እንደ ልጅ መሆን ነው መደሰት መፈንደቅ ፣
ባለን ነገር ሁሉ መገረም መደነቅ፣
ሰላም ማለት ለኔ መሞላት በተስፋ፣
ነገን አምኖ መኖር ከዛሬ እንዳይከፋ፣
እርጉዝ እንደመሆን ወይ እንደ ገበሬ፣
በሆዴ ልጅ ይዤ ዘር ከአፈር ጨምሬ፣
ወልጄ ለመሳም ሙሉ ተስፋ ይዤ ዘጠኝ ወር ቆጥሬ፣
ከአፈር ያኖርኩትን ያንን መልካም ፍሬ፣
አምኖ እንደመጠበቅ በተስፋ እንደማየት
እንዲበዛ ዘሬ።
(በረድኤት ወዳጅ)
እነኝህ ስንኞች ጥቅምት 23 ቀን 2015 ዓ.ም በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶርያ በኢፌዲሪ መንግስትና በሕወሓት መካከል የተደረገውን የሰላም ስምምነት ይገልጻሉ። ባለቅኔዋ እንደገለችው ሰላም ተስፋ ነው። ሰላም እንደ ገበሬ በተስፋ ዘርቶ እሸትን፣ ምርትን በእምነት እንደመጠበቅ ነው። አዎ ! ሰላም እንደ እናት ጸንሶ በዘጠኝ ወር ልጅን በተስፋ ለማቀፍ በጉጉት ቀን እንደመቁጠርና እንደ መጠበቅ ነው ። ሰላም እንደ ህጻን ልጅ ማመን ጭምር ነው። የፕሪቶርያው የሰላም ስምምነት እንደ ገበሬ ዘር በተስፋ የተዘራ የሰላም ዘር ነው። ጥንዶች ወልዶ ለመሳም በጉጉት እንደሚጠብቁት፤ ቀን እንደሚቆጥሩለት ጽንስ ነው፤ የፕሪቶርያው የሰላም ስምምነት። ዳሩ ግን ዘሩም ሆነ ጽንሱ ዝም ብሎ በተስፋ ላይ ያነጣጠረ ተስፋ ፤ እጅን አጣጥፎ የሚጠብቁት አይደለም።
ስራን ፣ ትጋትን ፣ ላብ ማፍሰስን ፣ ጊዜን ፣ ጉልበትንና ገንዘብን ይጠይቃል። ዘሩ እንደ ግብጦ ዘር ዝምብሎ በሜዳ የሚዘራ አይደለም። ወፍ ዘራሽም አይደለም። ሌት በቁር ቀን በሀሩር ተነስቶ መሬትን መላልሶ ማረስ ፣ ደጋግሞ ማለስለስ ፣ በሰኔ ፣ በሀምሌና በነሐሴ ክረምት ደግሞ ማረም መኮትኮት ፣ ሲያሸት ደግሞ ወፍ ፣ ዝንጀሮና አሳማ እንዳይበላው ሌት ተቀን መጠበቅ ፣ ሲደርስ ደግሞ ማጨድ መከመር ፣ አውድማ መለቅለቅ ማዘጋጀት መውቃት ማበራየት ፣ በመጨረሻም ሰብስቦ ጎተራ ማስገባት፣ ቀጣዩ የምርት ወቅት እስኪመጣ በቁጠባ መጠቀም፣ ለገበያ የሚሆነውን መለየት ፣ ለከርሞ ዘር ማስቀረትን ይጠይቃል ።
ጽንስም በራሱ መንገድ ለዛውም ህይወትን አሲዞ መከታተልን መንከባከብን ፤ ህይወትን ከፍሎ መስጠትን ይጠይቃል። ሰላምም እንዲህ ነው ። ተስፋን ፣ ጀግንነት ፣ ነጭ ላብ እስኪፈስ መጣር መጋር መድከም ይጠይቃል። እንደ ችግኝ መንከባከብን ፣ ውሃ ማጠጣትን ይጠይቃል። ለሰላም ምንም ያህል ቢደከምና ማንኛውንም ዋጋ ቢያስከፍል ተወደደ አይባልም። ይገባዋልና። