ዘመናዊ ስፖርት መዘውተር ከጀመረ ከአንድ ክፍለ ዘመን በላይ በተቆጠረባት ኢትዮጵያ፤ የተደራጀና ወጥ የሆነ አሠራር የዘርፉ መሠረታዊ ችግር በመሆን ቀጥሏል። የሕዝባዊና መንግሥታዊ አካላት ኃላፊነቶች መጣረስ ስፖርቱ እንዳያድግ ማነቆ ሆኖት ቆይቷል። በዓለም አቀፍ ውድድሮች የተገኙ ውጤቶችም በጠንካራ መሠረት ላይ የተንተራሱ ባለመሆናቸው ብቅ ጥልቅ በማለት ቀጥለዋል።
በ1990 ዓም በወጣው የኢትዮጵያ ስፖርት ፖሊሲ የትኩረት አቅጣጫ፤ ‹‹የስፖርት አጠቃላይ እንቅስቃሴ አደረጃጀትና አመራር ሕዝባዊ መሠረት እንዲኖረው ይደረጋል›› ይላል። ከዚሁ ጋር በተያያዘ የሃገሪቷን ስፖርት በበላይነት የመምራት ሥልጣን የሕዝባዊ አካሉ (ክለቦች፣ ፌዴሬሽኖች፣ ኦሊምፒክ ኮሚቴ እና የስፖርት ምክር ቤቶች) ሆኖ መንግሥታዊ አካሉ ሕዝባዊ አካሉን የመደገፍና የማገዝ ሚና እንደሚኖራቸው ይገልጻል። ነገር ግን በ2012 ዓም የተዘጋጀው ሀገራዊ የስፖርት ሪፎርም ጥናት መሠረታዊ ክፍተት መኖሩንና መንግሥታዊና ሕዝባዊ አካሉ አደረጃጀት በመፋለሱ ለያይቶ ለማስቀመጥ አዳጋች እንደሆነ ያስቀምጣል።
በፖሊሲው ላይ የተመላከተው ሃሳብ በሌሎች ሃገራት እየተተገበረ ያለው በቅደም ተከተሉ መሠረት በመሆኑ ስፖርቱ ብቻም ሳይሆን ስፖርቱን የሚመሩት አካላት ጭምር በአቅም የጎለበቱ ናቸው። የመንግሥት ሚና እንደ ኦሊምፒክ፣ የዓለም ዋንጫ፣ የመላ አፍሪካ ጨዋታዎችና የመሳሰሉት ትልልቅ ውድድሮች ሲካሄዱ፤ ሃገር የምትወከልበት እንደመሆኑ ብሔራዊ ቡድኑን መደገፍ ነው። ወደ ኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ ስንመለስ ግን ከፈረሱ ጋሪው ቀድሞ የሕዝባዊ አካሉን ሥራ መንግሥት ሲያከናውን በመቆየቱ የመዋቅር መደበላለቆች ታይተዋል።
መንግሥታዊው አካል (የኢፌዴሪ ባሕልና ስፖርት ሚኒስትር) ከ30 ለሚልቁ የስፖርት ፌዴሬሽኖችና አሶሴሽኖች፣ የጽሕፈት ቤት ኃላፊና ባለሙያዎችን ይቀጥራል፣ በጀት ይመድባል፣ የዓለም አቀፍ ስፖርት ማኅበራት የአባልነት ክፍያዎችን ይሸፍናል፣ ሥልጠናዎችን በአጋርነት ያዘጋጃል፣ ዓለም አቀፍ ውድድሮች ሲካሄዱም የገንዘብ የትጥቅ እና የቁሳቁስ ድጋፍ ያደርጋል። እንዲያም ሆኖ ግን ፌዴሬሽኖች ራሳቸውን ከመቻል ይልቅ በጎደለው እያማረሩና የመንግሥትን እጅ እየተጠባበቁ ዘመናትን አሳልፈዋል።
