በፍቃድ ሀብቴ በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ በተለምዶ ሰባተኛ ተብሎ በሚጠራ አካባቢ በአንድ የምግብ ቤት ውስጥ በመስተንግዶ ሥራ ተቀጥሮ ይሰራል። ተወልዶ ያደገው በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ፓዊ ወረዳ ሲሆን፤ በ2008 ዓ.ም ከአክሱም ዩንቨርሲቲ በሎጂስቲክስና ሰፕላይ ቼይን ማኔጅመንት የመጀመሪያ ዲግሪ ማግኘቱን ይናገራል።
እንደ በፍቃድ ንግግር፤ ወላጆቹ ለጣና በለስ የስኳር ፕሮጀክት ከቀዬያቸው ተነስተዋል። ወላጆቹ ቀዬያቸውን ለቀው ሲነሱ ልጆቻቸው ተመርቀው ሲወጡ በፋብሪካው ውስጥ ገብተው እንዲሰሩ ቃል የተገባ ቢሆንም ‹‹ፋብሪካው ቃሉን ባለማክበሩ እኔን ጨምሮ በርካቶች ለችግር እና ለእንግልት ተዳርገናል›› ይላል። ከጓደኞቹ ጋር በመሆን በተመረቀበት የሥራ መስክ ሥራ ቢያፈላልግም ማግኘት ባለመቻሉ ለተወሰኑ ወራት የጥበቃ ሥራ ሲሰራ ቆይቷል።
የጥበቃ ሥራው በመጠናቀቁ አሁን ወደሚሰራበት የመስተንግዶ ሥራ ተዛውሯል። ‹‹አዲስ አበባ ሥራ ተቀጥሬ ችግር ውስጥ ያሉትን ቤተሰቦቼን ለመርዳት እቅድ ነበረኝ›› የሚለው ወጣቱ አሁን ግን ሥራ ላገኝ ባለመቻሌ ቤተሰቤን መርዳት ቀርቶ ራሴም ችግር ውስጥ ነኝ ብሏል።
የፕሮጀክቱ ግንባታ በተጀመረበት ወቅት በሰርተፍኬት ከተቀጠሩት በጣት የሚቆጠሩ የልማት ተነሺ ቤተሰብ ልጆች ውጪ የአካባቢው ልጆች ተቀጥረው አያውቁም ያለው ወጣት በፍቃድ፤ የልማት ተነሺዎች ተወዳድረው እንኳ እንዳይቀጠሩ ክፍት የስራ ቦታ ማስታወቂያዎች የት እንደሚወጡ ራሱ ግልጽ አይደለም ሲል ግልጸኝነት የጎደለው አሰራር መኖሩንም ያነሳል። ሆኖም ግን ከሌሎች የሀገሪቱ አካባቢዎች የመጡ ሠራተኞች በየጊዜው እንደሚቀጠሩ ያነሳል።
እንደ በፍቃድ ማብራሪያ፤ የመጀመሪያ የፋብሪካ ግንባታ ሲጀመር ለሀገሩ፣ ለቤተሰቡና ለራሱ ትልቅ እድል ይዞ ይመጣል የሚል ተስፋ ስለነበራቸው ተገቢውን ካሳ፣ ምትክ መሬትና የንብረት ግምት ሳያገኙ ከቀዬያቸው ተነስተዋል።በአሁኑ ወቅት ግን በተመረቀበት የዲግሪ መደብ እንኳ ቀርቶ ሰርተፍኬት በሚጠይቁ መደቦች ላይ ተቀጥሮ የመስራት ፍላጎት ቢኖረውም ፋብሪካው ምንም አይነት እድል ለመስጠት ፈቃደኛ አልሆነም። በዚህም ምክንያት ቤተሰቦቹ ችግር ውስጥ መውደቃቸውና ለምሩቃን የተገባው ቃል ገቢራዊ ሆኖ ባለማግኘቱ በጣም ተቆጭቷል።
