ሐሳብን በሐሳብ ማሸነፍ ያቃታቸው አካላት የወንድማችንን የግርማ የሺጥላን ነፍስ ነጥቀዋል። ልዩነትን በሠለጠነ መንገድ መፍታት ባህል በሆነበት ክፍለ ዘመን፣ በሐሳብ የተለየንን ሁሉ በጠመንጃ ለማሳመን መነሣት የጽንፈኝነት የመጨረሻው ጥግ ነው።
ተወልዶ ባደገበት አካባቢ፣ ከእኛ የተለየ ሐሳብ ማሰብ አልነበረበትም ብለው የሚያምኑ ነውጠኛ ጽንፈኞች የፈጸሙት አስነዋሪና አሰቃቂ ተግባር፣ ጽንፈኝነትን በጊዜ ታግለን ካላስወገድነው ወደ መጨራረስ እንደሚወስደን ጉልሕ ማሳያ ነው።
ነፍስህ በሰላም ትረፍ!
– ከኢፌዴሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን የተላለፈ የኀዘን መግለጫ፡-
በወንድማችን አቶ ግርማ የሺጥላ በሥራ ላይ እያሉ በታጠቁ ኃይሎች በተፈጸመባቸው ጥቃት መገደላቸውን ስሰማ ከፍተኛ እና ጥልቅ የሆነ ኀዘን ተሰምቶኛል።
አቶ ግርማ እና የግል ጠባቂዎቻቸው ላይ የተፈጸመው ድርጊት ፍጹም ተቀባይነት የሌለው፣ የሕዝባችንን እሴት የማይመጥን ነውር እና ሕገወጥ ድርጊት ነው።
አቶ ግርማ የሕዝብ ሕይወት እንዲሻሻል የተሰጠውን ሕዝባዊ ኃላፊነት እየተወጣ የሚገኝ መሪ ሲሆን ህልፈቱ ለመላው ለክልላችን እና አገራችን ሕዝቦች ከፍተኛ ጉዳት ነው።
መንግሥት ይህን ድርጊት የፈጸሙ አካላትን ለሕግ በማቅረብ ተጠያቂ እንዲሆኑ ይሠራል።
ለወንድማችን ግርማ ፈጣሪ ነፍሱን በገነት እንዲያኖረው፣ ለቤተሰቦቹ፣ ለወዳጅ ዘመዶቹ እና መላው ሕዝባችንም መጽናናትን እንዲሰጥልን እመኛለሁ።
– ከአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት የተሰጠ መግለጫ፡-
ሚያዝያ 19 ቀን 2015 ዓ.ም ከሰዓት በኋላ የብልፅግና ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ አባል እና በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የብልፅግና ፓርቲ የአማራ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ የተከበሩ አቶ ግርማ የሺጥላ እና የግል ጥበቃዎቻቸው ላይ የመንግሥትና የድርጅት ሥራዎችን በሰሜን ሸዋ ዞን ሠርተው ከመሀል ሜዳ ወደ ደብረ ብርሃን ሲመለሱ ልዩ ቦታው መንዝ ጓሳ አካባቢ በታጠቁ ፅንፈኛ ኃይሎች በደረሰባቸው ጥቃት ሕይወታቸው አልፏል::
በደረሰው ልብ ሰባሪ ጥቃት የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት የተሰማውን መሪር ኀዘን ይገልጻል፡፡ እነዚህ ፅንፈኛ ኃይሎች በሀሳብ ትግል ማሸነፍ ያልቻሉትን በኃይል ለማስፈፀም ያደረሱት ጥቃት ዓላማውን ማሳካት የማይችልና ጊዜው ያለፈበት፣ ዘመኑን ያልዋጀ የጥፋት መንገድ ስለሆነ አምርረን የምንታገለው ተግባር ነው፡፡
