ጉርብትና ማለት በኢትዮጵያውያን ዘንድ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው አብሮ የመኖር ውጤት ነው። ‹‹ከሩቅ ዘመድ ይልቅ ቅርብ ያለ ጎረቤት›› የሚባለውም አብሮ በመኖር ውስጥ የሚፈጠረው ጠንካራ ግንኙነት ጥብቅና ከስጋ ዘመድ የሚልቅ በመሆኑ ነው። ጎረቤት ብትወድቅ ቀና የሚያደርግ፣ ጓዳ ጎድጓዳህን የሚያውቅ ክፍተትን የሚደፍን፣ መከራ ችግርን እንዲሁም ደስታ ሲገጥምህ በቶሎ ደርሶ አብሮ የሚጋራ ፈጥኖ ደራሽ ነው። ጎረቤት ‹‹ገመና ከታች›› ወይም ‹‹ገመና ሸፋኝ›› የሚባለውም በዚሁ ምክንያት ነው።
በሰዎች ላይ በሚደርስ ማንኛውም መከራና ችግር ፈጥኖ ደራሹ ጎረቤት ነው። አሁን አሁን የአኗኗር ዘይቤያችን ለዘመናዊ አኗኗር ተጋልጦ የጉርብትና ሕይወት የተቀዛቀዘ ቢመስልም ጨርሶ አልጠፋም። እርግጥ ነው ዛሬ ካንዱ ቤት እንጀራ ታጥፎ ከሌላ ቤት ወጥ አይጨለፍ ይሆናል እንጂ ከላይ ከላይ በሆነ ፍቅር አልፎ አልፎም ቢሆን አብሮ መብላት መተሳሰቡና በክፉ መደራረሱ ግን አልቀረም። ዛሬ እናቶች የአቻ ጎረቤታቸውን ልጅ አዝለው ባያሳድጉም ‹‹ማሙሽ ደህና ነው ሚሚስ እንዴት ናት›› በማለት የጎረቤታቸውን ሰላም ውሎ ማደር መጠየቃቸው ግን አልቀረም። ሊቀርም አይችልም።
ትናንት ጠንካራ የነበረው የጉርብትና ትስስር ዛሬ እጅግ ሳስቶ ‹‹ጎረቤት ድሮ ቀረ›› ቢያስብልም የሳሳው እንዳይበጠስ፤ የተቀዛቀዘው እንዲሟሟቅ ቆም ብሎ ማሰብ ከእያንዳንዳችን ይጠበቃል። ከማሰብ ባለፈም መገለጫችን የሆነውን መረዳዳትና መተሳሳብ ጥብቅ በሆነው ጉርብትናችን መተግበር ያስፈልጋል። ምክንያቱም እኛ እኮ ኢትዮጵያውያን አብሮ በመኖር ለሌሎች መልካም ምሳሌ መሆን የቻልን ታላቅ ህዝቦች ነን። ግለኝነት በነገሰበት ዓለም ካለን ላይ ቀንሰን የምናካፍል፤ ጎረቤት ይሸተዋል ብለን የቀመስነው የምናቀምስ፤ እንግዳችንን እግር አጥበን ካልጋ የምናስተኛ፤ እኛ ደግሞ መሬት አንጥፈን የምንተተኛ ዓለም የመሰከረልን እንግዳ ተቀባይ ህዝቦች ነን።
‹‹…ያንተ ቤት ሲንኳኳ ይሰማል እኔ ቤት…›› እንዳለው ድምጻዊ የጎረቤት ችግር ችግራችን፤ የጎረቤት ደስታም ደስታችን፤ ይሆን ዘንድ የግድ የሆነብን እኛ ኢትዮጵያውያን ጎረቤት ተርቦ እኛ ጠግበን ማደር የማንችል፤ ጎረቤት ሲታመም እኛ ብርድ ብርድ የሚለን፤ የጎረቤት ሰላም ማጣት እንቅልፍ የሚነሳን በአንጻሩ ደግሞ የጎረቤታችን ሰላም መሆን ሰላም የሚሰማን ነን።
