ከአገራችን ወቅታዊ ጉዳዮች አንዱ የክልል ልዩ ኃይሎችን መልሶ የማደራጀት ስራ ይጠቀሳል።መንግስት በጥናት ላይ በተመሰረተ የለውጥ ንቅናቄ አገርን ተራማጅ በሆነ እሳቤ ለማሻገር ከወሰናቸው ውሳኔዎች አንዱ የክልል ልዩ ኃይሎችን መልሶ የማደራጀት እና ለላቀ አገራዊ ተልዕኮ ዝግጁ ማድረግ አንዱ ነው።የአገርና ህዝብን ጥቅም መሰረት በማድረግ የተካሄደው የዚህ መልሶ የማደራጀት ሥራ ጥናት ተጨባጭ እምርታ እንዲያሳይ በየደረጃው ውይይት ተደርጎበት የክልል ልዩ ኃይሎችን ወደ ሌሎች የጸጥታ መዋቅር እንዲታቀፉ የማ ድረጉ ሥራ ተጀምሯል፡፡
በዚህም ሁሉም ክልል የሚገኙ የክልል ልዩ ኃይሎች ክብርና ጥቅማቸው ተጠብቆ፤ እንዲሁም በራሳቸው ፍላጎት ላይ ተመስርቶ በመከላከያ ሰራዊት፣ በፌደራል ፖሊሲ ወይም በክልል ፖሊስነት እንዲቀላቀሉ እድሉ ተመቻችቶላቸዋል።ይሄንን አልፈልግም ወደ መደበኛ ኑሯችን መመለስ እንሻለን ለሚሉም የመቋቋሚያ ድጋፍ ተደርጎላቸው ፍላጎታቸው የሚጠበቅና የሲቪል ኑሮን የሚቀጥሉ ይሆናል፡፡
የዚህ መልሶ የማደራጀት ተግባር አላማው የአገር ሉዓላዊነት እና የህዝብን ሰላምና ደህንነት ማሥጠበቅ፤ እንዲሁም አገራዊ ልማቱን ቀጣይነት ማረጋገጥ መቻል ነው።ከዚህ የዘለለ ግን ምንም አይነት ትርጓሜ ሊሰጠው አይገባም፤ ከዚህ የተለየም ዓላማ የሌለው ነው።በመንግስት በኩል የተሰሙ ተደጋጋሚ መግለጫዎችና ማብራሪያዎችም ይሄን እውነት የሚያጠነክሩ ናቸው።በመሆኑም ልዩ ኃይልን መልሶ የማደራጀት ስራው አገርን መልሶ ከመስራት ጋር ሊታይ የሚገባው ሃቅ ነው፡፡
በዓለማችን ነባራዊ ሁኔታ ጠንካራ የመከላከያ አቅም ያላቸው አገራት ራሳቸውን አስከብረው ሲዘልቁ፤ የመከላከያ ኃይላቸው ደከም ያሉ አገራት ግን ከውስጥም ከውጪም ዘርፈ ብዙ ጫናና ጥቃት ሲደርስባቸው ይስተዋላል።ኢትዮጵያም ምንም እንኳን የመከላከያ አቅሟ ከራሷ አልፎ ለሌሎች ሰላም መስፈን የተረፈ ቢሆንም፤ ይሄንን ከፍታ የበለጠ የማጠናከር ስራ ሊከናወንለት ያስፈልጋል።ለዚህ ደግሞ ከውስጥ ሊሰሩ የሚገባቸውን የቤት ስራዎች መስራት ተገቢ ሲሆን፤ ልዩ ኢ-መደበኛ አደረጃጀቶችን በመደበኛው አደረጃጀት ውስጥ እንዲታቀፉ መደረጉም የዚህ አንዱ ማሳያ ነው።የዚህ እውን መሆንም ኢትዮጵያ እንደ አገር አንድነትና ሉአላዊነቷ እንዲጠበቅ ከማድረግ ጎን ለጎን የውጪ አገራት ትንኮሳዎችን የምንከላከልበት ጠንካራ አቅም የሚፈጥር ነው፡፡
