉዳዮችን ብቻ ይዞ መንቀሳቀስ የአንድነት ኃይል የሚሰኝበት ፌደራላዊ አመክኒዮ የለውም፡፡ ሆኖም አሰላለፎቹ ከፌደራል ስርአት ውጭ የሚኖርን አውድ ታሳቢ ያደረገ ከሆነ እንደ አገራችን ነባራዊ ሁኔታ የፌደራሊስትም ሆነ የአንድነት ኃይል የብተና ኃይል የሚሆንበት እድሉ ሰፊ ነው፡፡
በአገራችን የፌደራል ስርዓት የአገራችን ነባራዊ ሁኔታ፤ የፌደራሊዝም ፍልስፍና እና ፌደራላዊ ፖለቲካ አደረጃጀት መሰረት አድርጎ ሁሌም በራስ አስተዳደር እና በጋራ አስተዳዳር መካከል የሚኖረውን ሚዛን ጠብቆ የሚተገብር ኃይል የፌደራሊስት እና ከዚያው ሳለም የአንድነት ኃይል ሆኖ የሚወጣበት ሁኔታ መፈጠሩ የማይቀር ነው፡፡
ዋናው ቁምነገር በፌደራል ስርዓት የበላይ ወይም የበታች የሚሆን ማህበረሰብ የሌለበት ሁሉም የራሱን ጉዳይ በራሱ በየደረጃው የሚያስተዳደርበት እና በጋራ ጉዳዮች ላይ የሚሳተፍበት እና ለጋራ አገራዊ እድገት አስተዎጽኦ የሚደረግበት እኩል እድል የሚፈጠርበት መሆኑን በመገንዘብ ለዚህ ስኬት በመነጋጋር፤ በመመካካር፤ በመደጋጋፍ፤ በመተባበር፤ በመከባባር፤ እውቅና በመስጠት፤ የሌሎችን ችግር እንደራስ አድርጎ በማየት፤ አሸናፊና ተሸናፊ የሚል የፖለቲካ ቁርቁስ ሳይሆን ሁሉም አሸናፊ የሚሆንበት ሚዛናዊ ሂደቶችን መከተል የሚጠይቅ መሆኑን መገንዘብ እና ለተግባራዊነቱ መትጋት ነው፡፡
የፌደራል ስርዓትን ተመራጭ የሚያደርጉትን ብዝሃነትን ለማስተናገድ ያለውን እምቅ አቅም እና በብዝሃነት የተዋበ አንድነትን ለመገንባት የስርዓቱ መኖር መሰረታዊ ምክንያት በትክክል በሚተገበርበት መልኩ የሚንቀሳቀስ ኃይል ከዚያው ሳለ የአንድነት እና የፌደራሊስት ኃይል ባህሪያትን የሚላበስበት ሀኔታ መፈጠሩ አይቀርም፡፡
ከዚህ አኳያ በአገራችን አሁን ከዚህም ከዚያም የሚሰሙት የኃይል አሰላለፍ ብያኔዎች ከፌደራል ስርዓት አመክኒዮ አንጻር ሲታዩ የተሳሳቱ እና ማህበረሰቡንም በፌደራል ስርዓት ዙሪያ ያለውን አረዳድ የበለጠ ትክክለኛ ወደ አልሆነ አቅጣጫ የሚመሩ ስርዓቱንም ከስርዓቱ ባህሪያት ወጣ ባለ መልኩ የፖለቲካ ሊህቃኑ በሚፈልጉት መልኩ የፖለቲካ ፍላጎት ማስፈጸሚያ በማድረግ በአገራችን ነባራዊ ሁኔታ በጣም ተፈላጊ የሆነውን ስርዓት በአግባቡ እንዳይተገበር እንቅፋት ከመሆን በዘለለ ፋይዳ የሌለው በመሆኑ በፌደራል ስርዓት ዙሪያ ትክክለኛ እይታዎች እንዲያድጉ እና በተግባርም እንዲውሉ የሁሉንም የጋራ ጥረት የሚጠይቁ ይሆናል፡፡
በአገራችን ከብዝሃነታችን ጋር ተያይዞ ለሚኖሩ ብዝሃ የሆኑ የፖለቲካ፤ ማህበራዊ፤ ኢኮኖሚያዊ እና አስተዳደራዊ ጥያቄዎች አንጻራዊ በሆነ መልኩ በተሻለ ሁኔታ ማስተናገድ የሚችለው የፌደራል ስርዓት የማይሆንን ከሆነ ምን አይነት ስርዓት ሊሆነን እንደሚችል ብዝሃነት እና አንድነትን መሰረት አድርጎ ሲፈተሽ አማራጩ ከመበተን የዘለለ ሊሆን የሚችልበት ሁኔታ ውስን መሆኑ ነው፡፡
ችግሩ በአገራችን የማህበረሰባዊ ውቅር፤ አሰፋፈር፤ አኗኗር፤ አስተሳሰብ፤ ስነልቦና ወዘተ አንጻር እርስ በእርስ ከመጠፋፋት በዘለለ በሰላም የምንለያይበት አማራጮች የሉም ብሎ መደምደም የሚስያችን አውድ ያለ መሆኑ ነው፡፡ ስለሆነም የፌደራሊዝም እሳቤዎችን በተገቢው መረዳት፤ የፌደራላዊ አስተዳደር ስርዓቱን በትክክለኛው መንገድ መተግበር አሳሳች የሆኑ የኃይል አሰላለፍ ብያኔዎችን መፈተሽ ፌደራል ስርዓቱን ትክክለኛ ወደ አልሆነ አቅጣጫ እንዳይመሩት በማህበረሰቡ ውስጥ የፌደራሊዝም አስተሳሰብ እና የፌደራል ፖለቲካዊ ስርዓት ላይ የአገራችን ተጨባጭ ሁኔታ መሰረት ያደረገ ግንዛቤ እንዲኖር መስራት ይጠበቃል፡፡
ኃይለየሱስ ታዬ (ዶ/ር)
ፌደራሊዝም ጥናት ረዳት ፕሮፌሰር
ኢ-ሜል፡- tayehaileyesus3@gmail.com
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 26/2015