ቀደምት ኢትዮጵያውያን ሀገርን በማጽናት ሂደት ውስጥ ለነጻነታቸው በበርካታ ጦርነቶች ውስጥ አልፈዋል። በእያንዳንዷ የጦርነት ወቅትም ከወታደር እስከ ሰላማዊ ዜጋ በወርቅ መዝገብ ሊሰፍር የሚገባውን ተጋድሎ ፈጽሟል። የዚህ ምስጢር ደግሞ ቅኝ ለመገዛት ፤ ላለመወረርና ላለመንበርከክ ያለ ቁርጠኝነት ብቻ ሳይሆን የሰላምን ዋጋና ሰላምን ለማረጋገጥ ብዙ መስዋእትነት መክፈል የሚጠበቅ መሆኑን በመረዳታቸው ነው።
ይሄ የአያት ቅድመ አያቶቻችን ታሪክና ገድል ነው። የዛሬዎቹ እኛ ደግሞ ይሄንን ብንችል የራሳችንን አዲስ ገድል መጻፍ፤ ባንችል ደግሞ ይሄንን አስጠብቆ ለቀጣዩ ማኖር ይጠበቅብናል። ለዚህ ደግሞ የታሪክ ባለቤትነቱን የማኖርም፣ የቀደምቶቹን ታሪክ ብሎም ያስጠበቁለትን ሀገር በነጻነትና በሰላም የማስቀጠም አስጠብቆ የማዝለቅም ኃላፊነቱ ከመቼውም ግዜ ባልተናነሰ ትግልን ይጠይቀዋል። ለዚህ ደግሞ የራቀውን ታሪክ ለታሪክ ሰናጆች ትተን የኢትዮጵያ ወርቃማ ልጆች እንደ አንድ ልብ መካሪ.. እንደ አንድ አንደበት ተናጋሪ … ሆነው የዛሬ 87 አመት የፈፀሙት ተጋድሎ ለዛሬው ትውልድ ቅርብ ምስክርም አስረጅም አድርጎ ማየት ይቻላል።
ወቅቱ ኢትዮጵያ ብቻ ሳትሆን መላው አለም በሁለተኛው የአለም ጦርነት የተጠመደበት ነበር። ጠንካራና ሀያላን የተባሉት የአውሮፓ ሀገራት ሳይቀሩ ብዙ የማይሽር ጠባሳን አስቀምጠው ያሳለፉበትም አጋጣሚ ነበር። እኛም ከቀናት በኋላ የምናከብረው የድል በዓላችን ዛሬ ያለው መላው ኢትዮጵያዊ አያት ቅድመ አያቶቹ ዛሬ እንዲኖረው ላሰቡት ሰላም ለትውልድ ሲሉ የከፈሉለት ዘመን አይሽሬ መስዋእትነት ውጤት ነው።
ወቅቱ የሚታወሰው ወራሪው የጣሊያን ጦር አገር የተቆጣጠረ ያለ በመሰለው ወቅት ፈላጭ ቆራጥ በመሆን በየዱር በገደል የሚዋጉትን አርበኞች የተበቀለ በሚመስል መልኩ ህዝብ እየጨፈጨፈ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያውያንን ሰላም ሲነሳ የነበረበት ነው። በዚህ ወቅት እያንዳንዱ አርበኛ ኢትዮጵያዊ መሞት ፈልጎ ሳይሆን ለሰላም መስዋእትነት መክፈል የግድ ይል ስለነበር ጉሮሮ ለጉሮሮ እየተናነቀ በከፋ መስዋእትነት የሀገሩን ነጻነትና ሰላም ማረጋገጥ ችሏል።
በአምስት የትግል ዓመታት በወራሪው ኃይል የተሰዉ ኢትዮጵያውያን ያን ሁሉ መከራ የተሸከሙት የኛን ሰላምና ነጻነት ለማስጠበቅ ነበር። ልፋታቸውም ውጤት አግኝቶ ዛሬ ላይ እንድንደርስ አብቅተውናል። ይሁን እንጂ በዚህ መልኩ ለወረራ በገባ ኃይል ከሚፈጸም ጭፍጨፋ እና የሰላም እጦት ነጻ መውጣት ብንችልም፤ የታሪክ አጋጣሚ ሆኖ እኛ ኢትዮጵያውያንና ሀገራችን ኢትዮጵያ የምንፈልገውን ሰላም አስጠብቀናል ለማለት የሚያስደፍር ሁኔታ የለም። ምክንያቱም ዛሬም ድረስ ከውጭም ሆነ ከሀገር ውስጥ የሚከሰቱ ፖለቲካዊ ችግሮች በተለያዩ ግዜያት እየተከሰቱ እየፈተኑንም ብዙ እያስከፈሉንም ይገኛል።