ምክንያቱም ጠንካራ አገራዊ መከላከያ ኃይሉ የሁሉም ህዝብ አቅም ሆኖ ስራውን እንዲያከናውን፤ ክልሎችም ከዚህ ዝቅ ያለውን ኃላፊነት ወስደው በመደበኛ ፖሊስ የየአካባቢያቸውን ሰላምና ፀጥታ የማስጠበቅ የቤት ስራን እንዲወጡ የሚያደርግ ነው።ይሄን እውነት አስመልክቶ በተለያየ ጊዜ ከመንግስት በኩል ከተሰጡ መግለጫና ማብራሪያዎች መካከል፤ “ከአሁን በኋላ ክልሎች የፖሊስ ኃይላቸውን አጠናክረው ወንጀልን በመከላከልና አካባቢያዊ ጸጥታን በማስከበር ላይ ይተጋሉ።ከየትኛውም አካል የሚሰነዘር፣ የአገርን ድንበር ህልውናና ሉአላዊነት የሚዳፈር ኃይል ሲነሳ መከላከያ ሰራዊት እርምጃ ይወስዳል” ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ የልዩ ኃይልን አደረጃጀት ከአገር ክብር ጋር የተቆራኘ እንደሆነ የገለጹበት ተጠቃሽ ነው፡፡
ከዚህ ባለፈ የመከላከያ ሰራዊት ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ፣ እንዲሁም ምክትል ኢታማዦር ሹም ጀነራል አበባው ታደሰ የሰጧቸው ጥልቅ ማብራሪያዎች እንደሚያስረዱት፤ የክልል ልዩ ኃይሎችን መልሶ የማደራጀት ስራው አንዳንድ የጥፋት አጀንዳ አራማጆች እንደሚሉት ከትጥቅ መፍታትና ከሌላ አሉባልታ ጋር የተያያዘ ሳይሆን፤ የአገርን ህልውናና ሉአላዊነት፣ ክብርና ነጻነት ከማስጠበቅ ጋር የተገናኘ መሆኑን ነው፡፡
በመሆኑም የክልል ልዩ ኃይልን መልሶ የማደራጀት ስራ አንዳንዶች እንደሚሉት የበሬ ወለደ ወሬ ሳይሆን፤ አሁን ካለው ነባራዊ ሁኔታ የአገርን ሰላምና አንድነት፣ ጸጥታና የሰራዊቱን አቋም ከማነጽ ጋር የተያያዘ ተግባር ነው።በሂደቱም ሁሉም የክልል መንግስታት አምነውበት ይሁንታቸውን የሰጡበት፤ ለውጤታማነቱም እየተጉ ያለበት ነው፡፡
የክልል ልዩ ኃይሎችን በዚህ መልኩ መልሶ የማደራጀት ስራው ከዚህኛው ዓላማ ባለፈ፤ ሕገ መንግስትን የማስከበር ርምጃ ነው።ምክንያቱም የክልል ልዩ ኃይልን አደረጃጀት በተመለከተ በህገመንግስቱ የተቀመጠ አንዳችም ድንጋጌ የለም።ይሄ ማለት የክልል ልዩ ኃይል በህገመንግስቱ እውቅና ያልተሰጠው አደረጃጀት ነው ማለት ነው።ስለዚህ ይሄንን ኃይል ወደ መደበኛና ሕጋዊ መዋቅር ማምጣቱ ተገቢም፤ አስፈላጊም ነው፡፡
አሁን እየተሄደበት ያለው መልሶ የማደራጀት ስራ የክልል ልዩ ኃይሎችን ወደህጋዊነት የሚመራቸው አሰራር ነው።ነገሩን በቀና ልብ ማየት ከተቻለ ደግሞ አገራችንን የምናገለግለው በህግ ጥሰት ውስጥ ሆነን ሳይሆን፤ በህግ በተፈቀደ አደረጃጀት ውስጥ ሆነን እንደሆነ የሚያሳየን ርምጃ ነው፡፡
በሌላ በኩል ዛሬ ላይ በመንግስት እየተከናወነ ያለው ተግባር የሕዝብ ጥያቄን የመመለስ ርምጃ ነው።ምክንያቱም የክልል ልዩ ኃይል አደረጃጀት ለምን አስፈለገ? ሲል ለመንግስት ጥያቄ ሲያቀርብ እንደነበር ይታወቃል።በወቅቱ መንግስት ጥያቄውን ተቀብሎ በብዙ ጥናትና ጥልቅ ማሰብ በኋላ ጊዜውን በጠበቀ ሁኔታ ወደትግበራ ተመልሷል።አሁን ላይ የተጀመረው የአደረጃጀት ትግበራ አንድም የህዝብ ጥያቄ ነው፤ አንድም የህገመንግስትን ማስከበር ነው፤ በተመሳሳይ ጠንካራ የመከላከያ አቅምን የመገንባት ጉዞውን የሚያግዝ ነው፡፡
