አሸባሪው የትግራይ ወራሪ ቡድን ባለፉት ጊዜያት በሰውና በንብረት ላይ ያደረሰው ግድያና ውድመት በተለያዩ የመገናኛ ብዙሃን ሲዘገብ መቆየቱ ይታወቃል። ቡድኑ በዚህ ድርጊቱ ሳያበቃና ሳያፍር አሁንም በድጋሚ የጥፋት ጦሩን ለመስበቅ እየተዘጋጀ ስለመሆኑ እየተሰማ ነው። ቀደም ሲል ያደረሰውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት ለመድገምም የጦርነት ነጋሪቱን እየጎሰመ ነውና በዚህ ዙሪያ ስለተፈጸመውና ሊፈጸም ስለሚችለው ሰብዓዊ መብት ጥሰትን እንዲሁም ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት ዝምታ ጋር ተያይዞ አዲስ ዘመን የቀድሞ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ኮሚሽነር አምባሳደር ጥሩነህ ዜና ጋር ያደረገውን ቃለ ምልልስ እንደሚከተለው አጠናቅሮ አቅርቧል።
አዲስ ዘመን፡- ቃለ ምልልሱን ለሰብዓዊ መብት ጥሰት ዋና ምክንያት ናቸው ከሚባሉ ጉዳዮች እንጀምር?
አምባሳደር ጥሩነህ፡- ይቻላል! የሰብዓዊ መብት በተለያዩ ሃገራት በተለያዩ ምክንያቶች ይጣሳል። ነገር ግን በሁሉም ሃገራት ሊባል በሚችል ሁኔታ ጥሰቱ የሚፈጸመው በሃገሪቱ ባለው ሥርዓት ምክንያት ነው ብዬ አስባለሁ። ከሥርዓት ውጭ የፖለቲካ ባህል እንዲሁም የሕዝብ ግንዛቤ እጥረት አለ፤ ለሰብዓዊ መብት ጥሰት ምክንያት የሚሆኑት እነዚህ ሁሉ ተደምረው ነው።
ደግሞም የሰብዓዊ መብት ጥሰት የሚፈጸመው በሁሉም ሃገሮች ነው ቢሆንም ጥሰቱ የሚፈጸመው በተለያየ ደረጃና በተለያየ ምክንያት ነው። ነገር ግን በእድገት ወደኋላ በቀሩ ሃገራት ደግሞ የበለጠ ይጎላል። ይህም የሚሆንበት ምክንያት በመጀመሪያ ደረጃ አጠቃላይ ሰብዓዊ መብት ምንድን ነው? የሰው ልጆች ግንኙነት ምን መምሰል አለበት? በመሪውና በሚመራው ሕዝብ መካከል ያለው ግንኙነት ምን መሆን አለበት? የሚሉ ጥያቄዎች ባላደጉ አካባቢዎች በግልጽ መልሳቸው የተቀመጠ አይደለም።
አዲስ ዘመን፡- በቅርቡ አሸባሪው የሕወሓት ቡድን በወረራ ተቆጣጥሯቸው የነበሩ አካባቢዎች እንደነበሩ የሚታወስ ነው፤ በእነዚያ ወቅት የደረሰው የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንዴት ይገልጹታል?