በፓዊ ወረዳ ክስቶን ቀበሌ ነዋሪዋ ወይዘሪት ገነት ዳዊት በበኩሏ እንደገለጸችው፤ በ2008 ዓ.ም ከኮሌጅ በሰርቬይንግ በዲፕሎማ ተመርቃለች። ወላጆቿ ለጣና በለስ ፕሮጀክት ከቀዬያቸው ሲነሱ ልጆቻቸው ትምህርታቸውን ሲያጠናቅቁ ፋብሪካው ውስጥ ተቀጥረው ይሰራሉ የሚል ቃል ተገብቶላቸው ነበር። አሁን ግን ከተገባው ቃል አንጻር የተገላቢጦሽ እየሆነ ነው። በተመረቀችበት ሰርቬይንግ ሳይሆን በጽዳት ወይም በጥበቃ ሥራ ለመሰማራት ፍላጎት ቢኖራትም ሊሳካ አልቻለም።
ፋብሪካው ለልማት ተነሺዎች የገባውን ቃል በማጠፍ ከሌሎች ክልሎችና ዞኖች የሰው ሀይል በገፍ እየቀጠረ ቢሆንም ለልማት ተነሺዎች ልጆች የገባውን ቃል ለመፈጸም ፈቃደኛ አለመሆኑ አሳዛኝ ነው ትላለች። እያጋጠማቸው ያለውን ችግር ከሌሎች ጓደኞቿ ጋር በመሆን ለወረዳውና ለክልል መንግሥት ቢያሳውቁም እስካሁን ምላሽ የሚሰጥ አካል እንዳልተገኘ ትገልጻለች። እንደ ገነት ማብራሪያ፤ የልማት ተነሺዎች ልጆች ድጋፍ ሊደረግላቸው ይገባል። ምክንያቱም የልማት ተነሺዎች ለሀገር ብለው የተሻለ ኑሯቸውን ለቀው በመነሳታቸው ልጆቻቸውን ለመርዳት አቅም ያንሳቸዋል።
ቤተሰብ አቅም ስለሌለው ልጆች ወደ አላስፈላጊ ነገር እንዲገቡ እያዩ ከማየት ምንም አማራጭ የላቸውም። በመሆኑም መንግሥት ትኩረት ሊሰጥ ይገባል። የፓዊ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ብርሃኑ አሰፋ እንዳመለከቱት ለጣና በለስ የስኳር ፕሮጀክት የተነሱ የልማት ተነሺዎች በሰፈሩባቸው ቀበሌዎች ውስጥ ምን ያህል ምሩቃን እንዳለ ልየታ ተደርጓል።
በሦስቱ ቀበሌዎች ከ50 በላይ ዲግሪና ዲፕሎማ የተመረቁ ሥራ አጥ ወጣቶች መኖራቸውን ለማረጋገጥ ተችሏል። የጣና በለስ ስኳር ፕሮጀክት የሰው ሃብት ሥራ አመራር ዘርፍ ምክትል ሥራ አስኪያጅ አቶ ሄኖክ በለጠ በበኩላቸው፤ ወጣቶቹ በሚያነሱት ቅሬታ አይስማሙም። ፋብሪካው ከሚነካቸው ከሦስት ወረዳዎች የተነሱ የልማት ተነሺዎች የተቀመጠላቸው ኮታ አለ። ኮታዎቹ በአብዛኛው ጽዳትና የጥበቃ ሥራ ላይ ነው። በነዚያ ኮታዎች እንዲቀጠሩ ተደርገዋል። ፋብሪካው ከሚነካቸው ከፓዊ፣ ጃዌና ዳንጉር ወረዳዎች 476 የሚሆኑ ቋሚ ሠራተኞች ከዚህ በፊት ተቀጥረዋል።
