ጸሐፊው በዚህ አምድ ስለዋጋ ግሽበቱና እሱን ተከትሎ እየተባባሰ ስለመጣው የኑሮ ውድነት ላለፉት ሁለትና ሦስት አመታት በተደጋጋሚ መጣጥፎችን በማጠናቀር ለማስነበብ ሞክሯል። የግልም ሆኑ የመንግሥት የህትመት፣ የኤሌክትሮኒክስና የማህበራዊ ሚዲያዎች እንዲሁ በዋጋ ግሽበቱና በኑሮ ውድነቱ ላይ እልፍ አእላፍ ዘገባዎችንና ፕሮግራሞችን ሠርተዋል። ሆኖ የተገኘው ውጤት እዚህ ግባ የሚባል አይደለም። ጸሐፊው የሚፈለገውን ያህል ውጤት ሊገኝ ያልቻለው ባለድርሻ አካላት ተናበውና ተቀናጅተው ባለመሥራታቸው ነው ብሎ ያምናል። እንዲሁም ባለድርሻ አካላት የኑሮ ውድነቱን አሳሳቢነት በእኩል ደረጃ ተገንዝበውታል ብሎ አያምንም።
ስለሆነም በተለይ ሰው ሰራሽ የሆነውን የዋጋ ግሽበትና እሱን ተከትሎ እየተባባሰ የመጣውን የኑሮ ውድነት ለማረጋጋትና ዘላቂ መፍትሔ ለማግኘት ተቀናጅቶ መሥራት ስለሚያስፈልግና ከጊዜ ወደ ጊዜ ከኢኮኖሚያዊ ጉዳይነት ተሻግሮ ማህበራዊ ችግር እየጎነቆለ ፤ በዚህ የሚቀጥል ከሆነም የሰላም፣ የደህንነትና የጸጥታ ችግር ወደ መሆን እየዳኸ መገኘቱ ላይ ወጥ የሆነ ግንዛቤ ተጨብጦ የመፍትሔ ፍኖተ ካርታ ማስቀመጥ እንዲቻል እና አልበርት አነስታይን እንዳለው ችግሩን በፈጠረው አግባብ መልሶ መፍትሔ ማስቀመጥ ስለማይቻል ጸሐፊው ከተለመደው እይታ ወጣ ያለ አተያይ ይዞ መጥቷል። ችግሩን ከማራገብ ይልቅ መፍትሔ ለማመላከት ይሞክራል። ለዚህ ነው የዛሬው ጽሑፉ ችግሩ ላይ ሳይሆን ወደ መፍትሔነት ሊያመራ የሚችል የመነሻ ሀሳብ ማቅረብ ላይ ያተኮረው።
የዚህ መነሻ ሀሳብ አበይት አላማዎች ሁለት ናቸው። የመጀመሪያው ሰው ሰራሹን የኑሮ ውድነት ወይም ፈር የለቀቀውን የግብይት ሥርዓት ለማስተካከል የሚደረግ ጥረት በአንድ ወገን ወይም በመንግሥት ብቻ ዳር ሊደርስ ስለማይችል መላ ሕዝቡን ወይም ሸማቹን ማሳተፍ ይጠይቃል። ለዚህ ደግሞ አገር አቀፍ ንቅናቄን ማቀጣጠል ይጠይቃል። አገራዊ ምክክሩ ደግሞ በእርሾነት ማገልገል ግንባር ቀደም አላማው ነው።
የመነሻ ሀሳቡ ሁለተኛ አላማ ሻጩም፣ ሸማቹም፣ መንግሥትም፣ ባለድርሻ አካላት ማለትም የሃይማኖት ተቋማት ምክር ቤት፣ የአዲስ አበባ የንግድና የዘርፍ ማህበራት፣ ብዙኃን መገናኛዎች፣ እንደ የኢትዮጵያ ሸማቾች መብት ተቆርቋሪ ድርጅት ያሉ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች፣ ወዘተረፈ የኑሮ ውድነቱ መፍትሔ ካልተበጀለት የህልውናና የደህንነት ስጋት ሊሆን እንደሚችል መግባባት ላይ በመድረስ በዚህ ልክ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ የጋራ ፍኖተ ካርታና የድርጊት መርሀ ግብር ማዘጋጀት ነው።