ምድር ላይ ህይወት እስካለ ድረስ ፍጥረታት በሙሉ ኑሯቸው በተቃርኖዎች ታጅቦ እና ታጅሎ እንዲኖሩ ይገደዳሉ። ምክንያቱም ተቃርኖዎች ተፈጥሯዊ ስለሆኑ። ከዚህ ጋር ተያይዞ ታዋቂው የማርክሲዝም ፈላስፋ ሄግልም ተቃርኖን «Everything inherently contradictory » ሲል ገልጸዋል።
ተቃርኖዎች በሰዎች ብቻ የሚፈጠሩ የሚመስለን በርካቶች ነን። ይህ ትክክል አይደለም። ምክንያቱም አብዛኛውን ጊዜ ተቃርኖዎች የሚፈጠሩት በተፈጥሮ ነውና። ይሁንና ተፈጥሮ ያመጣቻቸውን ተቃርኖዎች የምንፈታበት ዘዴ እና ጥብብ ግን የሰዎችን የአስተሳሰብ ደረጃ አጉልቶ ሊያሳየን ይችላል። በነገራችን ላይ በመላው ዓለም የሚታዩ እድገቶች በሙሉ የተቃርኖ ውጤቶች መሆናቸውን መገንዘብ ያስፈልጋል። ስለሆነም ለአንድ አገር ሁለንተናዊ እድገት ለማስቀጠል የተቃርኖዎች መኖር የግዴታ ነው። ነገር ግን ምን አይነት ተቃርኖ ? የሚለውን መለየት ያስፈልጋል።
የተቃርኖ መነሻቸው እና አይነታቸው በጣም በርካታ በመሆናቸው የተቃርኖ አይነቶችን አንድ፤ ሁለት ብለን መዘርዘር አንችልም። ይሁንና ጠቅለል አድርገን ስንመለከት ተቃርኖዎችን የተሳከሩ (ጤናማ ያልሆኑ) እና ጤናማ ብለን በሁለት ልንከፍላቸው እንችላልን። ይህ የራሴ አስተሳሰብ ነው። የፖለቲከኞች ወይም የፈላስፎች ያሉት አይደለም። ጤናማ ተቃርኖዎች የአንድን አገር ሁለንተናዊ እድገት ያፋጥናሉ። ከላይ ለመግለጽ እንደተሞከረው በመላው ዓለም የሚታዩ እድገቶች በሙሉ የተቃርኖ ውጤቶች ናቸውና። በአንጻሩ ተቃርኖዎች የተሳከሩ እንደሆነ ደግሞ የሚያስከትሉት ችግርም እጅጉን ሰቅጣጭ ይሆናል።
በዓለማችን በተለያዩ አገራት በፖለቲካዊ፣ ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ መሰረት ያደረጉ ደም አፋሳሽ ግጭቶች ውስጠ ምክንያታቸው የተሳከሩ ተቃርኖ ስለመሆናቸው ማንም የሚረዳው ነው። ለአብነት ያህል የሩቆቹን ትተን በቅርብ በሶሪያ፣ በየመን፣ በሊቢያ እና በደቡብ ሱዳን እንዲሁም ከሰሞኑ በሱዳን የተከሰቱ ግጭቶችን መንስኤ ስንመለከት በቡድኖች መካከል የሚፈጠሩ ጤናማ ያልሆነ ወይም የተሳከረ ተቃርኖ ነው። በእኛ አገርም በተለይ በሰሜኑ ክፍል ተከስቶ የነበረው ጦርነት ዋና ምክንያት የተሳከረ ተቃርኖ የወለደውን መሆኑን የሚያጠራጥር አይደለም።
የተሳከረ ተቃርኖ ሲያጋጥም «በሰጥቶ መቀበል » መርህ በሰከነ መልኩ ተቃርኖዎችን ማስታረቅ ይገባል። ምክንያቱም በተሳከረ ተቃርኖ ሳቢያ በሰው ህይወት መልሶ መተካት አይቻልምና፤ በንብረት ላይ የሚያስከትለው ውድመት ለመተካት በርካታ የጉልበት እና የገንዘብ ወጭዎችን ይጠይቃልና። ይህም አንድን አገር እድገት ክፉኛ ወደ ኋላ ይጎትተዋል።