አምባሳደር ጥሩነህ፡- በእርግጥ ጦርነት በሚኖርበት አካባቢ ያደገ ሃገርም ይሁን ያላደገ አገር የሰብዓዊ መብት ይጠበቃል ማለት አይቻልም። ጦርነት በሚካሄድባቸው አካባቢዎች ሰብዓዊ መብት ጥሰት ይፈጸማል፤ ደግሞም የሰው ሕይወት ከመቅጠፍ የበለጠ ሰብዓዊ መብት ጥሰት የለም። እንደሚታወቀውም ጦርነት ሙሉ በሙሉ ሰብዓዊ መብትን አክብሮ ይሄዳል ማለት አይቻልም።
እንዲያም ሆኖ ግን አንዳንድ ጉልህ የሆኑ ጥሰቶችን ማስቀረት አለበት በማለት የወጡ የዓለም አቀፍ ሕጎች አሉ፤ እነዚህ ሕጎች ተዋጊ ኃይላት በተለያየ ደረጃ የሚከተሏቸው ናቸው። ነገር ግን ኢትዮጵያን ወደመሰሉ ታዳጊ ሃገራት በሚመጣበት ጊዜ እነዚያን የዓለም አቀፍንም ሆነ የሃገር ውስጥ ሕጎችን ጦርነትም እየተካሄደ ቢሆን ሙሉ በሙሉ እንኳ ባይሆን በሚቻለው ሁኔታ መጠበቅ አለባቸው ተብሎ ክትትል የሚደረግበት አካሄድ በጣም አነስተኛ ነው። ምክንያቱም በተዋጊ ኃይላት መካከል ያለው የግንዛቤ ደረጃ ራሱ በጣም አነስተኛ ነው። ስለሆነም በዚህ ምክንያት ሰብዓዊ መብት ጥሰቶቹ ከፍ ይላሉ።
በተለይ በሃገራችን በሰሜኑ ክፍል በተደረገ ጦርነት በውጊያው ላይ የትግራይ ክልልም በከፍተኛ ደረጃ ሚሊሻ መልምሎ ነው ወደኢትዮጵያ የላከው፤ ይህ በሚሆንበት ጊዜ በሕዝብ መካከል የጥላቻ ፕሮፖጋንዳ እየተካሄደ ነው። እነዚህ ሁሉ ተደምረው የሚያመጡት የሰብዓዊ መብት ጥሰትን ነው። ብሎም የሚያስከትሉት የሰው ሕይወት መጥፋትን ነው። በመሆኑም በሰሜኑ አካባቢ የተፈጸመው ይህ ነው ብዬ አስባለሁ።
አዲስ ዘመን፡- እርስዎም እንደሚያውቁት የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን በተለይ በሰሜኑ ክፍል የተካሄደውን ጦርነት አስመልክቶ የተለያዩ ሪፖርቶችን ሲያወጣ ነበር፤ ያቀረበውን ሪፖርት አስመልክቶ በሃገር ውስጥም ሆነ በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ለሪፖርቱ የተሰጠውን ምላሽ እንዴት ይገልጹታል?
አምባሳደር ጥሩነህ፡- ሰብዓዊ መብት ሪፖርትን የሚመለከቱ አካላት ሐሳባቸውን የሚሰነዝሩት እንደየፖለቲካ ዝንባሌያቸው ያንን ተርጉመው ነው። የሰብዓዊ መብት ሪፖርት ለምሳሌ በምዕራባውያኑ የሚደገፉ ተቋማት፣ እነርሱ ፋይናንስ በሚያደርጉ ተቋማት፣ የእነርሱን ሐሳብና አመለካከት በሚያንጸባርቁ አካላት ተዘጋጅቶ በሚቀርብበት ጊዜ የምዕራቡ አካባቢ ሚዲያም ሆኑ መንግሥታት በአንድ ድምጽ በሚባል ሁኔታ የሚደግፉበት ሁኔታ አለ። ይህ ሄዶ ሄዶ ከፖለቲካ አተያያቸው ጋር የተያያዘ ነው።
ሰብዓዊ መብትን የሚገለገሉበት እንደመሣሪያ ነው። ይህ መሆን ከጀመረ ቆይቷል። ስለዚህ የፖለቲካ አመለካከታቸውንና ግንዛቤያቸውን ተከትሎ ነው የሚሄደው እንጂ በእውነት ለሰብዓዊ መብት ብለው አገሮችም ሆኑ ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከታቸው ድርጅቶች የሉም።
