የመንደርደሪያ ወግ፤
የዓለማችን የጂኦ ፖለቲካ ተንታኞች የምሥራቅ አፍሪካንና “የቀንዱን” ቀጣና የሚገልጹት “ሕመሙ እየተፈራረቀ ፈውስ እንደራቀው ምስኪን በሽተኛ በመምሰል ነው ” ይህንን የምሁራኑን ሃሳብ በእኛው አገራዊ እውነታ እናጎላምሰው ካልን ዕድሜ የተጫናቸው አዛውንቶች “እንዴት አደራችሁ!” ተብለው የማለዳ ሰላምታ ሲቀርብላቸው “ምን አዳር አለና! ጎኔን እየወጋኝ፣ ደረቴን እየሸቀሸቀኝ፣ ዐይኔን እየጠዘጠዘኝ፣ ጆሮዬም ጭው እያለ እንደጮኸብኝ ንጋት ወለል አለ:: የእኔን መሰል የበሽታ ዓይነት እንኳን ለወዳጅ ለጠላትም አይስጥ” እንደሚሉት መሆኑ ነው::
የቀጣናው ትኩሳትና ሕመም መልኩ አንድ ዓይነት ብቻ ሳይሆን ዝንጉርጉር ባህርይ ያለው ስለሆነ የአባል አገራቱ አኗኗር እህህ የበዛበት ሊሆን ግድ ሆኗል:: የቀጣናው ቤትኛ፣ ለእኛ ደግሞ የቅርብ ታሪካዊና ጥንታዊ ጎረቤታችን ሱዳን በራሷ ልጆች መካከል በተፈጠረ ግጭት መታመስ ከጀመረች ቀናት ተቆጥረዋል:: ቅዳሜ ሚያዝያ 7 ቀን 2015 ዓ.ም የተተኮሰ የአንድ አረር ብልጭታ ወደ ከባድ መሣሪያዎችና የአየር ላይ ፍልሚያ ከፍ ብሎ የሱዳን ግዛት በራሷ ልጆች ከሰማይ እሳት እየዘነበባት ፋታ አጥታለች::
በሁለት ጄኔራሎች የሚመሯቸው ሠራዊቶች መካከል የተቀሰቀሰው ግጭት በጥበብና በማስተዋል ካልሰከነ በስተቀር ከሱዳንና ከቀጣናው ችግርነት አልፎ ሰበቡና ዘርፈ ብዙ መዘዙ ለመላው አፍሪካ እና ለተቀረው ዓለም እንዳይተርፍ ከፍተኛ ስጋት አሳድሯል:: አገራችንና ሱዳን ያለፉበትን የዘመናት የጉርብትና ፈተናዎች፣ ግጭቶችና የጦርነቶች ዜና መዋዕል እየተረኩ ለመጻፍ በርካታ ብራናዎችና የአንድ ሺ አንድ ሌሊት ትጋት ስለሚጠይቅ እጅግም ደፍሬ ወደ ውስጥ አልዘልቅም:: ይልቁኑ በራሴ ግላዊ ገጠመኝ ብንደረደር የተሻለ ስለሚሆን ትውስታዬን እንደሚከተለው አጋራለሁ::
ይህ ጸሐፊ የኢትዮጵያ ፐብሊክ ዲፕሎማሲ የልዑካን ቡድን አባል በመሆን ሱዳንን ለመጎብኘት ዕድል ያገኘው በሚያዝያ 2007 ዓ.ም ነበር:: የልዑካን ቡድኑ ዋነኛ ተልዕኮ በታላቁ የህዳሴ ግድባችን መገንባት ሱዳንና ሁሉም የናይል ተፋሰስ አገራት ቢጠቀሙ እንጂ ምንም ጉዳይ እንደማይደርስባቸው በኢትዮጵያ ሕዝብ ስም ማረጋገጫ ለመስጠት ታስቦ የተዘጋጀ ጉዞ ነበር:: ለልዑካን ቡድኑ በተያዘው ፕሮግራም መሰረትም ከላይኞቹ የአገሪቱ ቁንጮ መሪዎችና ተቋማት እስከ የኃይማኖት መሪዎችና ዜጎች በተወከሉባቸው አደረጃጀቶች በርካታ ውይይቶች ለማድረግ ተሞክሯል::