የተሳከሩ ተቃርኖዎችን በግብዝነትም ወይም ግብታዊነት (spontanus) ለመፍታት መሞከር ያልቦካ ሊጥን ምጣድ ላይ አፍስሶ እንደማነኮር የሚቆጠር ነው። የአልቦካ ሊጥ ምጣድ ላይ ማፍሰስ አንደኛ ጉልበታችንን ያባክናል። ሁለተኛ ኢኮኖሚያችንንም ይጎዳል። ስለዚህ ጥሩ እንጀራ ለመጋገር መጀመሪያ ሊጡ መቡካት ይጠበቅበታል። ምጣድ ስላለን ብቻ ግን ያልቦካን ሊጥ እንጀራ ማድረግ አይቻልም። ምክንያቱም ሁሉም ነገር ስርዓት አለውና።
ከጉልበት ይልቅ ውይይት ተቃርኖዎችን ለማስታረቅ ሁነኛ መፍትሄ ተደርጎ መወሰድ አለበት። ሁሌም ቢሆን የተሳከሩ ተቃርኖዎችን በውይይት እንጂ በጉልበት ለመፍታት መሞኮር ትርፉ ኪሳራ መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል። ከሰሞኑ በሰሜኑ የአገራችን ክፍል ተከስቶ የነበረውን ችግር የተፈታበት እና ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት የተሄደበት እርቀት ደግሞ የጤናማ ተቃርኖ ውጤት መሆኑን ለመረዳት የሚከብድ አይደለም።
የሚገርመው በዚህ ጤናማ በሆነ ተቃርኖ ውስጥ ስለምን ሰላም ወረደ ? በሚመስል መልኩ የተሳከረ ተቃርኖ ያንጸባረቁ ኃይላት በርካቶች መሆናቸው ተመለከትኩ። በእርግጥ ብዙ አልተገረምኩም! ምክንያቱም በኢትዮጵያ ዘመናዊ የፖለቲካ ታሪክ በተለይም ደግሞ ከጣሊያን ዳግም ወረራ በኋላ የተፈጠሩ ፖለቲከኞች አብዛኛዎቹ በኢትዮጵያ መጥፋት ላይ የራሳቸውን ኪስ ለማደለብ የሚንቀሳቀሱ ስለሆኑ። ከሰሞኑ የነበረውን ጤናማ ተቃርኖ ተመልክተው ሂስ ለመስጠት የሞከሩትም እነዚህ በህዝቦች ግጭት ትርፍ የሚያጋብሱ ኃይላት ናቸው።
የሚገርመው እነዚህ ኃይላት አብዛኛዎቹ ዲያሌክታዊ (DIALECTICS) አስተሳሰብ አራማጅ ነን ይላሉ። በተግባር ግን ዲያሌክታዊ አስተሳሰብን ሲያራምዱ አልተመለከትናቸውም። ምክንያቱም ዲያሌክታዊ (DIALECTICS) አስተሳሰብ የሚያራምዱ ሰዎች ነገሮችን በመመርምር በጥልቀት የሚከራከሩ እና የሚወያዩ፤ በክርክራቸው እና በውይይታቸውም የነገሮችን እውነተኛ መዳረሻ መርምረው የሚያገኙ ናቸው። ዲያሌክታዊ ማለትም ይህ ስለሆነ።
ፈላስፎች እንዲህ ይላሉ” አይነ ስውር ያለ መሪ ሩቅ መንገድ ለመሄድ ይቸገራል። ለመሄድ ቢሞክር ብዙ ጉዳቶች ይደርሱበታል” ከሰሞኑ የተፈጠረውን የሰላም ስምምነት ያልተዋጠላቸው ኃይሎችም ከራሳቸው ውጭ ማንንም የማያደምጡ ግብዞች መሆናቸውን ከቀደመ ታሪካቸው መገንዘብ ይቻላል። በነገራችን ላይ ከሰሞኑ በአገራችን የተሳከሩ ተቃርኖዎችን ለማስወገድ የተሄደበት እርቀት እጅግ የሚደነቅ እና ይበል የሚያሰኝ ነው።