የሰብዓዊ መብት ኮሚሽነር ከመሆኔም በፊት በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) በነበርኩበት ጊዜ አብሬ ሠርቻለሁ። የሰብዓዊ መብት ሕጎች በሚረቀቁበት ጊዜና የሰብዓዊ መብት ሪፖርቶች በሚቀርቡበት ጊዜ በተመድ ሳለሁ የራሴንም ሃሳብ እሰነዝር ነበር። ሕጎቹ መሬት ላይ ወርደው በሥራ ላይ በሚውሉበት ጊዜ ምን መምሰል አለባቸው የሚለውን የራሴ የሆነ አስተያየት እስጥ ነበር። ምክያቱም ሁሉም የራሱን ይዞ ነው የሚመጣ። ደግሞም ሁሉም የየራሱ እንዲጸባረቅ ነው የሚፈልገው። እኛ ዝም ብለን የሌላውን ጭራ ይዘን መከተል የለብንም። የራሳችን የሆነ ነገር መኖር አለበት ብዬ አስባለሁ። የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሆኜ በተመረጥኩበት ጊዜ የራሴን አመለካከት ማለትም ሰብዓዊ መብት በተባበሩት መንግሥታት በሚቀረጽበት ጊዜ በሥራ እንዲተረጎም ሃገራቱ እንዴት ይናገሩ እንደነበር እኔም እንዴት አድርጌ ሐሳቤን እስነዝር እንደነበር ያንን ሁሉ አገናዝቤ ነው ስሠራ የነበረው፡
ይሁን እንጂ ኮሚሽነር ከመሆኔ በፊት የተባበሩት መንግሥታት በነበርኩበት ጊዜ እቸገርባቸው የነበሩ አንዳንድ ነገሮች ነበሩ፤ ለአብነት ያህል አገሮች የሰብዓዊ መብት ጥሰት በሚፈጽሙበት ጊዜ የኢኮኖሚ ማዕቀብ መደረግ አለበት ይባላል፤ ነገር ግን መደረግ የሚገባው ምን አይነት የኢኮኖሚ ማዕቀብ ነው? መደረግስ ያለበት በማን ላይ ነው? የሚጣለው የኢኮኖሚ ማዕቀብ የታችኛውን የኅብረተሰብ ክፍል የሚጎዳ ከሆነ ቆንጮው ላይ ያሉ አካላት በፈጸሙት ስህተት ደሃውን የበለጠ የምንጎዳ ይሆናልና እኛ ራሳችን የሰብዓዊ መብትን እየጣስን ነው ወይስ እውን የሰብዓዊ መብትን እየጠበቅን ነው? በሚል ዙሪያ ክርክር ነበር።
አዲስ ዘመን፡- እርስዎ እንዳሉት በአንድ ታዳጊ አገር ስልጣን ላይ ያለው አካል ባጠፋው ጥፋት የኢኮኖሚ ማዕቀቡም ሆነ ሌላ አይነት ማዕቀብ ሲጣል ይስተዋላል፤ ለዚህም በምክንያትነት የሚጠቀሰው ሰብዓዊ መብት ስለተጣሰ ነው የሚል ነው፤ ይሁንና ማዕቀቡ መልሶ ሰብዓዊ መብታቸው ተጥሷል የተባሉ የኅብረተሰብ ክፍሎችን ሲጎዳ ይታያልና መብታቸው መከበሩ ምኑ ላይ ነው ይላሉ?
አምባሳደር ጥሩነህ፡- እንዳልኩሽ የኢኮኖሚ ማዕቀቡን በአንድ አገር ላይ መጣል የደሃውን ሕዝብ መብት መጣስ አይሆንም ወይ ስንል ባነሳነው ጥያቄ በብዙ ተከራክረን በወቅቱ ወደስምምነት መምጣት ችለናል። ስምምነቱም የነበረው ጥፋት አጥፊውን ከሕዝቡ በመለየት እርሱ ላይ መጣል የሚል ነበር።
አዲስ ዘመን፡- ታዲያ ይህ እውን እየተተገበረ ነው ብለው ያስባሉ?
አምባሳደር ጥሩነህ፡- አዎ! ሁሌም ባይሆን አንዳንድ ጊዜ ይታያል።
አዲስ ዘመን፡- በቅርቡ በአሸባሪው ቡድን አማካይነት በኢትዮጵያውያኑ ላይ በተከፈተው ጦርነት የደረሰው የሰብዓዊ መብት ጥሰት ቁጥር ስፍር እንደሌለው ጥናቶች አመላክተዋል፤ በተደጋጋሚም ሪፖርቶች ተደምጠዋልና በዓለም አቀፉ ደረጃ ጉዳዩ የሚመለከተው በአሸባሪው ቡድን ላይ ጫና መፍጠር ያልቻለው ስለምንድን ነው?