ጉብኝቱ የተከናወነው በዋና ከተማዋ በካርቱም ብቻ ሳይሆን ከመዲናዋ ከ320 ኪሎ ሜትር በላይ እስከሚርቀው የጥንታዊቷ የመረዌ ከተማና በዚያው አካባቢ እስከሚገኘው የአገሪቱ ትልቁ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ተቋም ድረስ የዘለቀ ነበር:: በጉብኝቱ ውስጥ የተካተቱት ዝርዝር ጉዳዮች በሌላ ጽሑፍ ቢቀርቡ አስተማሪዎች ሊሆኑ ስለሚችሉ ወደፊት እንመለስበታለን::
እንደ እውነቱ ከሆነ በዲፕሎማሲና በፖለቲካ ቅባቶች ከወዙት የልዑካን ቡድኑ የፕሮቶኮል ስብሰባዎች ይልቅ ይህንን ጸሐፊ ይማርኩት የነበሩት “በፖለቲካ አይዲዮሎጂ ካልተበረዙ”፣ ከገለልተኛ ምሁራን፣ ከኪነ ጥበባትና ከደራስያን ጋር የተደረጉት ግልጽ ውይይቶች ነበሩ:: ስለዚህም በአጭሩ አስታውሼ ለማለፍ የምሞክረው “ፕሮቶኮል ተጭኗቸው” ቃል እየተመረጡ ከተደረጉት ቁጥብ የልዑካን ቡድኑ ውይይቶች ይልቅ ይህንን አምደኛ ይበልጥ ይማርከው የነበረው “በሳቅና በፈገግታ” ፈታ በማለት የተደረጉት ጭውውቶችና የሃሳብ ልውውጦች ነበሩ::
ብዙዎቹ ያረጋገጡልንን እውነታ የሚወክልልንን አንድ ጉዳይ ብቻ ልጥቀስ:: ኢትዮጵያን በሚገባ የሚያውቋትና በአገራችን ፍቅር የወደቁ አንድ የዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰርና ደራሲ የሁለቱን ተጎራባች ሕዝቦች ታሪካዊና ወቅታዊ ሁኔታ የገለጹት እንዲህ በማለት ነበር፤ “የሱዳንና የኢትዮጵያ አክራሪ ፖለቲከኞች፣ ድብቅ ዓላማ አራማጆችና ለጋራ ፈተናችን ምክንያት የሆኑ የቅርብና የሩቅ ጠላቶቻችን የሴራ አጀንዳቸውንና እጃቸውን ቢሰበስቡና ዕድሉን ለሱዳንና ለኢትዮጵያ ሕዝቦች ቢተው ሁለቱ አገራት ተከባብረው የሚኖሩት በመልካም ጉርብትና ብቻ ሳይሆን እንደ አንድ አገርና ሕዝብ እየተያዩ በመደጋገፍ ጭምር ነበር ”
“ታሪካዊና ነባራዊ ሁኔታዎችን ልብ ብሎ የሚያስተውል ሰው የሚረዳው አንድ ቁምነገር ሁለቱ አገራት ሰላም እንዳያገኙ የእሳት መጫሪያውን ገልና የማቀጣጠያ ክብሪቱን የያዙት የተለየ አፍራሽ ፍላጎት ያላቸው ፖለቲከኞችና አመራሮች አንጂ ተራው ሕዝብ አይደለም:: የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነቱ በጊዜያዊ ተግዳሮቶች ቢፈተንም በፍጹም ሊቋረጥ የሚችል አይደለም::