የፕሪቶሪያውን የሰላም ስምምነት ተከትሎ «ጦርነት ይብቃ ሰላምን እናጽና» በሚል መሪቃል ከሰሞኑ በወዳጅነት አደባባይ በተካሄደው ውይይት የተለያዩ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት እንደገለጹት፤ ሁለቱ ጎራዎች ሰላምን ለማምጣት የሄዱበትን እርቀት እውቅና ሰጥተው እና አመስግነዋል፤ የስምምነቱ አተገባበርም በፕሪቶሪያው ስምምነት መሰረት መፈፀም እንዳለበት አጽኖት ሰጥው ሲናገሩ ሰምተናል።
እውነት ነው ! የሰላም አተገባበር ሂደቱ የፕሪቶሪያውን ስምምነት መሰረት ያደረገ መሆን ይገባዋል። ከዚህ በተጨማሪ አፈጻጸሙ በታሰበው ልክ እንዲሄድ የሚደረጉ ማናቸውም ዓይነት እንቅስቃሴዎች መቶ በመቶ ግብታዊነት (spontanus) የጸዱ መሆን አለባቸው። ግብታዊነትን ትርጉም ለመረዳት መጀመሪያ ንቃተ ህሊና የሚለውን መረዳት ያስፈልጋል። ሰዎች የታሪክን አመጣጥ ተረድተው፤ የህብረተሰብን ህግጋቶች ተከትለው እንዲሄድ ሲያደርጉ ንቃተ ህሊናቸው ዳብሯል ይባላል። ነገር ግን ታሪክን በዘፈቀደ እንደአመጣጡ እየተረጎሙ እና የአንድን ማህበራዊ ህጎች እየጣሱ ለመሄድ መሞከር ግብታዊ አካሄድ ይባላል።
ከዚህ አንጻር ስምምነቱን በፕሪቶሪያው ስምምነት መሰረት ለማድረግ የኢትዮጵያዊውን ሁለንተናዊ ማህበራዊ ህግጋቶችን በደንብ መረዳት ከህግጋቶቹ አንጻር አፈጻጸሞቹን ቅኝታቸውን የተስተካከለ ማደረግ ያስፈልጋል። እኛ ኢትዮጵያውያን የአገራችንን ሁለንተናዊ እድገት ለማፋጠን ከፈለግን ለከዚህ በኋላ የሚኖሩን ተቃርኖዎች ጤናማ ማድረግ ያስፈልጋል። ይህን ለማድረግ ደግሞ እያንዳንዱ ዜጋ እንደዚህ ቀደሙ በዘፈቀደ በግብታዊነት (spontanus) ከሚደረጉ ንግግሮች እና ውሳኔዎች ሊታረም ይገባል።
እውነታው ሳይጠፋን ለፖለቲካ ጥቅም ሲባል ብቻ ታቀርኖዎችን እንዲሳከሩ ማድረግ ያስከፈለንን ዋጋ የሚታወቅ ነው። ከሰሞኑ የፕሪቶሪያውን የሰላም ስምምነት ተከትሎ «ጦርነት ይብቃ ሰላምን እናጽና» በሚል መሪቃል የተከናወኑ አይነት ጤናማ ተቃርኖዎች የአገረ መንግስቱን ስለሚያጸና ስለሆነ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ሊደግፈው ይገባል ባይ ነኝ ። ሰላም !
ይህ አምድ በተለያዩ ፖለቲካዊ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ዜጎች ነፃ ሀሳባቸውን የሚሰጡበት ነው።በዓምዱ ላይ የሚወጡ ጽሁፎች የዝግጅት ክፍሉን አቋም አያመለክቱም።
አሸብር ኃይሉ
አዲስ ዘመን ማክሰኞ ሚያዝያ 24 ቀን 2015 ዓ.ም