ይሄ ደግሞ ለውጪ ጠላት በአንድ ጸንቶ የቆመ ማንነታችን፣ በተለያዩ ምክንያቶች ጠላትን ካስወገደ በኋላ በአንድነቱ ጸንቶ የቆመበትን እሴት በመተው ለልዩነቶቹ ቦታ በመስጠቱ ምክንያት የተፈጠረ ነበር። በእነዚህ ልዩነቶች ደግሞ እርስ በእርስ ተገፋፍተናል፤ ጦር ተማዝዘንም ዋጋ ከፍለናል።
ሆኖም እነዚህ በውስጥ የገጠሙን አለመስማማቶች በሙሉ ሁሉም ሊባል በሚያስደፍር ደረጃ ከጦርነት ማግስት በድርድርና በስምምነት የተጠናቀቁ ናቸው። ለምን ቢሉ፣ እነዚህ አለመግባባትና ግጭቶች ቀድሞውኑ ከእልህ ወጥቶ መመካከር መነጋገር ቢቻል ኖሮ ዶላር የሚተፉ ጠብመንጃዎች የንጹሀንን ነፍስ ሳይነጥቁ… አካል ሳያጎድሉና ንብረት ሳያወድሙ በቀሩ ነበር።
ልዩነቶቻችን ደግሞ መገዳደል የሚያደርሱ ሳይሆኑ በወቅቱ በአግባቡ ቢያዙ በሀሳብ የበላይነት የሚፈቱም ነበሩ። ሌላው ቀርቶ ይህን የድል ቀናችንን «መጋቢት ሃያ ስምንት» ይሁን ወይንስ «ሚያዚያ ሃያ ሰባት» በሚል ብዙ ተወዛግበን በተለያዩ የአስተዳደር ዘመናት በተለያዩ ቀናት ስናከብረው መቆየታችን የታሪካችን አንድ ክስተት መሆኑን ለማስታወስ እፈልጋለሁ።
ይህ የሃሳብ ልዩነት ተፈጥሯዊ ነው፤ ቁምነገሩ የሃሳብ ልዩነቶቹን በመነጋገር ማረቅና ማስማማት መቻሉ ነው። እዚህ ላይ ዛሬ ሰላም ናቸው ብለን ከሰላም ኗሪ ህዝቦች ተርታ የመደብናቸው ሀገራትም ቢሆኑ የውስጥም ሆነ ውጫዊ ችግር የለባቸውም ማለት አይደለም። በየትኛውም ሀገርም ሆነ ህዝብ ውስጥ የሚቀርቡ ጥያቄዎችና የሚከሰቱ አለመግባባቶች እንዳሉ ይታወቃል። ልዩነቱ ግን ያለው እነዚህ ሀገራት ያሉባቸውን ልዩነቶችንም ሆነ አለመስማማቶች ወይንም ጥያቄዎች የሚያስተናግዷቸው ሰላማቸውን በማያደፈርስ የእለት ከእለት እንቅስቃሴያቸውን በማያውክ መልክ ነው። ምክንያቱም ሰላም ካለ ሁሉንም ነገር ለማድረግ ስለሚቻል ነው።
አሁን ላይ ባለኝ መረዳት ምን አልባትም በዚህ ወቅት ሰላም ለማስጠበቅ የሚሰራው ስራ ከመንግስት አካላትና ከፖለቲከኞች በላይ፣ ከህዝብ የሚጠበቅ መሆኑ ከቀደሙት ግዜያት ለየት የሚያደርገው ይመስለኛል። ሁሌም እንደሚባለው ምንም እንኳን ብዙውን ጊዜ ለችግራችን መነሻና መባባሻ የውጪ አካላት ጣልቃ ገብነት ያለበት ቢሆንም፤ አብዛኛው የሰላም እጦታችን መነሻውም መድረሻውም እኛው ኢትዮጵያውያን ነን።
ምክንያቱ ደግሞ እኛ ጋር የተለየ በአለም ያልደረሰ ችግር ተፈጥሮ ሳይሆን ያለውን ሁኔታ ዘመኑ በደረሰበት የሰለጠነ እሳቤ በመነጋገር በመደማመጥ ለመፍታት የምናደርገው ተነሳሽነትና ርብርብ ዝቅተኛ መሆኑ ነው። በተለይም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአንዳንድ ጉዳዮች ላይ በጥቂት አካላት የተጀመሩ ነገሮችን በማህበራዊ ሚድያና በአካል ጭምር ቤንዚን አርከፍክፈን ያዘው በለው እያልን የምናባብሳቸውና ትልቅ ቀውስ የምንፈጥረው እኛው ነን።