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይም ሆኑ መንግስታቸው እንደ ዘሩም ሆነ ጽንሱ ሰላሙን በተስፋ እየተንከባከቡት ነው። እህል ሆኖ ጎተራ እስኪገባ ፣ ልጅ ሆኖ እንዲወለድና በጤና እንዲያድግ እየተንከባከቡት ነው። በተለይ እሳቸው ገና ከጅምሮ ለሰላም ፣ በሰላም ፣ ስለሰላም ተወስደዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ወደ ኃላፊነት ከመጡበት ከወርሀ መጋቢት 2010 ዓ.ም ወዲህ ከኤርትራ የሰላም ስምምነት በመፈራረም ወደ 20 አመት የሚጠጋውን ፍጥጫ ማስወገድ ከመቻላቸው ባሻገር የተጠበቀውን ያህል ውጤታማ ባይሆንም ነፍጥ አንግበው ይታገሉ የነበሩ ታጣቂዎች ትጥቃቸውን ፈተው ሰላማዊ የፖለቲካ ትግሉን ተቀላቅለዋል። ሕወሓት ሰሜን ዕዝን አጥቅቶ ጦርነቱ እስኪጀመረ ድረስ ልዩነቱ በሰላማዊ ውይይት እንዲፈታ ያልፈነቀሉት ድንጋይ የለም። በይፋም በምስጢርም በተደጋጋሚ አሸማጋዮችን ወደ መቀሌ በመላክና በአዲስ አበባ ታዋቂ ትግራዋይን በማሳተፍ ወደ ጦርነት እንዳይገባ በታዋቂ ሰዎች፣ በሀገር ሽማግሌዎች፣ በሀይማኖት አባቶች ፣ በእናቶች አማካኝነት አስለምነዋል።
ጦርነቱ ግድ ከሆነ በኋላም በየዘመቻው ምዕራፍ የተናጠል የተኩስ አቁም በማድረግ የሰላም ጥሪ ያደርጉ ነበር። ሰራዊቱ በድል እየገሰገሰ ሳይቀር የወይራ ዝንጣፊ ይልኩ ነበር። በሶስተኛው ዘመቻም የመከላከያ ሰራዊት በወታደራዊ ትንተና ጦርነቱን እየቋጨ ባለበት ሰዓት እንኳ ፤ ከዚህም ከዚያም የሚሞተው ሰው ነው ፤ የሚተኮሰውም ዶላር ነው በማለት ጦርነት አይበጀንም በማለት ያለምንም ቅድመ ሁኔታ መንግስታቸው የሰላም ድርድር ለማድረግ ዝግጁ መሆኑን ገለጹ። የሰላም ስምምነቱ ከተደረገ በኋላም የሌላውን ወገን ምላሽ ሳይጠብቁ ረጅም ርቀት ተጓዙ። ምንም እንኳ ነገሮች ሁሉ አልጋ ባልጋ ባይሆኑም ለሰላም እንደታመኑ አሉ። ለዚህ ነው ለሰላም ፣ በሰላም፣ ስለሰላም ተወስደዋል የምለው።
ሌላው የሰላም ስምምነት ተፈረመ ብለው ስራው ያውጣው ከማለት ይልቅ ስምምነቱን ተቋማዊ በማድረግ ስጋና ደም እንዲኖረው በማድረግ ህይወት ስለሚዘሩበት ለሌላው ወገንም ሆነ ለአደራዳሪዎች ክፍተት ባለመስጠት ሰበብና ምክንያት ስለሚያሳጡ ሳይወዱ ለሰላሙ ቁርጠኛ እንዲሆኑ ያደርጋቸዋል። “ጦርነት ይብቃ ሰላምን እናጽና”በሚል መሪ ሃሳብ በአዲስ አበባ ወዳጅነት ፓርክ ባለፈው እሁድ ሚያዚያ 15 የተካሄደው የእውቅና እና ምስጋና መርሃ ግብር ስምምነቱን ተቋማዊ የማድረግ ሒደት አካል አድርጌ ነው የምመለከተው። የምስክር ወረቀትና ዋንጫ ከመስጠት፤ የሚዲያ ሽፋን ከማግኘት የተሻገረ አንድምታ ስላለው ከነጠላ ዜና ሽፋን በላይ ሊተነተንና ሊተረጎም ይገባል። በዚህ መርሀ ግብር ከታደሙና እውቅና የተሰጣቸው አደራዳሪዎች መልዕክትም የሰላም ስምምነቱ ተቋማዊ ወደ መሆን ደረጃ ከፍ ማለቱን ያሳያል።