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ከናይጄሪያ ቀጥሎ ከፍተኛ የሕዝብ ቁጥር ያላት አገር መሆኗ ይታወቃል:: አንዳንድ ይፋዊ ያልሆኑ መረጃዎች የሕዝብ ቁጥሯን እስከ 117 ሚሊዮን ይተነብያሉ:: ይህ ሕዝብ፤ በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ ሸማች ወይንም ሻጭ ነው። ዜጎች በአንድ አጋጣሚ ሸማች ሆነው በሌላ ጊዜ ደግሞ ሻጭ ይሆናሉ:: ይህ ሁላችንም ሸማቾች እንደሆነ ያሳያል። የአገራችን ሸማች በተመጣጣኝ ዋጋ፣ ጥራት ያለው፣ ጤንነቱ፣ ደህንነቱ የተጠበቀ ሸቀጥ አገልግሎት አማርጦ፣ አወዳድሮ የመሸመት መብት ቢኖረውም እውን ማድረግ ባለመቻሉ ለዘርፈ ብዙ ችግሮች ተዳርጎ ይገኛል::
ለኑሮ ውድነት፣ ለጤና ጠንቅ ለሆኑ ሸቀጦች እና ጥራት በጎደላቸው ሸቀጦች ጤናው እየታወከ ይገኛል:: ከሁሉም በላይ በሸማቹ፣ በሻጩና በመንግሥት መካከል ያለው ግንኙነት የተዛባ፣ ኢፍትሐዊና ኢዴሞክራሲያዊ መሆኑ በተለይ ሸማቹን ሁልጊዜ ተበዳይ፣ ተገፊና ተጠቂ አድርጎታል። ይህን የተዛባ ግንኙነት የሚያስተካክልና የተነጠቀውን መብትና ያጣውን ጥቅም የሚያስመልስ አደረጃጀት ያስፈልጋል:: በተለይ ወደ ንግድና ቀጣናዊ ትስስር የታጠፈው የንግድ ውድድርና የሸማች ባለስልጣን ራሱን ችሎ ሊደራጅ ይገባል።
የንግድና የግብይት ሥርዓቱን የሚቆጣጠረው ይህ ባለስልጣን ራሱን ችሎ ሊጠናከር ሲገባው በሚኒስቴሩ ስር መሆኑ የጥቅም ግጭት ይፈጥራል። ኢትዮቴሌኮምንና የኮሙኒኬሽን ባለስልጣንን በአንድ የማደራጀት ያህል ነው። ሆኖም የኑሮ ውድነቱ ጉዳይ ከአደረጃጀት ያለፈ አንገብጋቢ ችግር ስለሆነ ችግሩን እያነሳን ከማለቃቀስ ወደ መፍትሔው ማምራት ግድ ይላል።
መንግሥት በየደረጃው ከፍተኛ ቁጥር ያለውን ሸማች መብቱንና ጥቅሙን ለማስከበር ጥረት ቢያደርግም በሚፈለገው ደረጃ ውጤታማ ሊሆን አልቻለም:: ላለፉት 30 አመታት በአገራችን ሲንከባለል የመጣውና ተባብሶ የመጣውን ከፍተኛ የዋጋ ግሽበትና የኑሮ ውድነት ተፈጥሯል። መንግሥት ዜጋውን በእጅጉ እየፈተነ ያለውን የኑሮ ውድነት ለማረጋጋት ያደረጋቸው ጥረቶችም የሚፈለገውን ያህል ውጤታማ መሆን ባለመቻላቸው ከኢኮኖሚያዊ አጀንዳነት አልፎ የህልውና የሰላም የደህንነትና የጸጥታ ስጋት ወደመሆን እየዳኸ ይገኛል።
ስለሆነም የኑሮ ውድነቱና የዋጋ ግሽበቱ በጊዜ መፍትሔ ካላገኘ የሰላም የደህንነትና የጸጥታ አገራዊ ችግር የመሆን አቅም እንዳለው በመግባባት ተገቢውን ትኩረት እንዲያገኝና በቅንጅት መረባረብ እንዲቻል አገራዊ ምክክር እንዲካሄድ ጸሐፊው ይመክራል።
የዚህ አገራዊ ምክክር ዐቢይ ዓላማ የኑሮ ውድነቱንና የዋጋ ግሽበቱን አንገብጋቢና አገራዊ የህልውና ጉዳይ መሆኑን ለመንግሥት ለሕዝብና ለተቋማት በማስገንዘብ የጋራ የመፍትሔ ፎኖተ ካርታ አዘጋጅቶ ወደ ተግባር የሚመራ ሲሆን፤ በምክክሩ የኑሮ ውድነቱም ሆነ የዋጋ ግሽበቱ ከኢኮኖሚ ችግርነት ባሻገር የህልውና ጉዳይ መሆኑን በመገንዘብ የአጭር የመካከለኛና የረጅም ጊዜ የመፍትሔ ሀሳቦችን ቀምሮ ፈጻሚያቸውን በመለየት ቆጥሮ ወደትግበራ መግባት ነው። አፈጻጸማቸውን በዚሁ የምክክር መድረክ በተሰየመ ጉባኤ ይገመገማል። አቅጣጫ ይሰጣል። ይመራል። የምክክር አጀንዳዎች ሊዳብሩና ሌሎች ርዕሶችን ማካተት ቢችሉም ጸሐፊው ለመነሻነት የሚከተሉትን አጀንዳዎች አቅርቧል።