እንደሚታወቀው ስፖርት በባሕሪው እጅግ ከፍተኛ ገንዘብ የሚጠይቅ ዘርፍ ነው፤ በመሆኑም የራስን የገቢ ምንጭ ማፈላለግ የግድ ነው። ምክንያቱም እጅ ሲያጥራቸው ከታዳጊ ፕሮጀክት እስከ ብሔራዊ ቡድን የሚኖረውን ሥልጠና ማሳለጥ፣ የባለሙያዎች አቅም ግንባታ ሥልጠናዎችን ማዘጋጀት፣ በየደረጃው ውድድሮችን ማካሄድ፣ በአህጉር እና ዓለም አቀፍ ውድድሮች ላይ ሃገርን መወከል፣… አይቻልም። በዚህም የሚጎዳው ስፖርቱ ብቻ ሳይሆን ስፖርት እንደ አንድ የሥራ ዘርፍ እንዲሁም የመልካም ገጽታ መገንቢያነቱ ሃገርም ጭምር ነው።
በአንጻሩ ጊዜውን፣ ገንዘቡን፣ እውቀቱን እና ልምዱን ፈሰስ በማድረግ ስፖርቱን ይጠቅማል በሚል የተወከለው የሥራ አስፈጻሚ (ሕዝባዊው አካል) ተሳትፎውን የሚያረጋግጠው ጠቅላላ ጉባኤ ሲካሄድና ዓለም አቀፍ ጉዞዎች ሲኖሩ ነው። ሃገር አቀፍ የስፖርት ማኅበራት ስለሚቋቋሙበት ሁኔታ ለመወሰን ተሻሽሎ የወጣ መመሪያ፤ ሥራ አስፈጻሚ ማለት አንድን ሃገር አቀፍ የስፖርት ማኅበር የሥራ እንቅስቃሴ በበላይነት ለማስፈጸም በማኅበሩ ጠቅላላ ጉባኤ የተመረጠ አካል መሆኑን ይጠቁማል። ይህም ማለት ለሃገርና ለሕዝብ ጥቅም ቅድሚያ የሚሰጥ፤ ስፖርቱን በሃብቱ፣ በእውቀቱና በሙያው መደገፍ የሚችል ግለሰብ ነው። ማኅበሩ የውስጥ ገቢ የሚያሳድግበትን የተለያዩ ሥራዎች መሥራት እንዳለበትም በመመሪያው በግልጽ ተመላክቷል።
ያም ሆኖ አብዛኛዎቹ የሥራ አስፈጻሚዎች እንደ መስቀል ወፍ አልፎ አልፎ ብቅ ከማለት ባለፈ በግል ሥራቸው ላይ የተጠመዱ ናቸው። በመመሪያው የቀድሞ ስፖርተኛ፣ ሙያተኛ አሊያም ለስፖርቱ ጥልቅ ፍቅር ያለው እንዲሆኑ ቢያመላክትም በበርካቶች የሚነሳው ሃሳብ ግን ከዚህ በተቃራኒ ስለ ስፖርቱ እውቀት የሌላቸው መሆኑን ነው። ይህ ከሆነ ስፖርቱን ለመምራት ለምን አስፈለገ የሚለው ጥያቄ ሲነሳ የሚቀመጠው መላ ምት ስፖርቱን እንደ መረማመጃ በመጠቀም የራሳቸውን ጥቅም ማሳደድ ነው። ለዚህ ማሳያ የሚሆነውም የስፖርት ማኅበራቱ ችግር ውስጥ በሚሆኑበት ወቅት ወይም አስፈላጊ በሆነ ጊዜ ድርሻ ሳይኖራቸው፤ በመንግሥት በኩል አንዳንድ እንቅስቃሴዎች ሲደረጉ ቅሬታ ለማሰማትና ለዓለም አቀፍ የስፖርት ማኅበራት ሃገርን ለመክሰስ መሯሯጣቸው ነው። እርስ በእርሳቸው በሚያደርጉት የጥቅም ሽኩቻ ሕዝብ ድረስ የደረሰ፤ መንግሥትም ለመገላገል እጁን ያስገባበት ተደጋጋሚ እሰጣገባም ማስረጃ ነው።
በእርግጥ በባለቤትነት ስሜት ሙሉ ጊዜና ጉልበታቸውን ሰጥተው ስፖርቱን ለማሳደግ የሚለፉ፤ በዚህም ከሃገር አልፎ በአህጉርና ዓለም አቀፍ የስፖርት ተቋማት ሥራ አስፈጻሚ(ቦርድ) ውስጥ የመካተት እድል ያገኙ መልካም ባለሙያዎች ስለመኖራቸው አይካድም። የሚልቁት ግን በሚጠበቁት ልክ ያልተገኙ ስለመሆናቸው አሁንም ድረስ ጉዟቸው የእንፉቅቅ መሆኑ ያሳብቃል። መንግሥትም ፖሊሲውን ከማስተግበር ይልቅ ለዘመናት እነዚህን አካላትና አሠራሩን እሹሩሩ ሲል መቆየቱ ማኅበራቱ ራሳቸውን እንዳይችሉ በማድረግ ረገድ ሚና ነበረው።