የፕሪቶርያው የሰላም ስምምነት ዋና አደራዳሪ፤ በአፍሪካ ህብረት የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልእክተኛ የናይጀሪያ የቀድሞ ፕሬዚዳንትና እውቅና ከተሰጣቸው ቀዳሚ የሆኑት ኦሊሴጉን ኦባሳንጆ በዚሁ መርሀ ግብር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ ለሰላም ስምምነቱ ተግባራዊነት ላደረጉት ብርቱ ጥረት ምስጋና አቅርበዋል። በኢትዮጵያ የተደረሰው የሰላም ስምምነት የአፍሪካን ችግር በአፍሪካውያን መፍታት እንደሚቻል ትምህርት የሰጠ ነው። በሰላም ስምምነቱ አተገባበር መጀመሪያ ሁሉም ነገር አስቸጋሪ ቢመስልም በስኬት እንደሚጠናቀቅ ጽኑ እምነት ነበረኝ ሲሉ ልዩ መልዕክተኛው ተናግረዋል።
በሰላም ሂደቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ በተለየ መልኩ ለነበራቸው ቁርጠኝነትና ብርቱ ጥረት የላቀ ምስጋና ይገባቸዋል ካሉ በኋላ በማስከተል በኢትዮጵያ የተደረሰው የሰላም ስምምነት ስኬት ሁሉንም አፍሪካዊ ያኮራ መሆኑን ጠቅሰው፤ ትጥቅ የፈቱ ታጣቂዎችን መልሶ ለማቋቋም እየተደረገ ያለውን ጥረት ሁሉም አካል እንዲደግፍ ኦባሳንጆ ጥሪ አድርገዋል።
የትምህርት ቤቶች፣ ጤና ጣቢያዎች ዳግም ስራ መጀመር የትራንስፖርት አገልግሎት መከፈት የሰላም ሂደቱን ውጤታማነት የሚያሳዩ መሆኑን ጠቅሰው፤ የሰላም ስምምነቱን ሙሉ ለማድረግ ቀጣይ ስራዎችን አጠናክሮ መቀጠል ይገባል ሲሉ አሳስበዋል። የሰላም ስምምነቱን የተሟላ ለማድረግ ሁሉም አካላት በጋራ ሊሰሩ እንደሚገባና በሰላም ስምምነቱ ያገኘነውን ስኬት ስናከበር ለሰላም ያለንን ቁርጠኝነት በተግባር በማረጋገጥ ሊሆን ይገባል በማለት መክረዋል። በጦርነቱ ጉዳት የገጠማቸውና የተፈናቀሉ ዜጎችን መልሶ ለማቋቋም የሚደረገውን ጥረት ሁሉም አካላት እንዲያግዙ በማሳሰብ ፤ ከዚህ በኋላ በህዝቦች መካከል ዕርቅ በማስፈን፣ የመልሶ ማቋቋም ተግባራትን በማፋጠን ሰላምን፣ ደህንነትንና ልማትን ማፋጠን ይገባል። ኢትዮጵያ በሁሉም መስክ የአፍሪካ መሪ ለመሆን የጀመረችውን ጥረት በስኬት እንደምታጠናቅቅ ያላቸውን ተስፋም ገልጸዋል።
ሌላው አደራዳሪና የቀድሞ የኬንያ ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬኒያታ በበኩላቸው፤ የአፍሪካ አገራት በሰሜን ኢትዮጵያ አጋጥሞ የነበረው ችግር ከተፈታበት መንገድ ትምህርት ሊወስዱ ይገባል። በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላም ለማምጣት የተከናወነው ስራ ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለመላው አፍሪካ ኩራት ስለመሆኑ፤የዛሬው እለት የኢትዮጵያውያን ቀን ነው ያሉት ኡሁሩ ኬንያታ “ለሰላም ጥረት ያደረጋችሁ ሁሉ እና መላ ኢትዮጵያዊያን እንኳን ደስ አላችሁ” ብለዋል።