ፍሬ ሃሳቡን የጠቀስኩት በማስታወሻዬ ላይ ካሰፈርኩት ድንቅ ምሁራዊ አገላለጾች ቆንጥሬ ነው:: ዛሬ በራሷ ጄኔራሎች የጦርነት እሳት የተለኮሰባትና እየተሰቃየች ያለችው እንዲህ ዓይነት እጅግ መልካምና በጎ ሃሳብ ያላቸው የሚሊዮኖች ሕዝቦች መኖሪያ የሆነችው ጎረቤት አገር ሱዳን ነች::
የግጭቱ መነሾ፤ ሱዳን በወታደራዊ ካውንስል አመራር ሥር የወደቀችው ኦክቶበር 2021 ዓ.ም ከተደረገው መፈንቅለ መንግሥት በኋላ ነበር:: የዛሬዎቹ ሁለቱ ተፋላሚ ጄኔራሎች የአገሪቱን ፕሬዚዳንት ኡመር አል በሽርን ከመንበረ ሥልጣናቸው ለማውረድ ተቀዳሚ ተዋንያን ነበሩ::
የመደበኛ ጦር ሠራዊቱ አዛዥ የሆኑትና የወታደራዊ ካውንስሉን አስተዳደር እየመሩ ያሉት ጄኔራል አብድል ፈታህ አል ቡርሃን አንደኛው ተፋላሚ ሲሆኑ፤ ሁለተኛው ተፋላሚ ጄኔራል ደግሞ የካውንስሉ ምክትልና የተወርዋሪ ፈጥኖ ደራሽ (Paramilitary Rapid Support Force, RSF) አዛዥ የሆኑትና ሄሜዲት በሚል ቅጽል የሚታወቁት ጄኔራል መሐመድ ሃምዳን ዳጋሎ ናቸው:: እነዚህ ሁለት ጄኔራሎች መንበረ ሥልጣኑን ከተቆጣጠሩበት ጊዜ ጀምሮ በዋናና በምክትል የሥልጣን እርከናቸው አገሪቱን እየመሩ ነበር::
ላገረሸው የአገሪቱ ግጭት በዋና መንስዔነት እየተጠቀሰ ያለው ቁጥሩ 100,000 የሚገመተው የፈጥኖ ደራሽ ሠራዊት ከመደበኛው ጦር ሠራዊት ጋር ስለሚቀላቀልበት ሁኔታ በጋራ ስምምነት ላይ መድረስ ስላልተቻለ ነው:: ምክንያቱ ምንም ይሁን ምን የሱዳን ሕዝብ በጸሎትና በጾም ላይ በሚገኝበት በዚህ የረመዳን ወር መከራ ወድቆበት ግራ ተጋብቷል:: ግጭቱ ተባብሶ ወደ ከፋ ቀጣናዊ፣ አህጉራዊና ዓለማቀፋዊ ደረጃ እንዳይሸጋገር ስጋቱን ካባበሱት ምክንያቶች መካከል የሚከተሉት ሁለቱ በቅድሚያው ረድፍ ላይ ይገኛሉ::
የጦር ሠራዊቱ መሪ ጄኔራል የሚሰጡት ምክንያት “ለችግሩ ዋና መንስዔ የሆነው በአክራሪነት የተፈረጁት የእስልምና ተከታዮች (Radical Islamists) ሴራ ነው” የሚል ሲሆን፤ በአንጻሩም ጄኔራል ሄሜዲት ጮክ ብለው የሚያስተጋቡት “የምንዋጋው ለዲሞክራሲ መከበር ግድ ስለሚለን ነው”ብለዋል::