እነዚህ ፅንፈኛ ኃይሎች በክልሉ ውስጥ የሚፈጽሙትን ሥርዓት አልበኝነትና የሽብር ድርጊት ለመከላከል፤ ለመቆጣጠርና ሕግ ለማስከበር የክልሉ መንግሥት እርምጃ ይወስዳል:: የጥቃቱን አድራሾችም ለሕግ ያቀርባል፡፡ ማንኛውም በጥቃቱ የተሳተፉ ኃይሎችንና ተባባሪዎችን ሁሉ ከያሉበት ለሕግ በማቅረብ አስፈላጊው ፍትሕ እንዲረጋገጥ ይደረጋል፡፡
መላው የክልላችን ሕዝብ የተፈጠረውን የሽብር ድርጊት ከማውገዝ ጀምሮ ወንጀለኞች ለሕግ ቀርበው ፍትህ እንዲረጋገጥ፣ አስፈላጊውን ትብብር እንዲያደርግና እንዲረጋጋ ጥሪ እናቀርባለን፡፡
የጥፋት ኃይሎች ከዚህ በላይ ዓላማ ያላቸው እና ክልሉን የማፍረስ ተልዕኮ ይዘው የሚንቀሳቀሱ መሆኑ የሚታወቅ ሲሆን ከዚህ በኋላ የክልሉ መንግሥት እንደማይታገስ እና ጥብቅ እርምጃ እንደሚወስድ እናረጋግጣለን፡፡
የክልሉ መንግሥት ለቤተሰቦቻቸው፤ ወዳጆቻቸው፤ ለሥራ ባልደረቦቻቸው እንዲሁም ለመላው የክልላችን ሕዝብ የተሰማውን ጥልቅ ኀዘን ይገልጻል፡፡ ፈጣሪ ነፍሳቸውን በአፀደ ገነት ያሳርፍልን!
የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት
ሚያዝያ 19 ቀን 2015 ዓ.ም
ባሕር ዳር
– የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ዶክተር ይልቃል ከፋለ ያስተላለፉት የኀዘን መግለጫ:-
ወንድማችን አቶ ግርማ የሺጥላ በሥራ ላይ በነበረበት በታጠቁ ኃይሎች ግድያ ተፈጽሞበታል። እንዲህ ዓይነት እብሪተኝነት ውድቀትን እንጂ ድልን አያጎናጽፍም። ጥፋትን እንጂ ሰላምን አይሰጥም።
የሕዝባችን የቆየ መገለጫው ሥርዓታዊነት፣ ፍትሐዊነትና እኩልነት ነው። ከዚህ ታሪኩና ሥነ ልቦናው ጋር የሚቃረኑ ተግባሮች በሙሉ ሥርዓት አልበኝነት የወለዳቸው ናቸው።
በሕግና ሥርዓት እንጂ በደቦ ፍርድ የግልም ሆነ የቡድን፤ እንዲሁም የሕዝብም ሆነ የአገር ጥቅምና ፍላጎት ማሳካት አይቻልም። ምክንያቱም የሥርዓት አልበኝነት የመጨረሻ መዳረሻው ጥፋትና መጠፋፋት ነው።
ስለሆነም የክልላችን ሕዝብ ዘላቂ ሰላሙን ለማረጋገጥ እንዲህ ዓይነት ሥርዓት አልበኝነትንና ሕገወጥ ተግባሮችን ከመንግሥት ጎን ቆሞ ሊያወግዝና ሊታገል ይገባል።
በወንድማችን አቶ ግርማ የሺጥላ ህልፈት የተሰማኝን ጥልቅ ኀዘን በክልሉ መንግሥትና በራሴ ስም እየገለጽኩ፤ ለክልላችን ሕዝብ፤ ለቤተሰቦቹና ለወዳጅ ዘመዶቹ በሙሉ መጽናናትን እመኛለሁ።
– የኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት:-
የኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በክቡር ግርማ የሺጥላ ህልፈተ-ሕይወት የተሰማውን ጥልቅ ኀዘን ይገልፃል::