በኢትዮጵያ የሚፈለገው ሰላም እውን ሆኗል፤ በመሆኑም በግጭት ውስጥ ያሉ የአፍሪካ አገራት በሰሜን ኢትዮጵያ የነበረው ችግር ከተፈታበት መንገድ ትምህርት በመውሰድ ሰላም ማምጣት አለባቸው፤ አፍሪካ ለራሷ ችግር በራስ መፍትሄ ማምጣት እንደምትችል በተግባር አሳይታለች ያሉት የቀድሞው የኬኒያ ፕሬዚዳንት በኢትዮጵያ የመጣው ሰላም ለመላ አፍሪካዊያን ጥሩ ተምሳሌት ተደርጎ ሊወሰድ ይገባል ነው ያሉት። መጪው ጊዜ ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብና አጠቃላይ ለአፍሪካ ዘላቂ ሰላምና ብልጽግና እውን እንዲሆን ምኞታቸውን ገልጸዋል ።
የፕሪቶርያው የሰላም ስምምነት ኢትዮጵያ ቅኝ ያልተገዛች አፍሪካዊት ሀገር ብቻ ሳትሆን በሰላም ረገድም አርዓያነትን ያረጋገጠችበት አጋጣሚ መሆኑን የደቡብ አፍሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ናሌዲ ፓንዶር አስታውቀው፤ በሰሜን ኢትዮጵያ የነበረው ጦርነት የተፈታበት መንገድ የአፍሪካን ችግር በአፍሪካ መፍትሄ መቅረፍ እንደሚቻል ያረጋገጠ ፤ በአፍሪካ ሕብረት መሪነት የተደረሰው የሰላም ስምምነት የኢትዮጵያውያን ድል ብቻ ሳይሆን እንደ አፍሪካዊያን የሁላችንም ኩራት ሲሆን ፤
የፕሪቶርያ ሰላም ስምምነት የመንግስትና የሕወሐት አመራሮች ወደ ሰላም ለመምጣት ቁርጠኛ አቋም ማሳየታቸውን አስታውሰው፤ አፍሪካ ሕብረትን እና ሂደቱ እንዲሳካ ሚና የተወጡ አካላትን አመስግነው፤ የፕሪቶርያው የሰላም ስምምነት ዕውን መሆን የጥይት ድምጽ የማይሰማባት አፍሪካን ዕውን ለማድረግ ለተያዘው ግብ ስኬት መሆኑን ጠቅሰው፤ ለሰላም ስምምነቱ ዘላቂ ትግበራ ሁሉም ጥረት ማድረግ እንዳለበት አሳስበው ፤ የሰላም ስምምነቱ ስኬት ወረቀት ላይ መፈረሙ ሳይሆን በተግባር መሬት ላይ ያለው ትግበራ መሆኑን ያወሱት ሚኒስትሯ፤ የድህረ ሰላም ስምምነት ትግበራው ባደረጉት ክትትል በትግራይ ክልል የሰላም ስምምነቱ አፈጻጸም በጥሩ ደረጃ እየተተገበረ መሆኑን ጠቁመው፤ በቀጣይም ትግበራው ተጠናክሮ እንዲቀጥል ለመከላከያ ሰራዊትና ለሚመለከታቸው አካላት ድጋፍ እንዲደረግ ጥሪ አስተላልፈዋል።
ስምምነቱ ዘላቂ ሰላም፣ ልማትና አንድነት ለማምጣት የተገባ ቃል በመሆኑ ለተግባራዊነቱ ሁሉም ወገኖች በቁርጠኝነት እንዲሰሩ ፤ መሰል የሰላም ሂደቶች አፍሪካ በ2063 አጀንዳ የበለጸገች፣ ሰላሟ የተረጋገጠ፣ አካታች እና ዘላቂ ልማት የተረጋገጠባት አህጉር የማድረግ ግብ እንዲሳካ ሁነኛ አስተዋጽኦ እንዳላቸው አንስተው ፤ ኢትዮጵያ ቅኝ ያልተገዛች ሀገር ብቻ ሳትሆን ችግሮችን በሰላም በመፍታት ለአፍሪካ አርዓያነቷን ያረጋገጠችበት አጋጣሚ መሆኑን ጠቅሰው ፤ እንደ ኢዜአ ዘገባ በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በተቀረው የአፍሪካ ክፍል የጥይት ድምጽ የማይሰማባት አህጉር መፍጠር፣ ሰብዓዊ መብት መከበር፣ የዜጎችን ነጻነትና ብልጽግና ዕውን ማድረግ እንዲቻል በጋራ መስራት እንደሚገባም ጥሪ አቅርበዋል።
