የጨረታ Clichy ግን ደግሞ ዛሬም በየአጋጣሚው ጥቅም ላይ እየዋለ ያለ የነጮች ባለ 24 ካራት ወርቅ ይትበሀል አለ። “ጎደኞችህን መርጠህ መጎዳኘት ትችላለህ። ጎረቤትህን ግን መርጠህ ጎረቤት ማድረግ አትችልም።”/ “You can choose your friends, but you can’t choose your family.”/ አዎ አገራችን ከሱዳን፣ ከኤርትራ፣ ከደቡብ ሱዳን፣ ከጅቡቲ፣ ከኬንያና ከሶማሊያ ጋር ጎረቤት የሆነችው መርጣና ፈቅዳ አይደለም። የዛሬ መጣጥፍ ትኩረት በሱዳን ሰሞነኛ አኳኋን ላይ ስለሆነ እዛው ላይ እናተኩራለን።
በሱዳን የተከሰተው ቀውስ በአንድም በሌላ መልኩ ለአገራችን መትረፉ ስለማይቀር ጉዳዩን በቅርበት ሌት ተቀን መከታተል፤ የሁለቱን ወንድማማች ሕዝቦች ዘላቂ ጥቅሞች ከግምት ያስገባ፤ የአገሪቱን ብሔራዊ ጥቅም ታሳቢ ያደረገ፤ የታሪካዊ ጠላቶቻችንን አሰላለፍ በቅጡ የተረዳ፤ ብስለት የተሞላበት፣ በእውቀትና በጥበብ የሚመራ፣ ድንገት በእጅ የገባን አጋጣሚ አሟጦ የሚጠቀምና አሳልፎ የማይሰጥ ዘርፈ ብዙ የሆነ አመራር ይጠይቃል። አጋጣሚን መጠቀም ያለና የሚኖር የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ መርህ ነው። ይሄን መርህ እንደ ቻይና አሟጦ የተጠቀመበት አገር የለም። ያው አገርን ይሉኝታ አይዛትምና ይሉኝታ እንዳናሲዛት ለማለት ነው።
በሱዳን ጦርና በፈጥኖ ደራሽ ልዩ ኃይል መካከል ባለፈው ቅዳሜ በካርቱም በተቀሰቀሰ ግጭትና ቢያንስ በብዙ መቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ሲገደሉ ከ2000 በላይ ሰዎች ደግሞ መቁሰላቸውን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሱዳን ልዩ ተወካይ አስታውቋል።ሁኔታ እጅግ በጣም አሳሳቢ ነው የኃይል ሚዛኑ ወደ የት እንደሚቀየር ለመናገር በጣም አስቸጋሪ ነው ሲሉ ልዩ ተወካይ ቮልከር ፔርቴስ ተናግረዋል።የሱዳን ፈጥኖ ደራሽ ኃይል ካርቱምን ጨምሮ የአገሪቱን አየር ማረፊያና የግብፅ ጦር የሰፈረበትን ወታደራዊ ቦታዎች መቆጣጠሩን አስታውቋል።
ሁኔታዎች በፍጥነት እየተለዋወጡ ስለሆነ ያን ተቆጣጠረ ይሄን ለቀቀ ብዙ ውሃ የሚያነሳ መረጃ አይደለም። ገዥው ጥያቄ በሱዳን ሰላም፣ ሉዓላዊ የግዛት አንድነትና ህልውና ላይ የደቀነው አደጋ የሚቀለበሰው በጠረጴዛ ዙሪያ ውይይት ወይስ በኃይል የሚለው ነው። በጎረቤት አገር ኢትዮጵያ፣ በቀጣናውና በአኅጉሩ ጂኦ-ፖለቲካና ኢኮኖሚ የሚፈጥረው ተጽዕኖ እንዲሁም የግብጽ ሚና እና በሱዳን ቀውስ የአለማቀፉ የተጻጻሪ ኃይላት አሰላለፍ ማለትም ቻይናና ራሽያ በአንድ ወገን አሜሪካ መሩ ምዕራባውያን በሌላ በኩል እንዴት ይሆን የሚሉ ጥያቄዎች ናቸው ትኩረት ሊሰጣቸው የሚገባ።