ህገመንግስቱ ለአንድ አገር የሚፈቅደው አንድ መከላከያ ሰራዊትን፤ የፌደራል ፖሊስን እና የክልል መደበኛ ፖሊስን ነው።ይሄ ደግሞ ለፌዴራል መንግስቱም ሆነ ለክልሎች እንደ ደረጃቸው ኃላፊነታቸውን ሊወጡ የሚችሉበትን አቅም ለክቶ የሚሰጥ ነው።ይሁን እንጂ ከዚህ ድንጋጌ ውጪ የተደራጀው የክልል ልዩ ኃይል፤ አገር ችግር ላይ በወደቀች ጊዜ የበኩሉን ሚና የተጫወተ ቢሆንም፤ አደረጃጀቱ ብሄር ተኮር እንደመሆኑ ዘርፈ ብዙ ችግሮች የታዩበትም ነበር።አገራችን በዘር ፖለቲካ፣ በእኔነት ቁርሾ እየተንገዳገደች ባለችበትና አንድነት በናፈቀን ሰሞን የክልል ልዩ ኃይሎች በብሄር ተቧድነው እኔ እበልጥ እኔ እበልጥ የመባባላቸው ጣጣ የታየውም ለዚሁ ነበር፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ ልዩ ኃይልን በተመለከተ በመግለጫቸው ‹የክልሎች ፉክክርና ትብብር በልዩ ኃይል ግንባታ ሳይሆን በኢኮኖሚ፣ በማህበራዊ ልማትና በዲሞክራሲያዊ ባህል ላይ ሊሆን ይገባል› ያሉትም ለዚሁ ነበር።በዚህና በመሳሰሉት ምክንያቶች ህጉን መሰረት ባደረገ መልኩ የመልሶ ማደራጀት ስራው እውን እንዲሆን የግድ ብሏል።ይህ ሲሆን ግን የአደረጃጀት ትግበራው በፍላጎትና በነጻነት ላይ የተመሰረተ፤ ከምንም አይነት ውስጣዊና ውጫዊ ጫና የጸዳ መሆኑን መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡
ይሄ ማለት ልዩ ኃይሎች እንደፍቃዳቸው ወደፈለጉበት በመግባት (በመከላከያ ሰራዊት አባልነት፣ በፌደራል ፖሊሲና በክልል መደበኛ ፖሊስነት) አገርን ማገልገል ይችላሉ ማለት ነው።ከዚህ ውጪ የሆነ ፍላጎት ያለው የክልል ልዩ ኃይል መብቱ ተጠብቆለት መቋቋሚያ ተሰጥቶት ከማህበረሰቡ ጋር የሚቀላቀልበት ሁኔታ ተመቻችቶለታል።ውሳኔውም አገር የማዳን፣ አገር የማሻገር፣ ህዝብና ትውልድን አንድ የማድረግ መዋቅራዊ ለውጥ ነው።ከዚህ በተጓዳኝ ለሉአላዊነት አፋጣኝ ምላሽ የሚሰጥ ጠንካራ እና ብቁ መከላከያ ሰራዊትን መገንባት ነው።
ለዚህ ደግሞ መከላከያ ሰራዊት በአደረጃጀት፣ በስነልቦና፣ በሰው ኃይል እና በቴክኖሎጂ የተገነባ እንዲሆን ያስፈልጋል።ለዚህ የመንግስትን አላማና እቅድ የሚያስፈጽምና የሚተገብር በአንድነቱ የቆመ ህዝብ ያስፈልጋል።ከውስጥም ከውጪም የሚቃጡ ትንኮሳዎችንም በብቃት መመከት የሚቻለው የአገር መከላከያ ሰራዊት እና የክልል ልዩ ኃይል በሚል የተከፋፈለ አቅም ሳይሆን፤ አንድ ጠንካራ የአገር መከላከያ ሰራዊትን እውን ማድረግ ሲቻል መሆኑን በመገንዘብ፤ ሁሉም አካል ለዚህ ዓላማ እውን መሆን የድርሻውን ሊወጣ ይገባል፡፡
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 12/2015