የምክክር አጀንዳዎች፦
ሀ. የኑሮ ውድነቱና የዋጋ ግሽበት ወቅታዊ ሁኔታና በሕዝብ በመንግሥትና በተቋማት ላይ የፈጠረው ከፍተኛ ጫና ፤
ለ .ግልፅ አቅጣጫ ተቀምጦ በተቀናጀ ርብርብ ኢኮኖሚያዊ ቀውሱ ካልተፈታ ወደ የሰላም፣ የህልውና፣ የደህንነትና የጸጥታ ችግር የመባባስ ስጋት መደቀኑ፤
ሐ. ከመድረኩና ከተሳታፊዎች የተቀመረ የጋራ የመፍትሔ ሀሳቦችን ማመላከትና መቀመር፤
የመነሻ ሀሳብ አቅራቢ፤
በሀ እና ለ የተመለከቱ አጀንዳዎችን በተመለከተ የኢትዮጵያ የኢኮኖሚክስ ባለሙያዎች ማህበር ወይም የአአዩ ወይም የማህበራዊ ጥናት መድረክ የመነሻ ሀሳብ ወይም ጥናት ሊያቀርቡ ይችላሉ።
በአገራዊ ምክክሩ የሚሳተፉ፤
በአገራዊ ምክክሩ ይሳተፋሉ ተብሎ ከሚጠበቁ ባለድርሻ አካላት መካከል የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር፣ የፋይናንስ ሚኒስቴር፣ የፕላን ኮሚሽን፣ ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ፣ የጠቅላይ ሚ/ር ጽ/ቤት፣ ማህበራዊ ጥናት መድረክ፣ ማይንድ ኢትዮጵያ፣ የፌዴራል የሸማቾች ህብረት ሥራ፣ የአአ ከንቲባ ጽ/ቤት፣ የአአ ንግድ ቢሮ ፣ የንግድ ም/ቤት፣ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ፣ የሚዲያ ካውንስል፣ የኢኮኖሚ ባለሙያዎች ማህበር ፣ የእንባ ጠባቂ ኮሚሽን ፣ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ፣ የኢትዮጵያ ሸማቾች መብት ተቆርቋሪ ድርጅት፣ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ም/ቤት፣ የሸማቾች ባለስልጣን፣ የሸማቾች ሕብረት ሥራ ማህበራት ፣ የጋዜጠኞች ማህበር ፣ ማህበራዊ አንቂዎች፣ ፌዴራል ፖሊስ፣ አዲስ አበባ ፖሊስ፣ ተስፋ ለኢትዮጵያ የሸማቾች ማህበር፣ ወዘተረፈ ይገኙበታል። የተሳታፊዎች ብዛት የሚዲያ ሰዎችን ጨምሮ ከ500-600 ሊደርስ ይችላል። የዚህ አገራዊ ምክክር አዘጋጆች የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚ/ር፣ የኢትዮጵያ ሸማቾች መብት ተቆርቋሪ ድርጅት፤ የፍሬደሪክ ኤበርት ስቲፍተንግ ኢትዮጵያ፤ የኢኮኖሚክስ ባለሙያዎች ማህበር፣ የኢፌዴሪ ሰላም ሚ/ር እና አጋሮቹ ጋር በመተባበር ሊሆን ይችላል።