የአገራችን ትኩረት በበሽታዋ ላይ እንጂ በምልክቱ ሊሆን አይገባም። በውጊያው ግብጽ በቀጥታ ጣልቃ መግባቷ በግልጽ እየተነገረ ነው። ለምን !? ለምንስ ከአል-ቡርሀን ጎን ሆነች !? እነዚህ ጥያቄዎች ከተለያየ ጂኦ-ፖለቲካና ከሕዳሴውና ከቀጣናው አንጻር መተንተንና መብጠርጠር አለባቸው።
በአፍሪካ ጉዳዮች ላይ ጥናት እና ምርምር የሚያደርገው አማኒ አፍሪካ የተሰኘው ተቋም መስራች ዶ/ር ሰለሞን አየለ ደርሶ የሚጠቅሷቸው አንድ የቀጣናው ተመራማሪ ከአራት ዓመት በፊት እንደ ነብይ ሱዳንን፣ ጎረቤቶቻቸውንና ቀጣናውን የሚያሰጋው ሕዝባዊ ተቃውሞው ሳይሆን”በጦሩ ውስጥ የሚፈጠር የእርስ በእርስ ሽኩቻ ነው።”ብለው ነበር። ይሄው ያሉት ደርሷል። ዛሬም ሆነ ባለፉት ጥቂት ዓመታት በሱዳን ፖለቲካ የምንመለከተው ቀውስ ምንጩ ይህ የስልጣን ሽኩቻ ነው። የሁለቱም አጀንዳ የአብዛኛው ሱዳናዊ አጀንዳ አይደለም። ዜጋው ነጻነት፣ ዴሞክራሲ፣ የስራ ዕድል፣ የኑሮ ውድነቱ መረጋጋት፣ ወዘተረፈ እንጂ ጦሩ ስልጣን ላይ እንዲቀመጥ እንደማይፈልግ ባለፉት አራት ዓመታት በነቂስ ወደ አደባባይ በመውጣት ድምጹ አሰምቷል።
በሱዳን ወታደራዊ መሪዎች ከስልጣናቸው በተወገዱበት በጎርጎሮሳዊው አቆጣጠር 1964 እና 1985 ህዝባዊ አመጾች ወቅት “በአገሪቱ ወሳኝ ኃይል የነበረው ጦር ሰራዊቱ እንደነበር የሚያስታውሱት ተመራማሪው ዛሬም እየተስተዋለ ያለው ይሄ ነው ይላሉ። ሱዳንም ሆነ ግብጽ ከዚህ ቀለበት ሰብረው መውጣት አልቻሉም። ቀደም ሲል በዳርፉር ተሰማርቶ የነበረው ጃንጃዊድ የሚባለው የሚሊሺያ ኃይል አሁን “ፈጥኖ ደራሽ የድጋፍ ኃይል” በሚል እንደሚንቀሳቀስ ያስረዳሉ።
ከእነዚህ ኃይሎች ጎን “የማዕከላዊ ተጠባባቂ ፖሊስ” የሚባል ኃይል እና የሱዳን ገዢ ፓርቲ “እስላማዊ ታጣቂ ቡድን” እንዳለም ያብራራሉ። እነዚህ ኃይሎች በሳዑዲ አረቢያ፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች እና ኳታር እንደሚደገፉ የሚገልጹት የፖለቲካ ተንታኙ ሁሉንም እንደ የጸባያቸው አቻችለው መምራት የቻሉት ፕሬዚዳንት አልበሽር ብቻ እንደነበሩ ያሰምሩበታል። ዶ/ር ሰለሞንም በዚህ ትንታኔ ይስማማሉ።