የሁለቱ ጄኔራሎች ምክንያቶች ሌላ ጦስ እንዳይመዙ በአያሌው ተሰግቷል:: ያም ሆነ ይህ ለሱዳን የሰላም መፍትሔ የሚመነጨው ከራሷ ሕዝብ እንጂ የባዕዳን ጣልቃ ገብነትማ ምን ሊያስከትል እንደሚችል በሚገባ ይታወቃል:: ሱዳን ከቅኝ ገዢዎቿ ነፃነቷን ከተጎናጸፈችበት እ.ኤ.አ ከ1956 ጀምሮ “በአንጻራዊ ሰላም” የኖረችው ለአስራ አንድ ዓመታት ብቻ ነው:: በተረፈ ለ50 ዓመታት ያህል አንዳንዴ የባህል፣ አንዳንዴም የሃይማኖት፣ አልፎ አልፎም የብሔር ጉዳይ የጠብ መነሻ ሆኖ ስትታመስ ኖራለች::
ከጉያዋ ከወጣችው ደቡብ ሱዳን ጋር በዘይት ጉድጓድ ሃብት የይገባኛል ሙግት፣ ግጭትና በድንበር ማካለል ጉዳይ ዛሬም ቢሆን ሱዳን የሰላም እንቅልፍ እንደራቃት አለች:: “በቡሃ ላይ ቆረቆር” እንዲሉ ይህ ውስብስብ ችግሯ ያነሰ ይመስል ሌላ የእርስ በእርስ ግጭት ላይ መግባቷ አገሪቱን ክፉኛ እንዳያሽመደምድ ተሰግቷል::
ከራሳችን ሁኔታ ጋር ችግሩን እንገምግም ብንል እንኳን የእርሷ ጉዳት ለእኛም መትረፉ አይቀርም:: ለምሳሌ፤ የአፄ ቴዎድሮስ የትውልድ ሥፍራ የሆነችው ቋራ፣ አፄ ዮሐንስ ከመሃዲስቶች ጋር ተናንቀው የተሰውባት መተማ፣ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ከስደት አገር ከእንግሊዝ የቃል ኪዳን ጦር ጋር እየተዋጉ የገቡትና ለመጀመሪያ ጊዜ ሰንደቃላማችንን በክብር ያውለበለቡባት ኦሜድላ ሁሉም የሚገኙት በሱዳን ድንበር አካባቢ ነው::
ስለዚህ የሱዳኖች የእርስ በእርስ ግጭት ለእኛም ሊተርፍ ስለሚችል ችግራቸውን በሰላም እንዲፈቱ እስካሁን እየተደረገ እንዳለው በኢትዮጵያችንም በኩል ከፍተኛ ጥረት መደረግ ይገባል:: በደምም ሆነ በታሪክ ከሱዳን ህዝብ የተሳሰርን መሆኑን መረሳት አይገባም ? ለዚህም ነው “በጤና ለማደር ጎረቤት ሰላም ይደር” የሚል ርዕስ ለጽሑፋችን የሰጠነው:: የሰላም አምላክ ለሱዳን ሕዝብ ሰላሙን ያውርድልን::
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ) gechoseni@gmail.com
የሥነ ጽሑፍና የኮሙዩኒኬሽን ባለሙያ ናቸው።የኢትዮጵያ ደራስያን ማኅበርን ለዘጠኝ ዓመታት ያህል በፕሬዚዳንትነት መርተዋል።ከ1977 ዓ.ም ጀምሮ በአዲስ ዘመንና የዛሬይቱ ኢትዮጵያ ጋዜጣ፤ በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገራት ታትመው በሚሠራጩ የተለያዩ የኅትመት ውጤቶች ላይ (ዳግላስ ጴጥሮስ) በሚል የብዕር ስሙ በርካታ ጽሑፎችን አስነብበውናል።በግላቸው 12፣ ከሌሎች ጸሐፍት ጋር በርካታ መጻሕፍትን ለአንባብያን አቅርበዋል።
አዲስ ዘመን ረቡዕ ሚያዝያ 11 ቀን 2015 ዓ.ም