ይህ በጉርብትና ያዳበርነው ጠንካራ ማህበራዊ ግንኙነታችን ታድያ ግድግዳ ከሚለየን ጎረቤት አልፎ ከአገራት ጋር ባለን ጉርብትናም ስሜታችን አንድ ነው። ለአገራት ጉርብትና የነበረንና አሁንም ያለን ግንኙነት አገርኛ ከሆነው ጉርብትና የበለጠ ከሆነ እንጂ የሳሳ አይደለም። ምንም እንኳን የራሳችንን የማናስደፍር የሰውም የማንነካ ኩሩና ቆፍጣና ህዝቦች ብንሆንም ከጎረቤት አገራት ጋር አብሮና ተባብሮ በሰላም መኖርን አብዝተን እናውቅበታለን።
በሰላም አብሮ መኖርን በጉርብትና ያዳበረችው ኢትዮጵያ በታሪኳ ለገጠሟት ችግሮች ሁሉ የጠብ መነሻ ሆና አታውቅም። ለዚህም አብሮና ተባብሮ ተቻችሎ በመኖር የገነባቸው መልካም ዕሴቶቿ ምክንያት ናቸው። ያም ቢሆን ታድያ ገፍቶ ለመጣባት ጠላት ደከመኝ ሰለቸኝ ሳትል ሰላማዊ መንገድን ትመርጣለች። በተለያየ ጊዜ የገጠሟትን ችግሮች ስንመለከት ታድያ ችግሯን ሰላማዊ በሆነ መንገድ ለመፍታት እስከመጨረሻው ጥግ በመጓዝ ለሰላም ዋጋ ትከፍላለች። እሳት ሆኖ የመጣውን ለሰላም ቅድሚያ በመስጠት ውሃ ማድረግ ትችላለች።
አሁን አሁን ደግሞ ለሰላም ቅድሚያ ከመስጠት ባለፈ የውስጥ ችግሮቿን በውስጥ የመፍታት አቅሟን ከጉርብትና ወደ አገር ከአገርም ወደ አህጉር ከፍ ማድረግ ችላለች። ለዓለም የሚተርፍ የመቻቻልና የአብሮነት እሴት ያላት ኢትዮጵያ፤ በተለያዩ አካባቢዎቿ ለጸብ መድሃኒት የሆኑ ባህላዊ የእርቅ አይነቶች አሏት። አባቶች በዛፍ ሥር ተሰባስበው አጥፊውን ቀጥተው እርቀ ሰላም ከማውረድ ጀምሮ፤ ‹‹ዝቅ ያለ ከፍ ይላል›› እንዲል ቃሉ እርጥብ ሳር ይዘው ከመሬት ወድቀው ይቅርታና ምህረትን የሚጠይቁ፤ ለአገር ሰላም የሚተጉ ኢትዮጵያዊ አባቶች አሉ። እነዚህ ሁሉ መልካም እሴቶች ታድያ አብሮ በመኖር የዳበሩ በጉርብትና ተሰናስነው የመጡ ስለመሆናቸው የማይታበል ሃቅ ነው።
ኢትዮጵያ ዛሬ በትናንት መሰረቷ የሰላም ምሳሌ ከመሆን ባለፈ ‹‹የአፍሪካውያንን ችግር በአፍሪካውያን›› የሚለውን በተግባር ማሳየት ችላለች። ይህ ለሌሎች አፍሪካውያን እህትና ወንድሞች ምሳሌ መሆን የቻለ ታላቅ ተግባር ነው። ስለዚህ ‹‹…ሞያ ከጎረቤት›› እንዲሉ መላው አፍሪካውያን ኢትዮጵያ ለሰላም ቅድሚያ በመስጠት የወሰደችውን እርምጃ ቢወስዱ በብዙ ያተርፋሉ። በተለይም በአሁን ወቅት ጎረቤት አገር ሱዳን አሁን ካለችበት ወቅታዊ ሁኔታ በሰላምና በፍጥነት መውጣት የምትችለው ‹‹የአገሩን ሰርዶ በአገሩ በሬ›› እንዲሉ አበው ያለማንም ጣልቃ ገብነት የውስጧን ችግር በውስጥ አቅሟ መፍታት ስትችል መሆኑን የኢትዮጵያ መንግሥት በጽኑ ያምናል።