የትግራይ ህዝብ አሁን ያገኘው ሰላም ወደ ኋላ እንዲመለስ ፈጽሞ አይፈቅድም ሲሉ የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ርእሰ መስተዳድር ጌታቸው ረዳ ገልጸው፤”ከይዋጣልን መንፈስ ወጥተን ለኢትዮጵያ ሰላም በየቀኑና በጋራ መስራት አለብን”ካሉ በኋላ በማስከተል፤ ሰላምን ማስፈንና በጋራ መልማት የጋራ እጣ ፈንታችን በመሆኑ የጀመርነውን የሰላም መንገድ ማጽናት፤ ፖለቲከኞች ከግጭት አባባሽ አስተሳሰብ ተላቀው ለሰላም ቅድሚያ በመስጠት በትብብር መስራት እንደሚገባቸውም ፤ በሰላም ሂደቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ፤ የነበራቸው ቁርጠኝነትና የሄዱበት ርቀት የሚደነቅ ስለመሆኑ ጠቅሰው፤ የሰላም ርምጃዎች እንዲሰፉ ሁሉንም አቅም በማስተባበር መስራት አለብን ብለዋል ።
እንደ መውጫ
በፖለቲካና ወታደራዊ አመራሩ በፕሪቶርያና በናይሮቢ እውን የሆነው የሰላም ስምምነት እንዲጸናና ዘላቂ እንዲሆን የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነቱ በአስቸኳይ ሊጀመር ይገባል። የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነቱ ሲባል ግን ከአዳራሽና ከሚዲያ ፍጆታ የተሻገረና የልብ ለልብ ሊሆን ግድ ይላል። ያንን ፈታኝ ሁለት አመት እንዴት እንዳለፉት በግልጽ ሊነጋገሩ ይገባል። የትግራይ ሕዝብ ከወንድሞቹ የአማራና የአፋር ሕዝቦች ጋር መገናኘት አለበት። የአማራና የአፋር ሕዝቦችም እንዲሁ ከትግራይ ሕዝብ ጋር ፤ የትግራይ ሕዝብ ከመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር መገናኘትና የተቋረጠውን ግንኙነት ማደስ ያስፈልጋል። ኢትዮጵያውያን ያለፉበትን ሰቆቃ በማስታወስ ይህን መሰል ዘግናኝ ጦርነት እንዳይደገም መማማል ቃል ኪዳን መግባባት አለባቸው። ሀዘን ለቅሶ ሊደራረሱ ፣ እርስበርስ ሊጽናኑ ፣ እንባ ሊተባበሱ ይገባል ። የልብን በልብ ይዞ ከአንገት በላይ መገናኘት ለማንም አይበጅምና።
ሻሎም ! አሜን ።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን) fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 20/2015