በዚህ ረገድ ዘመኑ የደረሰበት ቴክኖሎጂና በየቀኑ እየተፈጠሩ ያሉ የመረጃ መለዋወጫ መሳሪያዎች ለእድገት፣ እንዲሁም ሰላምን ለማስጠበቅ በበጎ ለሚጠቀምባቸው የሚኖራቸው ፋይዳ አጠያየቂ አይደለም። አሁን ባለው ነባራዊ ሁኔታ ግን በአንዳንድ እኩይ አላማ ተሸካሚዎችና ገንዘብ ወዳድ ብልጣብልጦች ፤ እንዲሁም እኛ ራሳችን እንደ ዜጋ በሥርአትና በኃላፊነት ባለመጠቀማችን እያደረሱት ያለው ውድመት አስጊ ደረጃ ላይ እየደረሰ ይገኛል። ጥቂት የማንባል ሰዎች በማህበራዊ ሚድያ ማንም ለቃቅሞ ለገንዘብ ማግኛ የለጠፈውን እያየን ሌሎችን ከመተቸት ከመሳደብ አልፈን ራሳችንንም ጤና ስንነሳ እንሰነብታለን።
ትእግስት፤ ማጣራት፤ ማስተዋልና እኔስ ብሆን ብሎ ማሰብ እንደሀገር የራቁን ይመስለኛል። በየጎራችን… በየጎጣችን…. በየቡድናችን መሽገን መብታችን እንዲከበር የጠየቅነው ሁሉ እንዲመለስልን እንፈልጋለን። በተቃራኒው ሙሉ ለሙሉ ሊባል በሚያስደፍር መልኩ ሁላችንም ስለሌሎች መብት… ስለሌሎች ፍላጎት መሟላት… እንኳን ልንተባበር መስማት አንፈልግም። የኛ ባልናቸው ብልጣ ብልጦች የተነገረንን ሁሉ ደጋግመን ለራሳችን እየነገርን እኛ ብቻ ተበዳይ…. እኛ ብቻ ተገፊ…. እንደሆንን ይሰማናል። እናም ልዩነታችንን በትንሽ በትልቁ አስፍተን የገዛ ወገናችን ደስታ መነሻው የኛ ሀዘን ነው ብለን እናምንና የገዛ ሰላማችንን አጥተን የሌሎችንም ሰላም እስከማደፍረስ እንደርሳለን።
በዚህ መልኩ ጠብን ስንዘራ እንዳልቆየን ሁሉ፣ ትንሽ ግጭት ሲያጋጥም ደግሞ ያልዋልንበትን ፍለጋ “ሰላም ሰላም” እያልን መዘመር እንጀምራለን። የሰላም ዋጋዋ ምን ያህል እንደሆነ ለመገንዘብ ግን አያት ቅድም አያቶቻችን የከፈሉትን መስዋእትነት ሳይሆን በራሳችን ዘመን ባለፉት አመታት ተከስቶ ያየነውን ብቻ ብናስተውል በበቃን ነበር። አንጻራዊ በሆነ መንገድ ዛሬ እያጣጣምነው ላለው ሰላም ብዙ እንደተከፈለ ባለቤቶቹ ነንና ምስክር አያሻንም። እንደ ሀገር የደረሰብን ቁሳዊ አካላዊና ስነልቦናዊ ቁስል ገና አልተፈወሰም።
በእርግጥ ባለፉት ተከታታይ ወራት እየሰማናቸው ያሉ የስምምነትና የአብሮነት ዜናዎች ምን አልባትም ሁላችንም ውስጥ የፈጠሩብን ደስታ እንዳለ የሚካድ ሀቅ አይደለም። ከዋና ዋና መገናኛ ብዙሀን እስከ ማህበራዊ ሚድያ የሚወራው ሁሉ የመጨባበጥ የመተቃቀፍ ከሆነ ውሎ አድሯል። መሽቶ በነጋ ቁጥር የሰቀቀን ዜና ለህዝባችን ለማድረስ የሚናፍቁት መርዶ ነጋሪ አንዳንድ የማህበራዊ ሚድያዎችና ነውጠኛ ፖለቲከኞችም ሳይወዱ በግዳቸው አፋቸውን ለመዝጋት ተገደዋል።
ይህም ሆኖ የሀገራችንና የህዝባችንን ሰላም በዘላቂነት ለማረጋገጥ የተሰሩትም ሆነ እየተሰሩ ያሉት ስራዎች የመጨረሻው ግብ ላይ ደርሰዋል ማለት አይደለም። ዝናብ ሲያባራ በአንድ ጊዜ እንደማይቆም ሁሉ፤ እዚህም እዛም ተስፋ ባልቆረጡ የጥፋት መልእክተኞች ጠብ ጠብ የሚሉ ነገሮች መኖራቸው አይቀርም። ለዚህ ደግሞ እኛ ኢትዮጵያውያን እንደ ህዝብ ምላሻችን በሶስት ነገሮች ላይ የተቃኘ ሊሆን ይገባል የሚል ምልከታ አለኝ። አንደኛውና ቀዳሚው ከሁሉም በላይ በህግ የበላይነት ማመንና ለህግ ተገዢ መሆን ነው። ይህንን ስል ለራሳችን ብቻ ሳይሆን በሀገራችን ጉዳይ ጥያቄም ሆነ ቅሬታ ያለው ማንኛውም አካል በህግ ማእቀፍ ውስጥ ብቻ መንቀሳቀስ እንዳለበት በመቀበል ከዚህ ውጪ የሆኑ አካሄዶችን በተግባርም በንግግርም አምርረን ልንቃወም ይገባል።