አምባሳደር ጥሩነህ፡- ይህ ለምን ሆነ ላልሽው ቀደም ብዬ እንደተናገርኩት ሰብዓዊ መብት በፖለቲካ የተጠቀለለ በመሆኑ ነው። ሰብዓዊ መብት የፖለቲካ መሣሪያው በመሆኑ እነርሱን የሚደግፉትን ቡድኖች የሚጠቅም እና የሚደግፍ ከሆነ ያጎሉታል። ያ ካልሆነ ደግሞ ያጥላሉታል። በመጨረሻም ይጥሉታል።
ነገር ግን እነዚህ ያደጉ አገሮች እንደ ኢትዮጵያ በኢኮኖሚም ሆነ በፖለቲካው ቀና ቀና የሚሉና ነገም ሊሆኑ የሚችሉ አገሮች ያሰጓቸዋል። በተለይ እንደ ኢትዮጵያ ተስፋ የሚታይባቸው አገሮችና የሕዝብ ብዛታቸውም ከመቶ ሃያ ሚሊዮን በላይ የዘለቁ አገሮች ከሌሎቹ ጋር ኅብረት ፈጥረው በአንድነት የሚነሱ ከሆነ እና በሚሊታሪም ሆነ በኢኮኖሚ በአግባቡ መደራጀት ከጀመረ አካባቢውን አስገድዶ በሚፈልጉት መንገድ ለመምራት ያስቸግራል። ይህ በመሆኑ እንዲህ አይነቱ አካሄድ አይፈለግም።
ስለዚህ ይህንን አውቀን አንገታችንን እንዳይዙን ምን ማድረግ አለብን በሚለው ዙሪያ እጅግ በጣም መሥራት አለብን። እነርሱ የሚያደርጉት ነገር ቢኖር እርስ በእርሳችን እንድንባላ ነው እንጂ በቀጥታ መጥተው አንገታችንን አይዙም። እንድንዳከም የሚያደርጉንና እርስ በእርስ ተበላልተን እንድናልቅ የሚያደርጉት በዚህ ሁኔታ ነው። እነርሱ እንድንሆን የሚፈልጉትን ሁኔታ የሚያስፈጽሙት በሌላ ተወካይ ነው። እንደእርሱ አይነት መሣሪያ ደግሞ እንዲጠፋባቸው አይፈልጉም።
እንደ እኔ እንደ እኔ ለምን ቤታችን መጥተው አላጸዱልንም ብሎ ማሰብ የዋህነት ነው። ምክንያቱም ይህ በእነርሱ ዘንድ የሚፈለግ ዓይነት አካሄድ አይደለም። እነርሱም ይህን አያደርጉልንም፤ ነገር ግን የእነርሱ መሣሪያ ከሆንን ሊያስተካክሉልን ይችላሉ።
አዲስ ዘመን፡- እንደሚታወቀው አሸባሪው ቡድን የጦርነት ነጋሪት መጎሰም ከጀመረ ውሎ አድሯል፤ ይህ ደግሞ ለሰብዓዊ መብት ጥሰት የአንበሳውን ሚና ይጫወታልና ለመከላከል መደረግ ያለበት ምንድን ነው ይላሉ?
አምባሳደር ጥሩነህ፡- እውነት ለመናገር በዚህ ሁሉ የበለጠ ተጎጂ የሚሆነው የትግራይ ሕዝብ በመሆኑ እጅግ በጣም ያሳዝነኛል። ይህ ኃይል ባለፈውም ሆነ አሁን አካሄዳለሁ በሚለው ጦርነት ውስጥ ትልቁ ተጠቂ የትግራይ ሕዝብ ነው። በእርግጥ ይህ አመራር የትግራይን ሕዝብ እየጠቀመ ነው ወይ? ምናልባትም የትግራይ ወታደር የሰብዓዊ መብት ጥሰቱ ፈጻሚ ሊሆን ይችላል፤ በዚህ ሂደት እየተጎዳ ያለው የትግራይ ሕዝብ ነው። የኢትዮጵያ ሕዝብ በብዙ መንገድ ከትግራይ ክልል ሕዝብ እጅግ የተሻለ ነው። ነገር ግን የትግራይ ክልል ሕዝብም ያው የኢትዮጵያ ሕዝብ ነውና ጉዳቱ ከፍ ያለ ነው። ምክንያቱም የሰብዓዊ መብት ጥሰቱን የሚያመጣው አሸባሪው ቡድን ነው እንጂ እኔ የትግራይ ክልል ሕዝብ በአሸባሪነት አልተፈረጀም።