የብልጽግና ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ አባልና የአማራ ክልል የብልጽግና ፓርቲ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ክቡር አቶ ግርማ የሺጥላ ሚያዝያ 19 ቀን 2015 ዓ.ም በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን መንዝ ጌራ ወረዳ ልዩ ስሙ ጓሳ ተብሎ በሚጠራ አካባቢ የታጠቁ ፅንፈኛ ኃይሎች ባደረሱት ጥቃት የግል ጠባቂዎቻቸውን ጨምሮ ሕይወታቸው በግፍ ሊያልፍ ችሏል፡፡
ምክር ቤቱ በክቡር አቶ ግርማ የሺጥላ ሞት የተሰማውን ጥልቅ ኀዘን ገልጿል።
ክቡር አቶ ግርማ የሺጥላ በኢትዮጵያ ሕዝቦች መካከል የመቻቻልና የመከባበር የፖለቲካ ባህል እንዲያብብ፣ አብሮነትና ወንድማማችነት እንዲጠናከርና እንዲፀና ደከመኝ ታከተኝ ሳይሉ ሲለፉና ሲጥሩ ነበር።
እኩልነትና ማህበራዊ ፍትህ የነገሰባት ጠንካራ ሕብረብሔራዊት ኢትዮጵያን ለመገንባት በሚደረገው ርብርብ ክቡር አቶ ግርማ የሺጥላ ከሌሎች የሥራ ባልደረቦቻቸው ጋር በመሆን የተሰጣቸውን ታላቅ ሕዝባዊ፣ ድርጅታዊና መንግሥታዊ ኃላፊነት በልበሙሉነት፣ በትጋትና በኃላፊነት ስሜት የተወጡ አመራር ናቸው፡፡
ክቡር አቶ ግርማ የሺጥላ አገር ወዳድ፣ ብልህ ቁርጠኛ የፖለቲካ አመራር የነበሩ ሲሆን ለአገርና ለወገን ሲሉ ሙሉ ጊዜያቸውን፣ ጤናቸውን በመጨረሻም የማይተካውን ውድ ሕይወታቸውን ሰውተዋል፤ በመሆኑም የክቡር አቶ ግርማ የሺጥላ ጉልህ አገራዊና መንግሥታዊ አበርክቶ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ታሪክ ማህደር ፈፅሞ የሚዘነጋ አይሆንም። ታሪክ መዝግቦ የሚይዘው ይሆናል።
የኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በክቡር አቶ ግርማ የሺጥላና በግል ጠባቂዎቻቸው በደረሰው አደጋ የተሰማውን ኀዘን ይገልፃል፤ ለወገኖቻችን ሞት ምክንያት የሆነውንም አሳፋሪ ፅንፈኛ ድርጊትና ጥቃት በፅኑ አውግዟል።
ለቤተሰቦቻቸው፣ ለወዳጅ ዘመዶቻቸውና ለሥራ ባልደረቦቻቸው በሙሉ መፅናናትን ይመኛል።
የኢፌዴሪ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት
ሚያዝያ 20 ቀን 2015 ዓ.ም
– ከመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት የተሰጠ መግለጫ፡-
የጽንፈኝነትን ሰይጣናዊነት ያሳየ የግፍ ግድያ!
ጽንፈኝነት ብዙዎችን የሕዝብ ልጆች አሳጥቶናል። ጽንፈኞች ሰው መሆንን ይጠየፋሉ። ዛሬ የአማራ ክልል የብልጽግና ፓርቲ ጽ/ቤት ኃላፊ እና የፓርቲው ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል ግርማ የሺጥላ ባደገበት ቀዬ በጽንፈኞች በግፍ ተገድሏል። ይህም የጽንፈኛው ኃይል የመርዝ ፖለቲካ በቀዬ የማይወሰን፣ ከጓዳ ጭምር ገብቶ ቤተሰብን የሚበትን መሆኑን አሳይቶናል።
ውዱ የኢትዮጵያ ሕዝብ!