‹‹ያንተ ቤት ሲንኳኳ ይሰማል እኔ ቤት›› ነውና ነገሩ የጎረቤት ሱዳን ሰላም ማጣት ኢትዮጵያን እንቅልፍ የሚሰጣት አይሆንም። ‹‹ከሩቅ ዘመድ የቅርበ ጎረቤት›› ነውና ነገሩ ከሌሎች አፍሪካ አገራት ይበልጥ የጎረቤት ሱዳን ህመም ለኢትዮጵያም ህመም ስቃይዋም ስቃይ በመሆኑ ቁስሏ ይጠዘጥዛታል። ለጉርብትና ትልቅ ዋጋ የምትሰጠው ኢትዮጵያ ከሱዳን ጋር ጥብቅና ጠንካራ ወዳጅ የሆነች ጎረቤት አገር ናት።
ኢትዮጵያና ሱዳን በመንግሥት መለዋወጥ ያልዋዠቀ ጽኑ ወዳጅና ጎረቤት አገራት ስለመሆናቸው ይነገራል። ታድያ ሱዳን ካጋጠማት ወቅታዊ ችግር እንድትወጣ የጉርብትና ትርጉሙን ጠንቅቃ የምታውቀው ኢትዮጵያ በየትኛውም ሁኔታ ከሱዳናውያን ጎን እንደምትሆን አረጋግጣለች። የኢትዮጵያ መንግሥታት ከአጼ ኃለስላሴ ጀምሮ አሁን እስካለው እስከ ጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ አህመድ መንግሥት ድረስ ሱዳን ያጋጠሟትን ችግሮች በሰላም እንድትፈታ ጉልህ ሚና መጫወታቸውን ታሪክ ይነግረናል።
ዛሬም ቢሆን ጎረቤት ሱዳን የገጠማትን የሰላም መደፍረስ ሰላማዊ በሆነ መንገድ በመነጋገርና በመወያየት መፍታት እንድትችል ኢትዮጵያ የጸና ፍላጎትና ዕምነት ያላት ስለመሆኑ ጠቅላይ ሚኒስቴር ዐቢይ አህመድ የሱዳን ወንድማማች ፓርቲዎች ወደ ሰላም ንግግር እንዲመለሱ ባቀረቡት ጥሪ የሱዳን ወንድማማች ፓርቲዎች ከግጭት አባባሽ ድርጊቶች ተቆጥበው የተፈጠረውን ግጭት በውይይት እንዲፈቱ ጥሪ ማቅረባቸው ይታወሳል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገፃቸው በሱዳን ከተፈጠረው ግጭት ጋር በተያያዘ በአረብኛ ቋንቋ ባስተላለፉት መልዕክት የኢትዮጵያ መንግሥት በሱዳን ወንድማማች ፓርቲዎች መካከል የተፈጠረውን ግጭት በትኩረት እየተከታተለው እንደሆነም ገልጸዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የሱዳን ወንድማማች ፓርቲዎች በመካከላቸው የተፈጠረውን ግጭት እንዲያረግቡ ባቀረቡት ጥሪ መሰረት በሁለቱ አካላት መካከል የተፈጠረውን ችግር ለመፍታት እና የአፍሪካን ችግር አፍሪካዊ መፍትሔ ለመስጠት አዲስ አበባ ሁሌም ቢሆን በሯ ክፍት እንደሆነ በመልዕክታቸው ጠቅሰዋል። ‹‹ሳይቃጠል በቅጠል እንዲሉ›› አበው ሱዳን ከጎረቤቷ ኢትዮጵያ በመማር የሰላምን መንገድ አማራጭ ብታደረግ መልካም ነው። እያልን፤ ሱዳን ሆይ! ከሩቅ ዘመድ የቅርብ ጎረቤት ይበልጣልና ከጎረቤትሽ ኢትዮጵያ ተምረሽ ህዝብሽን ከጥፋት ታደጊ በማለት እናብቃ!
ፍሬሕይወት አወቀ
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 25/2015