አሁን ሌላ ትርምስ ለመፍጠር ወደጦርነት የሚንደረደሩ ከሆነ በሰው ልጅ ላይ የከፋ መከራ እንደሚደርስ አጠያያቂ አይደለም። ከመከራዎቹ ውስጥ አንዱ በርካታ የትግራይ ልጅ ማለቁ ተጠቃሽ ነው። ምክንያቱም ጦርነት ወደገበያ የመሄድ ያህል የምናቀለው ተግባር አይደለምና ነው። በኢትዮጵያ በኩል ስልጡን ወታደሮች አጥረው የያዙትን ድንበር ጥሼ ወደ ኢትዮጵያ እገባለሁ የሚለው እሳቤ የትግራይ ልጆችን ከስልጡን ወታደሮች ፊት እማግዳቸዋለሁ እንደማለት ነውና አሸባሪው ቡድን ለወታደሮቹ ምንም አይነት ርህራሄ አለመኖሩን ነው የሚያመላክተው።
እንደ እኔ የትግራይን ክልል እመራለሁ የሚል አካል ከኢትዮጵያ በኩል የሚቀርብለትን የሰላም ጥሪ ተቀብሎ በሁለቱም በኩል ያለውን ሕዝብ ሰላም እንዲያገኝ የሚደረግበት ሁኔታ ቢፈጥር ነው ደስታዬ። አንድነትን በማጠናከር ትልቋን ኢትዮጵያ ለማስቀጠል ጥረት ቢደረግ እመርጣለሁ። ሕልሜም ይህ ሲሆን፣ ለዚህ ስኬት ደግሞ እጸልያለሁ።
አዲስ ዘመን፡- የአገራዊ ምክክር ኮሚሽን ተቋቁሞ ወደሥራ መግባቱ ለሰብዓዊ መብት መከበር አስተዋጽዖው የት ድረስ ነው ብለው ያስባሉ?
አምባሳደር ጥሩነህ፡- በመጀመሪያ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንዲመጣ ካደረጉት ነገሮች ውስጥ አንዱ አለመከባበሩ፣ አለመተማመኑ፣ አለመግባባቱና አንዱ ሌላውን አለማዳመጡ ነው። ስለዚህ እነዚህን ችግሮች ለማስወገድ ውይይት ይደረግ በሚባልበት ጊዜ በጋራ በመሆን ያሉብንን ችግሮች በጋራ እንፍታ፤ ወደ መገዳደል፣ መሰዳደብ እንዲሁም ወደአለመግባባት አንሂድ ነው። ምክንያቱም የሰው ዘር ነን፤ ደግሞም የሰለጠንን ሕዝቦች ነን ካልን በውይይት የማይፈታ ነገር የለም። ስለሆነም ችግሮቻችንን በውይይት እንፈጽም ነው መባል ያለበት።
ይህ ኮሚሽንም የተቋቋመበት መርሕ ይህ ነው። የተቋቋመው ኮሚሽን ለአንዱ ቡድን ተሟግቶ ሌላው ቡድን ተሸንፎ እንዲወጣ የሚሠራ አይደለም። ሁሉም ወገን በጥሞና ተነጋግሮና ተደማምጦ ሁሉም ወገን በአሸናፊነት የሚወጣበት መድረክ መሆን አለበት ብዬ ነው የማስበው።
ሁሉም ወገን ሲያሸንፍ ኢትዮጵያ ታሸንፋለች። የኢትዮጵያ ችግር የልጆቿ አለመግባባት ነው። የልጆቿ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ያለመስማማት ነው። የልጆቿ በአንድነት ላይ አለመሥራት ነው። ስለዚህም ልጆቿ ተወያይተውና ተስማምተው ይህን ማድረግ ከጀመሩ ኢትዮጵያ አሸነፈች ማለት ነው። ከዚህ በተጨማሪ ኢትዮጵያ የምታሸንፈው ልጆቿ ከእንግዲህ ወዲህ በጠብመንጃ አፈሙዝ መፍትሔ ለማምጣት ማቀዳቸውን አቁመው ከዚህ በኋላ ለችግሮቻችን መፍትሔ መሆን የሚችለው ሰላማዊ በሆነ መንገድ ስንወያይ ነው ብለው በግልጽ መነጋገር ሲጀምሩ ነው። ኢትዮጵያ ካሸነፈች ደግሞ ሁላችንም አሸናፊ ሆንን ማለት ነው።
አዲስ ዘመን፡- በተባበሩት መንግሥታት ውስጥ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ነን ከሚሉት አካላት ጀምሮ አድራጊ ፈጣሪዋ አሜሪካ ጭምር የሰሜን ዕዝ ጀርባውን ከመወጋቱ አስቀድሞ በህዳሴ ግድቡ ላይ እንዲሁም መከላከያ ጥቃት ከደረሰበት በኋላም ባለው ሂደት በኢትዮጵያ ላይ እስካሁኗ ጊዜ የሚያደርሱት ጫና ቅጥ አላጣም?