አጀንዳ አልባ የጥላቻ ፖለቲካ ዘርተው ጽንፈኝነትን በማብቀል ልጆችህን በየአደባባዩ የሚቀጥፉ የደም ነጋዴዎችን ማስቆም ካልቻልክ፣ የግፍ በትራቸውን የብዙኃኑን ቤት ማንኳኳቱ አይቀሬ ነው።
ዓላማቸው ማተራመስና አገራችንን ዕረፍት መንሣት የሆኑ አካላት አሉ። የእነዚህ አካላት አርአያዎቻቸው ዓለም አቀፍ አሸባሪዎች ናቸው። የእነርሱን ተግባር በኢትዮጵያ ለመድገምና ኢትዮጵያን ለማጥፋት በሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ ያልተፈጸሙ ዘግናኝ ተግባራትን ሁሉ ይፈጽማሉ።
ኢትዮጵያን ለማጽናትና ለማበልጸግ የጀመርነውን ትግል ጽንፈኞች አያስቆሙትም። ይሄንን ነውረኛ ዘግናኝ ተግባር የፈጸሙት የትም ቢገቡ ለሕግ ይቀርባሉ። ሌሎች በእነርሱ መንገድ መጓዝ የጀመሩ በሕግ ማስከበር እንዲቆሙ ይደረጋል።
ነብስህ በሰላም ትረፍ!
ሚያዝያ 19 ቀን 2015 ዓ.ም
አዲስ አበባ
የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት
– የብልጽግና ፓርቲ የኀዘን መግለጫ፡-
የፓርቲያችን ሥራ አስፈፃሚ አባል እና የአማራ ክልል ብልፅግና ጽ/ቤት ኃላፊ የሆኑት በአቶ ግርማ የሺጥላ በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ልዩ ቦታው መንዝ ጓሳ በተባለ አካባቢ ለሥራ እየተንቀሳቀሱ ባሉበት ወቅት በታጠቁ ፅንፈኞች በደረሰባቸው ጥቃት ሕይወታቸው አልፏል።
የብልጽግና ፓርቲ ዋና ጽሕፈት ቤት የተሰማንን መሪር እና ጥልቅ ኀዘን እየገለጽን ለመላ ቤተሰቦቹና ባልደረቦቹ ፈጣሪ ያፅናችሁ ማለት እንወዳለን።
ለመላ የአማራ ሕዝብ፣ ለፓርቲያችን አባላትና ደጋፊዎች በሙሉ መጽናናትንም እንመኛለን። ፓርቲያችን የአቶ ግርማ የሺጥላን ገዳዮች በአፋጣኝ ተከታትሎ ለሕግ እንደሚያቀርብ እና በፍትህ አደባባይም ደሙን በፍትህ እንደሚመልስ ለማረጋገጥ እንወዳለን።
በሃሳብ የተለየን ሰው በሃሳብ ሞግቶ፤ በአመለካከት የተለየን በአመለካከት ረትቶ መነጋገርና የሚበልጠውን የሚበጀውን ለአገርና ለወገን ፍሬ የሚያፈራውን ሃሳብ ማስፋትና ማሳደግ ሲቻል የሰውን ልጅ የመሰለ ክቡር ፍጡር:፣ ያውም እንደ ግርማ የሺጥላ ዓይነቱን የአገር- የሕዝብና የወገን አለኝታ የሆነ ምሁር ፖለቲከኛ በእንዲህ ዓይነት መልኩ መግደል መሸነፍ መሆኑን አሁንም ደግመን መናገር እንፈልጋለን።
የአቶ ግርማን በፅንፈኛ ኃይሎች ጥቃት መቀጠፍ ስንሰማ ልባችን በኀዘን ደምቷል። በዚያውም ልክ ፅንፈኝነትን አምርረን መታገልና ማክሰም ጊዜ የማይሰጠው ተግባር እንደሆነ አሳይቶናል።
በአገራችን እየታየ ያለው የፅንፈኝነት አስተሳሰብ እና ከአስተሳሰቡ የሚነጩ እኩይ ድርጊቶች ከፍተኛ አደጋ ውስጥ ሊከቱን እንደሚችሉ ምንም ጥያቄ የለውም። በመሆኑም ብልፅግና ፓርቲ ምልዓተ ሕዝቡን ያሳተፈ ጠንካራ የፖለቲካ ትግል በማድረግ እና ሕግ የማስከበር እርምጃዎችን በማጠናከር ጽንፈኝነትን ለመግታት ከምንጊዜውም በበለጠ ጠንክሮ እንደሚሠራ በዚህ አጋጣሚ ለመግለጽ እንወዳለን።
የብልፅግና ጉዟችን በጽንፈኞች እና ሌቦች እኩይ ተግባር ፈፅሞ አይደናቀፍም!