ከዚያ በተጨማሪ የኦፕሬተርነት ስልጠና ተሰጥቷቸው የተቀጠሩ አሉ። ሙያ በሚፈልጉ የሥራ ዘርፎች ላይ በኮታ ለመቅጠር አስቸጋሪ በመሆኑ ማስታውቂያ ወጥቶ ሠራተኞች እንዲቀጠሩ ተደርጓል የሚሉት አቶ ሄኖክ በተለያዩ የኢንጂነሪንግ ትምህርቶች የተመረቁ ተማሪዎች በወጣው ማስታውቂያ ተወዳድረው ተቀጥረው ከፍ ያለ ቦታ ላይ የሚሰሩም አሉ ይላሉ። የፋብሪካው ግንባታ ሲጠናቀቅ ለብዙ ሺህ ወጣቶ ሥራ እድል ይፈጥራል ያሉት አቶ ሄኖክ፤ የፋብሪካው ግንባታ ሲጠናቀቅም ለልማት ተነሺዎች በተፈቀዱ ቦታዎች ላይ በኮታ የመቅጠር ስራው ያለ አድልኦ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። ሙያ በሚፈልጉ ዘርፎች ላይ ግን እንደከዚህ ቀደሙ ፋብሪካው ከመላ ሀገሪቱ ሠራተኞችን አወዳድሮ መቅጠሩን ይገፋበታል ብለዋል። በስኳር ኮርፖሬሽን ኮርፖሬት ኮሙዩኒኬሽን ሥራ አስፈጸሚ አቶ ጋሻው አይችሉህም እንደገለፁት የመንግሥት የልማት ድርጅት የሆነው የስኳር ኮርፖሬሽን ቀርቶ የግል ኩባንያዎች እንኳ ለልማት ተነሺዎች ቅድሚያ የመስጠት ማህበራዊ ሀላፊነት አለባቸው።
እንደየትምህርት ዝግጅታቸውና እንደየአቅማቸው ከከፍተኛ እስከ ዝቅተኛ ደረጃ የአካባቢውን ነዋሪዎች የመቅጠር ማህበራዊ ሀላፊነት አለባቸው። ስኳር ኮርፖሬሽን በሚያለማቸው በሁሉም ፕሮጀክቶች ዙሪያ ላሉ ነዋሪዎች በተለይም ለስኳር ልማት ተነሺዎች ቅድሚያ የሚሰጥበት አሰራር አለው። ይህንኑ አሰራር ተከትሎ የስኳር ልማት ፕሮጀክቶች ባሉባቸው አካባቢዎች ላሉ ማህበረሰቦች ቅድሚያ ሰጥቶ እንዲቀጠሩ እያደረገ ይገኛል። ይህ ማለት ግን ከሌላው የሀገሪቱ ክፍል ሄዶ ስኳር ልማት ፕሮጀክቶች ባሉበት ቦታ አይሰሩም ማለት አይደለም የሚሉት አቶ ጋሻው፤ ከየትኛውም የሀገሪቱ ክፍል የሚመጡ ዜጎች የስኳር ፕሮጀክቶች ውስጥ የመስራት መብት አላቸው፤ እየሰሩም ናቸው ይላሉ።
ለልማት ተነሺዎች ቅድሚያ መሰጠቱ ለልማት ተነሺዎቹ ብቻም ሳይሆን ለኮርፖሬሽኑም ጭምር እጅግ ጠቃሚ ነው። ምክንያቱም የስኳር ልማት ፕሮጀክቶች በርካታ የሰው ሀይል የሚጠይቁ በመሆናቸው ከሌላው የሀገሪቱ አካባቢዎች ሰራተኞችን ከማጓጓዝ ይልቅ የልማት ተነሺዎች ተቀጥረው የሚሰሩበት ሁኔታ በማመቻቸት ፋብሪካው ይጠቀማል እንጂ አይጎዳም ይላሉ።
በአንዳንድ አካባቢዎች ቀጥታ በፕሮጀክቶች ውስጥ ተቀጥረው ባይሰሩ እንኳ ስኳር ኮርፖሬሽኑ አደራጅቷቸው የተለያዩ ስራዎችን እየሰሩ ነው የሚሉት አቶ ጋሻው፤ ጣና በለስ ግን በጣም የተጓተተ በመሆኑ የተቀጠሩትም ያለ ሥራ ደመወዝ እየተከፈላቸው በመሆኑ የሰው ሀይል በብዛት ለመቅጠር አልተቻለም ይላሉ። የፋብሪካው ግንባታ ለማፋጠን እየተሰራ ነው። ፋብሪካው ወደ ሥራ በሚገባበት ወቅት በርካታ የጣና በለስ የስኳር ልማት ተነሺዎች ልጆች የሥራ እድል ተጠቃሚ እንዲሆኑ ይደረጋል ብለዋል።
አዲስ ዘመን መጋቢት 12/2011
መላኩ ኤሮሴ