አምባሳደር ጥሩነህ፡- አጥቷል እንጂ! የተመድ ሁኔታ እኔንም አስገርሞኛል። እኔ በነበርኩበት ጊዜ እንዲህ ዓይነት ሁኔታ አልገጠመኝም። ይህ ሁኔታ ለአንድ ወገን ያደላ ግልጽና ገሃድ የወጣ ነው። እኔ በነበርኩበት ወቅት እስከማወቀው ድረስ የሌሎችን አመራር ተቀብሎ ወደፊት ሂድ ሲባል የሚሄድ ዓይነት ድርጅት አልነበረም። ምክንያቱም የራሱ የሆነ አቋም የነበረው ድርጅት እንደነበረ ነው የማስታውሰው። የራሱ የሆነም አመለካከት ነበረው። ስለዚህም በወቅቱ አሁን ያለው አይነት አቋም ይዞ ማየቴን አላስታውስም። ተመድ በተለይም በእኛ በኢትዮጵያውያን ላይ እያደረገ ያለው መድልዎ ገዝፎ የታየበት ጊዜ ቢኖር አሁን ነው ማለት እችላለሁ።
ለምን ብትይኝ፤ እንደሚታወቀው ትልቁ ኃይል አሜሪካ ነው። በአሁኑ ወቅትም በእኛ ላይ ኃይላቸውን ያሠማሩት አሜሪካና ምዕራባውያን ናቸው። የአንበሳውን ድርሻ የያዘችው ግን አሜሪካ ስለመሆኗ እውን ነው። እና አሜሪካውያን በመሩትና ባሉት መንገድ ሄደው ነው አሜሪካውያኑ ያሉትን ሐሳብ ቃል በቃል እየደገሙ በእኛ ላይ ሲፈጽሙ የነበረው። ይህን እኔ በጭራሽ ያልጠበቅኩት ጉዳይ ሆኖ አግኝቼዋለሁ። እኔ በቆየሁባቸው ስምንትና ዘጠኝ ዓመት ውስጥ በእኔም ሃገር ሆነ በሌሎች ላይ ደርሶ አላየሁም፤ አልሰማሁምም።
እኔ በነበርኩበት ጊዜ ትልቁ ነገር የነበረው የኢራቅ ጦርነት ነው። በጸጥታው ምክር ቤት ክርክር በሚደረግበት ጊዜ ሃገሬን ይመለከታል በሚል ማመልከቻ ጽፌ ነበር ስከራከር የነበረው። ምክንያቱም ሃገሬ ትልቅ ሃገር ናት። ከዚህም በላይ ራሷ ብቻ እንደ አፍሪካም የምትታይ አገር ናት። ስለሆነም መከራከሬ በዚህ አይነት ጉዳይ ድምጽዋ መሰማት አለበት የሚል እምነት ስለነበረኝ ነው። በወቅቱ የነበረው መንግሥት ተው ይህን አታድርግ ብሎ ቢለኝም፤ እኔ ግን በጸጥታው ምክር ቤት ወንበር ይዤ እስከተቀመጥኩ ድረስ ከፈለጋችሁ አባርሩኝ በማለት ከማድረግ ወደኋላ አላልኩም። በዚያን ወቅት ታድያ እንዲህ ዓይነት ነገር ተፈጽሞ አለማየቴን ነው መናገር የምችለው።