የዚህ አገራዊ ምክክር ግብ የኑሮ ውድነቱም ሆነ የዋጋ ግሽበቱ የህልውና አደጋ ወይም የሰላምና የደህንነት ስጋት ሊሆን እንደሚችል በመንግሥት በሕዝብና በተቋማት መግባባት ላይ በመድረስ ለመፍትሔው አገራዊ ንቅናቄን በአዲስ አበባ ማስጀመር ሲሆን ይህን ተሞክሮና መድረክ ቀምሮ በሁሉም ክልሎችና በሁለቱ የከተማ አስተዳደሮች እስከ ወረዳ በማስፋት ግንዛቤና አደረጃጀት ፈጥሮ ቀጣይነትና ተከታታይነት ያላቸውን ተግባራት በማከናወን ተቋማትን በተለይ ሸማቹን በግብይት ሥርዓቱ የወሳኝነት ሚና እንዲኖረው/empower/ ማድረግ ነው። ስለመፍትሔው ይሄን ያህል የመነሻ ሀሳብ ካቀረብሁ፤ ስለኑሮ ውድነቱ አሳሳቢነት ደግሞ ከተለያዩ ምንጮች የቀራረምሁትን አሁናዊ መረጃ ላጋራ።
ልክ እንደ ሌሎች አገሮች ሁሉ የኑሮ ውድነትና የዋጋ ግሽበት በኢትዮጵያም ማሳሰብ ከጀመረ ከራርሟል:: የኑሮ ውድነቱ መነሻ በርካታ መንስዔ ያለው ችግር እንደሆነ ይነገራል:: በመፍትሔነትም በርካታ ጉዳዮች ታሳቢ ሊደረጉ እንደሚገባ ማሳሰቢያ ሲቀርብ ይታያል:: ለረዥም ዓመታት ሳያቋርጥ የቀጠለው የዋጋ ግሽበት የኑሮ ውድነትን እየወለደ በዚሁ የሚቀጥል ከሆነ፣ ውጤቱ ወዴት ያመራል የሚለው ጉዳይ ደግሞ አሳሳቢነቱ የጎላ መሆኑ ተደጋግሞ ይነገራል ይለናል በአማርኛው ሪፖርተር ላይ የወጣ ዘገባ ::
ከሰሞኑ በተለይ በስንዴና በጤፍ ላይ የተፈጠረው የዋጋ ንረትና መናጋት፣ በኢትዮጵያ ያለውን የኑሮ ውድነት ምንጭና ምን ሊደረግ ይገባል ስለሚለው ጉዳይ ብዙ እያወያየ ይገኛል:: በኢትዮጵያ የሚታየው የኑሮ ውድነት ወይም የዋጋ ንረት ጤናማ ያልሆነና ኢኮኖሚያዊ መነሻ የሌለው ነው የሚል አስተያየትም ይሰማል:: የዋጋ ንረቱና የኑሮ ውድነቱ ከዚህ ቀደምም ቢሆን በንግድ አሻጥርና በሕገወጥ ግብይት የመጣ ነው የሚል አመክንዮ ሲያሰጥ ቆይቷል::
“The Ethiopian Economist View” በሚባለው የፌስቡክ፣ የቴሌግራምና የዩቲዩብ ገጽ ላይ የተለያዩ የኢኮኖሚ ጉዳዮችን በመተንተን የሚታወቁት የምጣኔ ሀብት ባለሙያ አቶ ዋሲሁን በላይም፣ የኑሮ ውድነቱ በኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ምንጭ አለው የሚለውን ሐሳብ
ይጋሩታል::”የፖለቲካዊ ለውጦች ፍላጎትን ይጨምራሉ:: ለምሳሌ በግጭትና በጦርነት የተነሳ ሰዎች ይፈናቀላሉ:: እንዲሁም ከአምራችነት ወደ ምርት ፈላጊነት ሕይወታቸው ይቀየራል::
ይህ ደግሞ የምርት ፈላጊ ቁጥርን ስለሚጨምር ዋጋን ያሻቅባል:: “የከተሞች ማደግ፣ የመንደሮች መስፋፋትና የመንገድ ትራንስፖርት እንቅስቃሴ መጨመር የባጃጅ ትራንስፖርት አቅርቦትን አስፈላጊ አድርጎታል:: በየቦታው፣ በየጉምሩክ መፈተሻ ኬላውና በየወደቡ አላስፈላጊ ቀረጥና ታሪፍ መጨመርም ዋጋን ያንራል:: ዕቃ ከውጭ ለማስገባት ታሪፍና ቢሮክራሲ ሲበዛ ዞሮ ዞሮ ሸማች ላይ ይመጣል:: መሬት፣ መብራት፣ ውኃ፣ መንገድ ለማግኘት አምራቹ ዋጋና ቢሮክራሲ ሲበዛበት ችግሩ ተመልሶ ሸማቹ ላይ ይወድቃል፤”