ወንድማችን ግርማ የሺጥላ ነፍስዎት በአፀደ ገነት ትረፍ!
ብልፅግና ፓርቲ
ሚያዝያ 19/2015
– ከአማራ ክልል ምክር ቤት የተሰጠ መግለጫ፡-
የተከበሩ አቶ ግርማ የሺጥላ ሚያዝያ 19/2015 ዓ.ም የመንግሥትና የድርጅት ሥራዎችን በሰሜን ሸዋ ዞን ሠርተው ከመሀል ሜዳ ወደ ደብረ ብርሃን ሲመለሱ ልዩ ቦታው መንዝ ጓሳ አካባቢ በአማራ ክልል በሰሜን ሸዋ ዞን ባሶና ወረና ወረዳ ቀይት ምርጫ ክልልን ወክለው የተመረጡት የክልል ምክር ቤት አባል፣ የብልፅግና ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ አባል እና በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የብልፅግና ፓርቲ የአማራ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ በተከበሩ አቶ ግርማ የሺጥላ እና የግል ጥበቃዎቻቸው ላይ በታጠቁ ፅንፈኛ ኃይሎች በደረሰባቸው ጥቃት የተሰማን ኀዘን መራራ ነው።
የአማራ ክልል ምክር ቤት ለሟቾች ቤተሰብ፣ ወዳጅ ዘመድ እና መላው ሕዝብ መጽናናትን ይመኛል።
የአማራ ክልል ምክር ቤት
ባሕር ዳር
– የኦሮሚያ ብልጽግና ፓርቲ መልዕክት፡-
ብሩህ ራዕይ በሀሳብ ድሆች አይሞትም!
የፖለቲካ አመለካከትን በዕውቀትና በእውነት ማራመድ የተሳናቸው የሀሳብ ድሆች ማሰብ የሚችሉ ባለ ብሩህ ራዕይ ሰዎችን ማጥቃት ብቸኛ አማራጫቸው ነው።
ግርማ የሺጥላ የኢትዮጵያውያንን ህብረ ብሔራዊ ወንድማማችነትና እህትማማችነት ለማጽናት ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይል ቀን ከሌሊት ሲሠራ የነበረ የቁርጥ ቀን የኢትዮጵያ ልጅ ነበር።
ሀሳብ የነጠፈባቸው ጽንፈኛ ብሔርተኞች ሰላማዊውን የሀሳብ መድረክ መቋቋም እንደማይችሉ ስለሚያውቁ ኢትዮጵያን የሰላምና የልማት ምድር ለማድረግ ዕድሜውን ሙሉ የለፋውን ብርቱ መሪ በልተውታል።
ወንድማችን ግርማ በሙሉ አቅሙ የታገለው ለሁሉም ኢትዮጵያውያን ብሔሮች፣ ሃይማኖቶችና ሌሎች ማንነቶች እኩልነትና ለዜጎች ነፃነት ነበር። ይህ ያልተዋጠላቸው የሀሳብ ቆሞ ቀሮች ብሩ ሀሳብን በጥይት መግደል የሚቻል መስሏቸው ተራማጅ ሀሳብ የነበረውን ባለ ጽኑ አቋም መሪ ሕይወት ቀጥፈዋል።
ይህን አስነዋሪ የወንጀል ድርጊት በፈጸሙ ጽንፈኛ ወንጀለኞች ላይ የሚወሰደው እርምጃ ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል።
አክራሪነትንና ጽንፈኝነትን በሀሳብ የበላይነት እያመከንን በኢትዮጵያውያን መካከል አስተማማኝ ህብረ ብሔራዊ አንድነትን፣ የሕዝቦችን እኩልነት፣ ነፃነትና ወንድማማችነትን ለማረጋገጥ የሚደረገው የሕዝቦች ትግል ተጠናክሮ ይቀጥላል።
ወንድማችን ግርማ ነፍስህ በሰላም ትረፍ!