በአልበሽር የመጨረሻ የስልጣን ቀናት በደህንነት ኃይሎች እና በጦር ሰራዊቱ መካከል፤ በተቃዋሚ ሰልፈኞች ላይ እርምጃ በመውሰድ እና አለመውሰድ ላይ አለመግባባት ተፈጥሮ እስከመታኮስ መዳረሳቸው የተነገረ ቢሆንም፤ ከዚያ በኋላ የጎላ ችግር ባለመከሰቱ ስጋቱ የቀነሰ መስሎ ነበር። ስልጣኑን የተረከበው ወታደራዊ ምክር ቤት ከገዢው ፓርቲ ጋር ግንኙነት ያላቸውን እስላማዊ ሚሊሺያዎች “ተቆጣጥሯል” መባሉም ስጋቱን ትንሽ አርግቦት ነበር። በተለያዩት የጸጥታ ኃይሎች መካከል ለጊዜውም ቢሆን ስምምነት ያለ ቢመስልም በጦር ሰራዊቱ ውስጥ ያለው ልዩነት ግን ጊዜው ጠብቆ ፈንድቷል።
ከአልበሽር ስልጣን መነሳት በኋላ በመሪነት ብቅ ያሉት የሱዳኑ መከላከያ ሚኒስትር ስልጣናቸውን ከአንድ ቀን በኋላ ሳይጠበቅ ያስረከቡ ዕለት መጪው ጊዜ ለሱዳን ክፉ ንግር ነበር። መከላከያ ሚኒስትሩን ሌፍተናት ጄነራል አዋድ ሞሃመድ ኢብን አውፍን የተኳቸው በተመሳሳይ ወታደራዊ የማዕረግ ደረጃ ያሉት አብደልፈታህ አልቡህራን ናቸው። ሹም ሽሩ ቀጥሎ የብሔራዊ የደህንነት እና የጸጥታ አገልግሎት ኃላፊው ሳላህ አብደላ ጎሽ ስልጣናቸውን ለቅቀዋል። እነዚህ መጠላለፎች የውስጣዊ ችግሩ ብስናት ነበሩ።
የሱዳንን መጻኢ ሁኔታ አቅጣጫ ለማስያዝ ዛሬን ጨምሮ ቀጣዩቹ ቀናት ወሳኝ መሆናቸውን የፖለቲካ ተንታኞች ያሳስባሉ። በአገሪቱ ያለው ፖለቲካዊ ውጥንቅጥ በፍጥነት በሚለዋወጥበት በዚህ ወቅት ከሱዳን ጋር ወደ 1600 ኪሎ ሜትር ገደማ ድንበር የምትዋሰነው ኢትዮጵያ ጉዳዩን የያዘችበትን መንገድ መጠየቅ የአባት ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ሰሞኑን የሱዳንን ወቅታዊ ሁኔታ አስመልክተው ባስተላለፉት መልዕክት ሁለቱ አገራት ልዩነታቸውን በውይይት እንዲፈቱ፤ የውጭ ኃይሎችም በአገሪቱ የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ ከመግባት እንዲቆጠቡ አሳስበዋል።
ኢትዮጵያ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቷ በኩል ባለፈው ሐሙስ ምሽት ካወጣችው አጭር መግለጫ ውጭ በጉዳዩ ላይ ዝርዝር ማብራራያ አልሰጠችም። ኢትዮጵያ “በሱዳን እየተካሄደ ያለውን ወቅታዊ ሁኔታ በቅርበት እየተከታተለች” መሆኑን የጠቀሰው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መግለጫ “ሱዳናውያን አሁን ያሉበትን አስቸጋሪ ሁኔታ በብቃት እንደሚወጡት ኢትዮጵያኑ ጽኑ እምነት አላት” ብሏል። አገሪቱ “የሱዳናውያን ፍላጎት ሙሉ በሙሉ የምታከብር” መሆኗንም ጠቁሟል ይለናል የዶቸ ቬለ ዘገባ ።