አቶ ዋሲሁን እንደሚሉት፣ ወትሮም 40 በመቶ ላይ ብቻ ተወስኖ የቆየው የኢትዮጵያ አምራች ኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅም፣ በተለያዩ ፖለቲካዊ ዕርምጃዎች የሚስተጓጎል ከሆነ የምርት አቅርቦት ችግርን የበለጠ ይጎዳል:: አምራቾች የመጨረሻው የሸማች ኅብረተሰብ ላይ የሚያወርዱት ዋጋ የማምረቻ ወጪንና ትርፍን ብቻ ሳይሆን፣ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ያልሆኑ ጉዳዮችንም ታሳቢ ያደረገ መሆኑን ይገልጻሉ:: የኃይል አቅርቦት፣ የብድር አቅርቦት፣ የውጭ ምንዛሪ አቅርቦት ብቻ ሳይሆኑ የሠለጠነ የሰው ኃይል የማግኘት፣ እንዲሁም የተቀላጠፈ ቢሮክራሲያዊ አሠራር የማግኘት፣ አስተማማኝ የመሠረተ ልማት አቅርቦት ብቻ ሳይሆን አስተማማኝ ፀጥታና የደኅንነት ዋስትና የማግኘት አመቺነትንም ታሳቢ በማድረግ፣ አምራቾችና አቅራቢዎች ሸማቹ ኅብረተሰብ የሚከፍለውን ዋጋ እንደሚተምኑ አስረድተዋል::
በኢትዮጵያ ኢኮኖሚክስ አሶሴሽን ከፍተኛ ተመራማሪ የሆኑት አረጋ ሹመቴ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ አገሪቱ ያለችበት ሰላማዊ እንቅስቃሴ ስንዴን ወይም ጤፍን ከቦታ ወደ ቦታ አጓጉዞ ለመሸጥ አመቺ መሆን አለመሆኑም ዋጋውን እንደሚበይን ይናገራሉ:: ምርት አለ ተብሎ በሚታመንበት ወቅት እንኳን ምርት ከገበያ የሚታጣውና ዋጋው የሚንረው በአገሪቱ ሰላምና ፀጥታ ሁኔታ ችግር መሆኑንም ያሰምሩበታል::”አገሪቱ ባለሁለት አኃዝ የዋጋ ግሽበት ማስተናገድ ከጀመረች 20 ዓመታት አስቆጠረች:: ይህ የዋጋ ግሽበት ደግሞ ከሥራ አጥነት፣ ካልተረጋጋ የኢኮኖሚ ዕድገት፣ ከውጭ ምንዛሪ እጥረትና ከውጭ ንግድ ሚዛን መዛባት ከመሳሰሉ ዓበይት የኢኮኖሚ ቀውሶች ጋር ሲደራረብ ችግሩን ያከፋዋል፤”በማለት ለጋዜጣው ይናገራሉ::
የምጣኔ ሀብት ባለሙያው አቶ ዋሲሁን፣ «የኑሮ ውድነት የዋጋ ንረትና የሰዎች የመግዛት አቅም መዳከም ተደምረው የሚፈጥሩት ችግር ነው፤» ይሉታል:: የዋጋ ንረቱ መነሻ በቀጥታ ከፍላጎት መጨመር ጋር የተገናኘ መሆኑን የሚጠቅሱት ባለሙያው፣ የዜጎች ተጨማሪ ገቢ የማግኘት ዕድል የጠበበ ከመሆኑ ጋር ተዳምሮ ችግሩ መክፋቱን ያስረዳሉ:: «ለአንዳንዶች የጤፍ በኪሎ ግራም አንድ መቶ ብር መግባትና ብዙም ሳይቀንስ ተሰቅሎ መቅረት ጉዳያቸው ላይሆን ይችላል:: ከጤፍ ይልቅ የሱዙኪ ተሽከርካሪ ዋጋ መውጣትና መውረድ የሚያሳስባቸው አሉ:: ይሁን እንጂ ገበያው በየቀኑ ሰዎችን እየተፋቸው፣ የመኖር ዋስትናን እያናጋ፣ ብዙ ሰውም በረንዳ እየወጣ በየቀኑ እያየን በመሆኑ፣ ችግሩ ኢኮኖሚያዊ ብቻ ሳይሆን ፖለቲካዊ መፍትሔዎችን የሚሻበት ደረጃ ላይ እንገኛለን፤» ብለዋል::
ሻሎም ! አሜን ።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 10/2015