– የከንቲባ አዳነች አቤቤ መልዕክት፡-
የአማራ ክልል ብልጽግና ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ በነበሩት አቶ ግርማ የሺጥላ መሰዋት እጅግ አዝኛለሁ።
ግርማ ላመነበት የወንድማማችነትና ህብረብሔራዊ አንድነት አላማ በጀግንነት የታገለ የአቋም ሰው ነው። ግርማን መግደል ብትችሉም ሀሳቡንና የቆመለትን አላማ መግደል አትችሉም። የጽንፈኝነት ተሸናፊ ሀሳብ እየሞተ የወንድማማችነት ሀሳብ አሸናፊ ሆኖ ይቀጥላል።
ለቤተሰቦቹ ፣ ለወዳጆቹ እና ለሥራ ጓዶቹ መጽናናትን እየተመኘሁ ፈጣሪ ነፍሱን በአፀደ ገነት ያሳርፈው።
– ከሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት የተሰጠ የኀዘን መግለጫ፡-
የሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት የብልፅግና ፓርቲ ሥራ አስፈፃሚ አባልና የአማራ ክልል ብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ግርማ የሺጥላ በፅንፈኛ ኃይሎች በደረሰባቸው ጥቃት ሕይወታቸው በማለፉ የተሰማውን ጥልቅ ኀዘን ይገልጻል።
የጥፋት መንገድን በተከተሉ፣ የአገርን ሉዓላዊነት ክብር ለማዋረድ ሌትተቀን በሚዳክሩ ኃይሎች ቅንጣት ታክል ትግላችንንና ሰላማችን አይቀለበስም።
እነዚህ ፅንፈኛ ኃይሎች በሰለጠነ መንገድ ፖለቲካዊ አካሔዳቸውን ማስፈፀም የማይችሉና ሁልጊዜ ፀብና ግጭት በመፍጠር አጀንዳቸውን ለማስፈፀም ነፍጥ የሚያነሱ ከዘመኑ ፖለቲካ ስልጣኔ አንፃር ችግሮቻቸውን በውይይት ለመፍታት አቅም የሌላቸው ፤ የህብረ ብሔራዊት ኢትዮጵያን ከፍታና አንድነት ለመናድ የሚታትሩ የአገር ጠላቶች ናቸው።
እነዚህ ፅንፈኛ ኃይሎች በፈፀሙት የወንጀል ድርጊት መላው የክልላችን ሕዝብና መንግሥት የተፈጠረውን አስነዋሪና አፀያፊ ድርጊት ከማውገዝ ባሻገር ወንጀለኞች ለሕግ ቀርበው ፍትህ እስኪረጋገጥ ድረስ ከወንድም አማራ ሕዝብና መንግሥት ጎን እንደሚቆም የክልሉ መንግሥት ያረጋግጣል።
የሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ለቤተሰቦቻቸው፣ ለወዳጆቻቸውና ለሥራ ባልደረቦቻቸው እንዲሁም ለመላው አማራ ሕዝብ የተሰማውን ጥልቅ ኀዘን ይገልጻል።
ፈጣሪ ነፍሳቸውን በአፀደ ገነት ያሳርፍልን!!
የሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት
– የሶማሌ ክልል ርእሰ መስተዳድር አቶ ሙስጠፌ ሙሁመድ መልዕክት፡-
የሶማሌ ክልል ርእሰ መስተዳድር አቶ ሙስጠፌ ሙሁመድ በአማራ ብልፅግና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ግርማ የሺጥላ ግድያ የተሰማቸውን ጥልቅ ኀዘን የገለጹ ሲሆን፤ ርእሰ መስተዳድሩ ኀዘናቸውን በገለፁበት መልእክታቸው፤ የትኛውም የፖለቲካ ልዩነት በአፈሙዝ መፍታት ጊዜ ያለፈበት ብቻ ሳይሆን ካለፍንባቸው የሩቅ እና የቅርብ ታሪኮቻችን መማር አለብን ብለዋል።
በአሁኑ ሰዓት አገራችን የአመለካከት ልዩነቶችን በሰላማዊ መንገድ እና በውይይት እንጂ በመሣሪያ አፈሙዝ መፍታትን የምትሸከምበት ጫንቃ የላትም ሲሉም አሳስበዋል።
ለሟች ቤተሰቦች፣ ለመላው የአማራ ክልል ሕዝብ እና ለወዳጅ ዘመዶቻቸው መፅናናትን በመመኘትም፤ አሁን መላው ሕዝብ ይህን ግድያ መቃወም እና በቃ ሊባል እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
– የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል መንግሥት ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ዶክተር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ መልዕክት፡-
የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት የብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊ በነበሩ በወንድሜ በአቶ ግርማ የሺጥላ ድንገተኛ ሞት የተሰማኝ ኀዘን በጣም ጥልቅ ነው::
አቶ ግርማ በሃሳብ ልዕልና የሚያምኑ፣ ለአገራዊ አንድነትና ለሕዝቦች ወንድማማችነት የሚታገሉ ኢትዮጵያዊ ነበሩ::
ለሥራ ባልደረቦቹ፣ ለወዳጅ ዘመዶቹና ለቤተሰቦቹ መጽናናትን እመኛለሁ::
ወንድሜ ነፍስህ የዘላለም እረፍት እንድታገኝ ፀሎቴ ነው::
– የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳ መልዕክት፡-
አክራሪ ኃይሎች ታታሪና ጀግና የሕዝብ አገልጋይ የነበረውን ወንድማችን አቶ ግርማ የሺጥላን ነፍስ ነጥቀዋል። ለሐሳብ ልዕልና በሐሳብ ሲታገል የነበረውን፣ በመሣሪያ ቃታ መግደል የእነዚህን ኃይሎች መሸነፍ የሚያረጋግጥ ይሆናል እንጂ፤ የሕግ የበላይነት የተረጋገጠባትና ሀሳብ የሚከበርባት አገር ከመመስረት ለአፍታም ቢሆን የሚያቆመን አይሆንም።
አክራሪዎች በዚህ ዘመን ውስጥ በሀሳብ ሳይሆን፣ በአፈሙዝ ለማሸነፍ እንዲሁም በጦርነት ስልጣን ለመያዝ ሊያስቡ ይችላሉ፤ በተጨባጭ ግን የዚህ ዓይነቱ አስተሳሰብ በዚህ ዘመን አይሠራም። ወንድማችን የአማራ ክልል ብልፅግና ፓርቲ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ግርማ የሺጥላ፣ ጠንካራ አመራርና በሀሳብ የበላይነት የሚያምን እና ይህን ለማረጋገጥ ሲተጋ የቆየ ነበር።
በድንገተኛው የአቶ ግርማ የሺጥላ ህልፈት የተሰማኝን ጥልቅ ኀዘን ስገልጽ፣ በተሰበረ ልብ ነው። ለቤተሰቦቹ፣ ለወዳጅ ዘመዶቹ፣ ለሥራ ባልደረቦቹና የትግል አጋሮቹ እንዲሁም ለመላው ሕዝባችን መፅናናትን እመኛለሁ።