አሁን ይህ አሠራር ተቀይሯል፤ ሚኒስትሩ ተግባራዊ ያደረገውን መዋቅር ተከትሎ አብዛኛዎቹ የስፖርት ማኅበራት ድንገት ከጎጆው እንደወደቀ ጫጩት ግራ መጋባት ውስጥ ገብተዋል። በፖሊሲው የትኩረት አቅጣጫ መሠረት ማኅበራቱ ራሳቸውን ችለው ከመንግሥት እገዛ እንዲላቀቁ፣ ባለሙያዎችን እንዲቀጥሩና የራሳቸውን ቢሮ እንዲያደራጁ እየተደረገ ነው። አስቀድሞ ራሳቸውን የቻሉ 6 ማኅበራት (እግር ኳስ፣ አትሌቲክስ፣ ኦሊምፒክ ኮሚቴ፣ ሞተር ስፖርት፣ ወርልድ ቴኳንዶ እና ፈረስ ስፖርት) ብቻ ነበሩ። መዋቅሩን ተከትሎም ከፊሉ ተቀላቅለዋቸዋል፤ የተቀሩት ደግሞ በአንድ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ስር በጀታቸው 50 ከመቶ ቀንሶባቸው ራሳቸውን ለመቻል ጥረት እንዲያደርጉ ጊዜ ተሰጥቷቸዋል።
ይህ ሁኔታ የከበዳቸው ፌዴሬሽኖች አሁንም ቅሬታዎችን በማንሳት ላይ ይገኛሉ። ቀድሞ የነበረው የውድድር ተሳትፏቸውም ይበልጥ እየቀነሰ መጥቷል። ጫጩት እንደመሰሎቿ መብረር እንድትችል ከጎጆዋ በቅድሚያ የምትገፋት እናቷ ስትሆን፤ ይህም የጭካኔ ሳይሆን ራሷን እንድትችል ለማድረግ መሆኑ ግልጽ ነው። መንግሥትም ፖሊሲውን እውን ለማድረግ ይህንኑ መንገድ መርጧል፤ ስለሆነም ማኅበራቱ መፍጨርጨር ያለባቸው ራሳቸውን ለመቻል እንጂ ለክስና ለቅሬታ መሆን የለበትም። ማኅበራቱን መምራት የሚገባቸው የሕዝባዊ አካላት ተወካዮችም አሁን ትክክለኛ ሚናቸው የሚወጡበት ጊዜ የመጣ ይመስላል።
በመሆኑም ሕዝብ የመረጣችሁ፣ ስፖርቱን ታሳድጋላችሁ የሚል ተስፋ የተጣለባችሁና አቅም ያላችሁ የሥራ አስፈጻሚዎች ብቃታችሁ የሚለካው አሁን ነው። ስፖርቱን እንዴት ልጥቀመው የሚለውን ሃሳብ ያዙ፤ እንዴት ልጠቀም የሚል ራስ ወዳድነትን አርቀው መጣል አለባቸው። በሠሩት መልካም ተግባር ሃገርን በበጎ ከማስጠራት ባለፈ የሚኮሩበት ሃሳብና ተግባር ይዘው ስፖርቱን ለመምራት መዘጋጀት አለባቸው።
ይህ አምድ በተለያዩ ፖለቲካዊ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ዜጎች ነፃ ሀሳባቸውን የሚሰጡበት ነው።በዓምዱ ላይ የሚወጡ ጽሁፎች የዝግጅት ክፍሉን አቋም አያመለክቱም።
ብርሃን ፈይሳ
አዲስ ዘመን ሚያዚያ 19/2015