ምክንያቱም ከላይ እንዳነሳሁት ዛሬም ድረስ ሀሳብን በሀይል ለማራመድ የሚንቀሳቀሱ አካላት መኖራቸውን እያየን በመሆኑ ነው። ሲሆን ሲሆን እነዚህ አካላት አንዳች ጎራ በመፍጠር ራሳቸውን የመጨረሻ መደበቂያቸው በማድረግ ሰላማችንን የሚነሱን በመሆኑ እዛው በእንጭጩ ከሀሳባቸው ጀምሮ ልንሞግታቸው ይገባል። ሀሳባችንን ተቀብለው ማንኛውንም አመለካከታቸውን በሰላም የማያራምዱ ከሆነ ደግሞ እንደ ማህበረሰብ በያለንበት የአጥፊዎች መሸሸጊያ ከመሆን መጠበቅ አለብን። ለእነሱ የመጣ እሳት ለእኛ ብርሃን ብቻ ሳይሆን ጥፋትም መሆኑ አይቀርም።
ሁለተኛው ጉዳይ፣ እንደ ህዝብ ከመሪዎቻችን ጋር ያለንን ግንኙነት ማጠናከር የሚጠበቅብን ይሆናል። ህዝብ እንደ ህዝብ ከመሪዎቹ ጋር ያለውን ግንኙነት የሚያጠናክረው እነሱ ትክክል ስለሰሩ ለመደገፍ በርቱ ቀጥሉ ለማለት ብቻ አይደለም። ይልቁንም የተሳሳቱ ነገሮችም ካሉ በቅርበት በመከታታል በወቅቱ ሰላምን በማያደፈርስ ጥፋት በማያስከትል መልክ እንዲስተካከሉ ለማድረግ እድል የሚሰጥ በመሆኑም ነው።
ሶስተኛውና መሰረታዊ ጉዳይ ባለፉት አመታት ውድቀታችንን መለያየታችንን በሚሹ አካላት የተሸረበብንን የእነሱና የእኛ አመለካከት መናድ ነው። ለሺ ዘመናት ስንኖር በውስጣችን ያለ ተፈጥሯዊ ልዩነት አንድነታችንን ህብረታችንን አፈራርሶት አያውቅም። የጣልያንን ወራሪ ከአንዴም ሁለቴ ገጥሞ የሀገሩን ነጻነት ያስጠበቀው ህዝብ አንድ ኢትዮጵያዊ በመባል ቢገለጽም የየራሱ ቋንቋ ባህልና ማንነት ያለው ኩሩ ህዝብ ነው።
ዛሬም ያለው ይህው የየራሱ የሚያኮራ ማንነት ህዝብ ነው። ልዩነቶቻችን ደግሞ የውበታችን የኩራታችን ምንጭ ናቸው። እነዚህን ልዩነቶቻችንን አምነን ስንቀበልና የእኛ ስናደርጋቸው አንድነታችን የጸና ፤ ህብረታችን የተጠናከረ ይሆናል። ይሄ ያንተ አይደለም አልያም ይሄ አንተ አይደለህም እያሉ ሊበጣጥሱን የሚመጡትም መግቢያ ቀዳዳ አያገኙም። ይልቁንም ልዩነታችን የመለያያ ጉዳያችን አለመሆኑን ሲረዱ እነሱም እንደኛው ልዩነታችንን በውበትነት ለመቀበል ይገደዳሉ።
ባጠቃላይ እንደ ህዝብም እንደ ሀገርም የተጀመረው ሰላማችን እንዲጸና እንደ ዜጋ ከእኛ ብዙ እንደሚጠበቅ ልንገነዘብ ይገባል። ኢትዮጵያ የእኛ እንደመሆኗና ሰላሟ ሲናጋ እንደምንጎዳ ሁሉ ሰላሟን ለማስጠበቅም ቀዳሚ ተሳታፊዎች እኛው መሆን አለብን። በመሆኑም ትናንት በብዙዎች መስዋእትነት የተጠበቀልንን ሰላም ለማስቀጠል እኛም በየደረጃው ቢያንስ ለችግር መነሻና አባባሽ ባለመሆን ብዙ እየከፈልን ልንጠብቀው ይገባል እላለሁ።
በጋዜጣው ሪፖርተር
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 25/2015