እናም የእኛ ብቻ ሳይሆን በጸጥታው ምክር ቤትም ሆነ በተባበሩት መንግሥታት ጠቅላላ ጉባኤ ላይ አሜሪካ ኢራቅ ላይ ጦሯን በምታሠማራበት ጊዜ በወቅቱ በአሜሪካ ላይ የደረሰው ውግዘት ከፍ ያለ ነበር። ብዙ ትችትም ነበረ። ይህ ብቻ ሳይሆን የወቅቱ የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሐፊ የሆኑት ሚስተር ኮፊ አናን አፍሪካን በመልካም ሁኔታ እያስጠራ የሚኖር ትልቅ ሰው ነበር፤ በወቅቱም ያለው ነገር ቢኖር ‹‹ይህ ወረራ ነው። ከወረራም በላይ የሚወገዝ ወረራ ነው›› ሲል ነበር። ይህን በማለቱ ከአሜሪካ ምን ያህል በአመለካከት ርቆ መቆሙን ያሳያል። በአሁኑ ወቅት ያለው ግን የአሜሪካንን ድምጽ የሚያስተጋባው ቃል በቃል ነው። በኮፊ አናን ጊዜ የተባበሩት መንግሥታት በብዙ ክርክር የራሱን አቋም ይዞ ሲወጣ ነበር የማወቀው።
ሌላው ደግሞ አፍሪካውያኑ ራሳቸው ዝም ብለው ነበር። እኔ በማውቅበት ጊዜ የአፍሪካ ቡድን የሚባል ነገር አለ። በዚህ ቡድን ውስጥ ተሰባስበን እንወያያለን። በተለይ ደቡብ አፍሪካ፣ ጋና፣ ኢትዮጵያ እና ሌሎች አምስት ስድስት የሚሆኑ ሃገራት ተስማምተው ወደ ቡድኑ የሚያስተጋቡት ሐሳብና አመለካከት ቀጥታ የጸጥታውን ምክር ቤትንም ሆነ በጠቅላላው ጉባኤ ላይ ጎልቶ ይንጸባረቅ ነበር። ስለዚህ የጸጥታው ምክር ቤት አባልም ባንሆን የራሳችን የሆነ ተሰሚነት እንዲኖረን እናደርግ ነበር። በአሁኑ ወቅት በተቃራኒው አፍሪካውያኑ ዝም ሲሉ ሳይ በጣም ነው ያስደነገጠኝ። ምክንያቱም ይህ እኔ የማውቀው ተመድ ነው ወይ ሌላ የሚል አመለካከት ነበር የተመላለሰብኝ።
አዲስ ዘመን፡- የተመድም ሆነ የአሜሪካ ጫና በሚበዛበት ወቅት በሁሉም አገር ያሉ ኢትዮጵያውያና ትውልደ ኢትዮጵያውያኑ ‹‹በቃ›› የሚልና በሌላም ጉዳይ ላይ ታላቅ ንቅናቄ ማድረጋቸው የሚታወስ ነው፤ይህንን የዲያስፖራውን ንቅናቄ ያዩት እንዴት ነው? መቀጠል ያለበትስ በምን መልኩ ነው ይላሉ?
አምባሳደር ጥሩነህ፡- ፐብሊክ ዲፕሎማሲ ወይም ዲያስፖራው የያዘው አቅጣጫና ያሰማው ድምጽ ቀደም ሲል በማብራሪያዬ ተመድ እንዲህ ሆኖ አይቼ አላውቅም እንዳልኩት አይነት ነው የሆነብኝ። ቀደም ሲል የዲያስፖራው እንቅስቃሴ ቀዝቃዛ ከመሆኑም በላይ በተቃራኒውም ይቆም እንደነበር አስታውሳለሁ። በአሁኑ ወቅት ግን ዲያስፖራው ኢትዮጵያን ደግፎ በዚህ መልኩ በታላቅ እንቅስቃሴ ሲቆም ሳይ ይህ የመጀመሪያዬ ነው ማለት እችላለሁ። ይህ እንቅስቃሴ በከፍተኛ ደረጃ የሚደገፍ ከመሆኑም በተጨማሪ መቀጠልም ያለበት በጎ ተግባር ነው። ኢትዮጵያውያን አገር ወዳዶች ናቸው። ነገር ግን በዚህ መቆም የለብንም። እኛን የሚወድና ሊደገፈን የሚፈልግ ሕዝብ ብዙ ነው።
አዲስ ዘመን፡- ለምሳሌ እንዴት?