በቅርብ ጊዜያት በኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ ታሪክ ላይና በተለይ በቀጣናው ጉዳይ ተከታታይ ቃለ ምልልሶችን ለሸገር ኤፍ ኤም ሬዲዮ በመስጠት የሚታወቁት ዶ/ር በለጠ በላቸው በበኩላቸው፤ ስለኢትዮጵያና ሱዳን ግንኙነት ሲጠየቁ፣ ‹‹ግንኙነቱ በሦስት መዋቅሮች ይወሰናል፤›› ይላሉ።አንደኛው የሱዳን የፖለቲካ ኃይሎች የኃይል አሠላለፍ ሲሆን ፤ የውጭ ኃይሎች ጫናና የውጭ ግንኙነታቸው አቅጣጫ በሱዳንና ኢትዮጵያ መካከል የቆየውን የግንኙነት ሁኔታ ሲወስን መቆየቱን ያስረዳሉ፡፡
ሱዳን ለበርካታ ጊዜያት መፈንቅለ መንግሥት ሲካሄድባት የዘለቀች፣ ለበርካታ ዓመታት የተረጋጋ መንግሥት ለመመሥረት ስትቸገር የኖረችና የተለያየ የፖለቲካ አሠላለፍ የሚታይባት አገር ናት ይላሉ። ሱዳን ከዚህ በተጨማሪም በራሷ ብቻ መቆም የማትችልና የውጭ ጫና የሚበዛባት አገር ናት።አገሪቱ ከመካከለኛው ምሥራቅ ብዙ ጫና ለማስተናገድ የምትገደድበት ዓረባዊ ማንነት ያላት ናት።የዓረቡ ዓለምና አፍሪካን የምታስተሳስር ናት በሚል ጫናው ከፍተኛ መሆኑንም ዶ/ር በለጠ ያብራራሉ፡፡
በሱዳን ፖለቲካ ውስጥም ቢሆን ብዙ ዓይነት አቋምና የፖለቲካ አሠላለፍ መኖሩን የውጭ ግንኙነት ምሁሩ ያስረዳሉ።የኃይማኖት ርዕዮተ ዓለም በሱዳን ፖለቲካ ውስጥ ከፍተኛ ተፅዕኖ እንዳለው የሚጠቅሱት ምሁሩ፣ ይህም ሁለት ትልልቅ ጎራዎች መፍጠሩን ይገልጻሉ።አንዱ ጎራ የካትሚያ እስላማዊ የፖለቲካ ሠልፍ ሲሆን፣ በዚህ በኩል እንደ አሺካና ናሽናል ዩኒየኒስት ያሉ ፓርቲዎች ተሰልፈዋል። የዚህ ርዕዮተ ዓለም ጎራ ፖለቲከኞች (ሠልፈኞች) ኢትዮጵያ ጠልና አፍቃሪ ግብፅ ፖለቲካን ማራመድ ባህላቸው መሆኑን ይናገራሉ፡፡
ከእነዚህ በተቃራኒው የቆሙት ደግሞ የመሀዲያ (መሀዲስት) ርዕዮተ ዓለም ፖለቲከኞች ናቸው ይላሉ።በዚህ ወገን በተለይ የኡማ ፓርቲ ዋነኛው ሠልፈኛ መሆኑን የሚያስረዱት ዶ/ር በለጠ፣ በዚህ በኩል በአመዛኙ ከኢትዮጵያ ጋር ግንኙነትና ጉርብትናን የተሻለ የማድረግ አቅጣጫን የመከተል የፖለቲካ ባህል መኖሩን ያስረዳሉ።የውጭ ግንኙነት ታሪክ አጥኚው እንደሚሉት በሱዳን ሥልጣን ላይ የሚመጡ የፖለቲካ ኃይሎች (ወታደራዊም ሆነ ሲቪል አስተዳደር)፣ በሁለቱ የሃይማኖት ርዕዮተ ዓለሞች ሠልፍ ዥዋዥዌ የመጫወት ልምድ ያላቸው ናቸው።ይህ የጎራ ልዩነት (ሠልፍ) ደግሞ ከኢትዮጵያ ጋር የሚኖራቸውን ግንኙነት ሲጫነው ይታያል፡፡