ነፍስህ በሰላም ትረፍ።
– የደቡብ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ርስቱ ይርዳው መልዕክት፡-
የደቡብ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ርስቱ ይርዳው የአማራ ክልል ብልጽግና ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ በነበሩት በአቶ ግርማ የሺጥላ ህልፈተ ሕይወት የተሰማቸውን ኀዘን ገልጸዋል።
አቶ ርስቱ ይርዳው በኀዘን መግለጫቸው፤ «አክራሪ ኃይሎች ታላቅ የሕዝብ አደራን ተቀብለው በጀግንነት እና በታታሪነት አገራቸውን እና ሕዝባቸውን በቅንነት ሲያገለግሉ የነበሩትን መሪ እንድናጣ ምክንያት ሆነዋል» ብለዋል።
አሁን ባለንበት ዘመን ልዩነት በምክክር እና በውይይት መፍታት ሲቻል የመሣሪያ አፈ ሙዝን በመፍትሄነት መጠቀም ተስፋ ቢስነትን ያመላክታል ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ ጀግናችንን በሞት ብንነጠቅም እንደ አገር የጀመርነው የልማትና የእድገት ጉዞ ላፍታም ሊገታ አይችልም ነው ያሉት።
አክራሪ ኃይሎች በአቋራጭ ስልጣን ለመያዝ ያልፈነቀሉት ድንጋይ እንደሌለ ጠቁመው መግደልን አማራጭ ማድረጋቸው ምን ያህል በሕዝብ ደም የመነገድ ፍላጎት እንዳላቸው ማሳያ መሆኑን ጠቁመዋል።
አቶ ግርማ የሺጥላ በሥራ ክቡርነት የሚያምኑ የተጣለባቸውን የሕዝብ አደራ በብቃት እየተወጡ የነበሩ ጠንካራ አመራር መሆናቸውንም በኀዘን መግለጫቸው ገልጸዋል።
ለቤተሰቦቻቸው፣ ለወዳጅ ዘመዶቻቸው፣ ለሥራ ባልደረቦቻቸው፣ ለትግል አጋሮቻቸው እንዲሁም ለመላው ሕዝብም መፅናናትን ተመኝተዋል።
– የሐረሪ ክልላዊ መንግሥት የኀዘን መግለጫ፡-
የሐረሪ ክልላዊ መንግሥት በአማራ ክልል ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ በነበሩት አቶ ግርማ የሺጥላ ህልፈት የተሰማውን ጥልቅ ኀዘን የገለጸ ሲሆን፤ የክልሉ መንግሥት ባወጣው የኀዘን መግለጫ የፖለቲካ አመለካከትን በዕውቀትና በእውነት ማራመድ የተሳናቸው የሀሳብ ድሆች ማሰብ የሚችሉ ባለ ብሩህ ራዕይ ሰዎችን ማጥቃት ብቸኛ አማራጫቸው ነው ብላል።
በዚህ ዘመን ሐሳብን በሐሳብ ማሸነፍ ያቃታቸው አካላት ልዩነትን በሠለጠነ መንገድ መፍታት ባህል በሆነበት ክፍለ ዘመን፣ በሐሳብ የተለየንን ሁሉ በጠመንጃ ለማሳመን መነሣት የጽንፈኝነት የመጨረሻው ጥግ ማሳያ መሆኑን በመግለጽም፤ የክልሉ መንግሥት ለቤተሰቦቻቸውና ለወዳጅ ዘመዶቻቸው እንዲሁም ለመላው የአማራ ክልል ሕዝብ መፅናናትን ይመኛል ብሏል።
– የአማራ የምሁራን መማክርት ጉባዔ፡-
በአማራ ክልል የምሁራን መማክርት ጉባዔ በአቶ ግርማ የሺጥላ ላይ በታጠቁ ኃይሎች የተፈፀመውን ግድያ በፅኑ በማውገዝ የተሰማውን ጥልቅ ኀዘን በመግለጽ፤ የሐሳብም ሆነ የፖለቲካ ልዩነቶችን በኃይልና በመግደል ለመፍታት መሞከር ለሕዝባችን እና አገራችን ዘለቄታዊ ሰላም አያመጣም ብሏል።
የምሁራን መማክርት ጉባዔው ለኢቢሲ በላከው መግለጫ ለቤተሰቦች እና ለአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥትና ሕዝብ መፅናናትን ተመኝቷል።
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 21/2015