አምባሳደር ጥሩነህ፡- ጥሩ ጥያቄ! ለምሳሌ አሜሪካ ያለው ጥቁር ኢትዮጵያን የሚያየው በልዩ ሁኔታ ነው። ከዚህም የተነሳ ኢትዮጵያን ለመቅረብ ይፈልጋል። ከኢትዮጵያ ጋር ኅብረት ፈጥሮ ለመሥራት ይፈልጋል። እኛ ግን ለዚህ ነገር በጎ ምላሽ ስንሰጥ አንታይም።
አዲስ ዘመን፡- ለዚህ ምክንያቱ ምን ይሆን?
አምባሳደር ጥሩነህ፡- የእውቀት አለመኖር ነው፤ ራስንም ልዩ አድርጎ የማየትም ሁኔታ ነው የሚታየው። ይህ ደግሞ አይጠቅመንም። ምክንያቱም እኛ እንደምናስበው አይደለንም። መምራት የምንፈልገው አፍሪካን ነው። አውራ መሆን የምንፈልገውም በአፍሪካዊነት ነው። የእስራኤል አውራ መሆን አንችልም። ስለዚህም እስራኤላዊ መሆንን እየተመኘን የአፍሪካ አውራ መሆን አንችልም። እኔ አፍሪካዊ አይደለሁም እያልኩ አፍሪካን መምራት አልችልም። ይህ አለማወቅ ነው። በዚህ ዙሪያ ግንዛቤ ስለሌለን አርቆ ማሰብ ተስኖናል።
በነገራችን ላይ እኛ ኢትዮጵያውያን ነን የሚሉ በርካታ የአፍሪካ አገራት አሉ። እኛ ኢትዮጵያውያን ራሳችንን እስራኤላውያን ነን ስንል ጥቂት የማይባሉ ቀሪዎቹ አፍሪካውያን ግን እኛ ኢትዮጵያውያን ነን ይላሉ። እኛ ኢትዮጵያውያን ነን ከሚሉት መካከል እነማሊ፣ ቡሩንዲ፣ ሩዋንዳ፣ ተጠቃሽ ናቸው። እነዚህን እንኳ ለማቅረብ አልሞከርንም። ይህ በራሱ ብናውቅበት ኃይል ነበር። ኢትዮጵያ ብዙ እድል እያላት መጠቀም አልቻለችም።
አዲስ ዘመን፡- በአሁኑ ወቅት አሸባሪው ቡድን የጦርነት ነጋሪት እየጎሰመ ስለመሆኑ በተለያየ ሁኔታ ሲነገር ይደመጣልና እዚህ ላይ የሚሉት ነገር ካለ?
አምባሳደር ጥሩነህ፡- እኔ እግዚአብሄር ልብ ይስጣቸው ነው የምለው። ይህ ነገር ሕዝብን ከማስጨረስ ውጪ የሚያዋጣ አይደለም። አካባቢውን የበለጠ መጉዳት ነው። ሕወሓት በዚህ አካሄዱ ከቀጠለ የበለጠ የሚጎዳው የትግራይ ሕዝብና አካባቢው ነው።
ሕዝቡ እኔን ይሰማኛል፤ ይከተለኛልም በማለት በሕዝቡ ላይ ያልተገባ ነገር መጫን ጥሩ አይደለም፤ ይህ ወንጀል ነው። ለሕዝቡ ማዘን አለባቸው። የኢትዮጵያ መንግሥት ለሕወሓት የዘረጋው የሰላም እጅ አለ። ኢትዮጵያ የዘረጋችው የሰላም እጅ እንዳይታጠፍ የኢትዮጵያን መንግሥትንም ሆነ ሕዝቡን እለምናለሁ። ጊዜም ቢወስድ ኢትዮጵያ የዘረጋችው የሰላም እጅ ተቀባይነት እስኪያገኝ እንደተዘረጋ ቢቆይ እመርጣሁ። ሕወሓትም ልብ እንዲልና የተዘረጋውን የሰላም እጅ ተቀብሎ ለኢትዮጵያውያን ሁሉ ሰላምና ብልጽግና አብሮነቱን ቢያሳይ እመርጣለሁ። ለዚህም ስኬት እጸልያለሁም።
አዲስ ዘመን፡- የሁልጊዜ ተባባሪያችን አምባሳደር ከልብ አመሰግናለሁ።
አምባሳደር ጥሩነህ፡- እኔም በጣም አመሰግናለሁ።
አስቴር አልያስ
አዲስ ዘመን ግንቦት 17/2014