እንደ መረጃዎቹ”..በአልፋሽቃ መሬቶች የነበሩ (አልቡርሃን-መራሽ) የሱዳን ወታደሮች ከቦታው ለቅቀው እየወጡ ናቸው..” በማለት የተሰራጩ ሲሆን፤ የመረጃው አቅጣጫም ሆነ አመጣጡ ግን ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚፈልግ መሆኑ ነው የሚያመዝነው..። የአሁኑ የሱዳን ውጊያ ትያትር በዋነኛነት የሃያላን ድርሰት ሲሆን ሁለቱ የጦር መሪዎች በሀያላኑ ስክሪፕት መሰረት የመተወን ሚና ላይ ናቸው ይለናል የዐባይና የቀጣናው አክቲቪስት ሱሌማን አብደላ። ሁለት የኢትዮጵያ ስጋቶች የሚያደርጉት የፍልሚያ ክረት የልቀት resolution ደረጃውን ሲያገኝ ማንን አሸናፊ እንደሚያደርግ ከኢትዮጵያ በኩል ለተመለከተው ለመረዳት ከባድ አይሆንም።
ሁለቱም ተፋላሚዎች የጦር አቅም እንጂ ህጋዊ እውቅናም ሆነ ሕዝባዊ ይሁንታ የሌላቸው ጊዜያዊ ባለስልጣናት እንደመሆናቸው ግጭቱ የቡድን ጥሎ ማለፍ ሽኩቻ የወለደው ነው። ከነሱ አመክንዮ በላይ አንገብጋቢ ጉዳይ ያለባት ካይሮ በበኩሏ አንደኛውን ደግፋ የጦር ጀቶቿን በውጊያው ላይ አሰማርታለች። ግብጽም ኢትዮጵያን ጎትታ በግጭቱ ማሳተፍ ትሻለች።
የሚጠብቃትን ዘርፈ ብዙ ቀውስ በኢትዮጵያ ላይ ማውረድን ትመርጣለች ይለናል ሱሌማን አብደላ። ሰን ዙ የተባለው የቻይና ጄነራልና ስትራቴጂስት”ሁለት ወገኖች ግጭትን ሲመርጡ ከመካከላቸው ቢያንስ አንዱ ተሳስቷል። ምናልባትም ሁለቱም ተሳስተው ይሆናል። “አሸናፊ” የሚሆነውም ቢሆን የተሳሳተ ሊሆን ይችላል። ምክንያቱም እያንዳንዱ ግጭት ሁሉንም ስለሚያዳክማቸው ይለናል።
The art of war ላይ “..ድል አድራጊዎች ቀድመው አሸንፈው ወደ ጦርነት ይሄዳሉ፣ ተሸናፊ ተዋጊዎች ግን በመጀመሪያ ወደ ጦርነት ይገቡና ከዚያ በኋላ ነው ለማሸነፍ የሚፍጨረጨሩት..።” የሚለውን እናገኛለን። ኢትዮጵያ ደግሞ ይህን ተጨባጭ አጋጣሚ የምትጠቀምበት አውድ ተፈጥሮላታል። ግብፅን ጨምሮ ሁለቱም የሱዳን ተፋላሚዎች በኢትዮጵያ ጥቅም በኩል ትልቅ ነጥብ የሚጥሉበት ጊዜ ላይ ናቸው።
ለአልፋሽቃ ሉአላዊ እልባት ማግኘት ጉዳይ የኢትዮጵያ የቤት ስራ ሲሆን ከመቸውም ጊዜ በላይ የተመቻቸ አጋጣሚ የተፈጠረበት ወቅት ላይ ነን ማለት ይቻላል። ይሁን እንጂ ካይሮ ወደ መዳፋቻን የተጠጋውን የአልፋሻቃ ካርድ የምታመላክተን ከሆነ ጉዳዩ የሱዳኑን ጦርነት ሰፊ ምስል እንዲደበዝዝብንና ቁልፉ ጉዳይ ላይ ከማተኮር እንዳያደናቅፈን ትልቅ ጥንቃቄ ያስፈልገናል የዐባይና የቀጣናው ተሟጋች ወጣት ሱሌማን ያስጠነቅቃል።
አራተኛው ሙሌት ምናልባትም የመጨረሻው የግድቡ ምዕራፍ ሊሆን ይችላልና ጭንቀት ውስጥ የገባችው ካይሮ በሱዳኑ ጦርነት አልቡርሃን በየትኛውም መንገድ ድል ቢቀናው ቢያንስ የተስፋ ስንቅ ይሆናታል። የጀነራሉ ሽንፈት ግን የሞት ሞቷ ይሆናልና ይህን ከመመልከት ሱዳን እንደ ሶሪያና የመን የውክልና ጦርነት አውድማ ብትሆን ትመርጣለችየዚህ ወላፈን ዋነኛ ኢላማዋ ኢትዮጵያ ናትና ወደጫረችው እሳት እንዳታስገባን እያንዳንዷን የካይሮ ቀመር በጥንቃቄ መከታተል ጠቃሚ ጉዳይ ይሆናል። ለዚህ ይረዳን ዘንድ የአገራችንን የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ በወፍ በረር እንቃኝ።
ኢትዮጵያ በአካባቢው ያላት ተሳትፎና የውጭ ፖሊሲዋ እ.ኤ.አ በ2002 ሥራ ላይ ባዋለችው የውጭ ጉዳይና የብሔራዊ ደኅንነት ፖሊሲና ስትራተጂ ላይ የተመሠረተ ነው።በቅርቡ ያጋጠሟት ውስጣዊ ግጭቶች ቢኖሩም አገሪቱ በአፍሪካ ቀንድ ውስጥ ቁልፍ ተፅዕኖ ፈጣሪ ናት፣ በክፍለ አኅጉሩ ውስጥ መረጋጋት በመፍጠር በኩልም ወሳኝ ሚና አላት።የኢትዮጵያ መንግሥት በወሳኝ መልኩ ኢጋድና የአፍሪካ ኅብረት በመሳሰሉት ባለብዙ ዘርፍ ኤጀንሲዎች አማካይነት በክፍለ አኅጉሩና በአኅጉሩ ውስጥ ትልቅ ተሳትፎ ያደርጋል።
በምሥራቅ አፍሪካና በአፍሪካ ቀንድም እንደ አንድ የሚታመን አደራዳሪ ይታያል።ይህ ሚናውም ባለው ተነጻጻሪ ወታደራዊ አቅምና በአካባቢው የሰላም ደኅንነት ዕርምጃዎችና እንቅስቃሴዎች ውስጥ በሚያደርገው ቋሚ ተሳትፎ፣ ሽብርን በመቋቋም ረገድ ያለው አቅምና ተነሳሽነት፣ የአፍሪካዊነት ውርሱና ባለብዙ ዘርፍ መድረኮችን አሟጦ የመጠቀም አቅሙ የመሳሰሉት ባህርያት እንዲዳብሩ አድርጓል።
የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ በወሳኝ መልኩ የሚመሠረተውም ለውስጣዊ ሥጋቶች በሚሰጥ ግብረ መልስ ላይ ነው።ሽብርና የጎረቤት አገሮች ያላቸው የተስፋፊነት ፖሊሲዎች፣ ከኤርትራ ጋር ያለው ግንኙነት፣ በዓባይ ዙርያ ከግብፅ ጋር ያለው የተጠቃሚነት ክርክር የመሳሰሉት ኢትዮጵያ ባላት የሰላምና የማኅበራዊ ዕድገት ጉዞ ላይ የሚያጠሉ የውጭና የውስጥ ሥጋቶች ናቸው።
የውጭ ጉዳይና የብሔራዊ ደኅንነትና ስትራቴጂ ፖሊሲው መሠረታዊ መርሆች ከሁለት አሥርታት በኋላም ቢሆን አግባብነታቸው እየታየ ቢሆንም ኢትዮጵያ ለውስጣዊ ተጋላጭነት ልዩ ትኩረት ከሚሰጠውና ከሚፈለገው በላይ ወደ ውስጣዊ ጉዳዮች ከሚያየው የውጭ ፖሊሲ ይልቅ ሚዛኑ በጠበቀ መልኩ የውጭ ሥጋቶችን ቀድማ ወደምታመክንበትና ሕጋዊ ተጠቃሚነቷንም ወደምታስከብርበት ፖሊሲ መሸጋገር ይጠበቅባታል ሲሉ ዶ/ር መሐሪ ታደለ ማሩ ይመክራሉ፡፡
ሻሎም !
አሜን።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 12/2015