ባገኘሁት አጋጣሚ ሁሉ የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የመማሪያ መጻሕፍትን ከተማሪዎች እየተቀበልኩ አያለሁ። በተለይም የአንደኛ ደረጃ (እስከ 8ኛ ክፍል) ሳይንስ በአማርኛ የተማርኩባቸው የሳይንስ ቃላት ይታሰቡኛል። ለሳይንስ ትምህርቱ ሲባል የተፈጠሩ የአማርኛ ቃላት ይስቡኛል።
ባለፈው ሐሙስ ከሰዓት የሆነ የቴሌቪዥን ጣቢያን ለማግኘት ቻናል እያቀያየርኩ ነበር፤ በአጋጣሚም በአንድ የቴሌቪዥን ጣቢያ ትምህርት በቴሌቪዥን ሲተላለፍ አገኘሁ። በቴሌቪዥኑ የሳይንስ ትምህርት በአማርኛ ቋንቋ እየተላለፈ ነበር፤ ሪሞቱን አስቀምጬእየተሰራጨ ያለውን ትምህርት መከታተል ጀመርኩ። ለካስ ሊያልቅ አካባቢ ነበርና የደረስኩበት ትምህርቱ የሳይንስ መሆኑን እንጂ የትኛው የሳይንስ ትምህርት ዓይነት እና የስንተኛ ክፍል እንደሆነ አላየሁም። ከማስታውሳቸው የሳይንስ ቃላትና ጽንሰ ሀሳቦች ተነስቼም የ7ኛ ክፍል ፊዚክስ ነው ስል ገመትኩ።
በትምህርቱ ውስጥ ከአሥራ ምናምን ዓመታት በፊት የማውቃቸውን የአማርኛ የሳይንስ ቃላት ስሰማ አዘጋጆቹን አመሰገንኳቸው። ምክንያቱም በአንደኛ ደረጃ መማሪያ መጻሕፍት ላይ በአንዳንድ የሳይንስ ትምህርቶች የሳይንስ የእንግሊዝኛ ቃላት በአፍ መፍቻ ቋንቋ ተተርጉመው ይሠራባቸው የነበረበት ሁኔታ ቀረ ወይ የሚያሰኝ ሁኔታን እንድታዘብ አረገኝ።
በሃገራችንም ይህን አሠራር ክልሎች በተለያየ መልኩ እየተገበሩት ይገኛሉ። በኦሮሚያ ክልል እስከ 8ኛ ክፍል ትምህርት የሚሰጠው በአፍ መፍቻ ቋንቋ እንደነበር አውቃለሁ (አሁን የተቀየረ ነገር ከሌለ)፤ በአማራ ክልልና አዲስ አበባ ግን 7ኛና 8ኛ ክፍል ላይ ትምህርት የሚሰጠው በእንግሊዘኛ ነው። አማራ ክልል የ7ኛ እና 8ኛ ክፍል ትምህርት መስጫው ወደ አፍ መፍቻ ይመለሳል ሲባል ነበር። ለማንኛውም የክልሎች የትምህርት ፖሊሲ ምን ላይ እንዳለ ለጊዜው ሙሉ መረጃ ስለሚፈልግ እሱን እንለፈው። ዋናው ነገር ተማሪዎች በአፍ መፍቻ ቋንቋ እንዲማሩ መደረጉ መሰጠት እንዳለበትይታመናል፤ ትክክልም ነው።
ከአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ከወጣሁ ጊዜ ጀምሮ የሚቀየሩ የመማሪያ መጻሕፍትን ከተማሪዎች እየተቀበልኩ አያለሁ። 2008 ይሁን 2009 አካባቢ በዚህ ጉዳይ ላይ ትዝብት መጻፌን አስታውሳለሁ። የ4ኛ፣ 5ኛና 6ኛ ክፍል የሳይንስ መማሪያ መጽሐፎችን ከልጆች ላይ እየተቀበልኩ ሳይ እነዚያ እኔ የተማርኩባቸው ቃላት የሉም። ይህ የሆነው እንግዲህ የአፍ መፍቻ ቋንቋቸው አማርኛ ለሆኑ ተማሪዎች ነው።
የመማሪያ መጽሐፉ ለስሙ በአማርኛ ነው የተዘጋጀው። የሳይንስ ቃላቱን ለተመለከተ ግን የተጻፈበት ፊደል ነው እንጂ አማርኛ፤ ቃላቱ የእንግሊዘኛ ናቸው። ቀደም ሲል በነበረው ግን በአማርኛ ቃላት ይጻፍና አንዳንድ ቦታ ላይ እንግሊዝኛው በቅንፍ ውስጥ ይሆናል። ይህ ሲሆን የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች የእንግሊዘኛ አቻውን እያወቁት ይሄዳሉ ማለት ነው። በመማሪያ መጽሐፉ ጀርባ ደግሞ ሙዳዬ ቃላት(Glossary) ተብሎ ይቀመጣል። ሙዳዬ ቃላቱ መዝገበ ቃላት ማለት ነው። የአማርኛ ቃላትን በእንግሊዝኛ የሚፈታ። እንግሊዝኛውንም በዚያ ነበር የምናውቀው። እንደ መምህራኑ ብቃት ደግሞ በአማርኛ እያስተማሩ የእንግሊዘኛ ቃላቱንም ያለማምዱን ነበር።
አሁን እየታዘብኩ ያለሁት ግን በአማርኛ ፊደል የእንግሊዝኛው ቃል /በላቲን ፊደል ደግሞ የእንግሊዝኛው ቃል/ እየተጻፈ ያለበትን ሁኔታ ነው። ለምሳሌ የምግብ ሥርዓተ ልመት (digestive system) መባል የነበረበት ‹‹ዳይጄስቲቭ ሲስተም( digestive system)›› ተብሎ ይጻፋል። ይህ አገላለጽ ቦታ ከማባከን ውጭ ምንም ጥቅም የለውም ማለት ነው።
የትምህርት ጥራት ጉዳይ በየጊዜው ሲነሳ የቆየ ቢሆንም፣ የመማሪያ መጻሕፍት የሚጻፉበት ቋንቋ ጉዳይ ሆኖ ሲያከራክር ብዙም አይታይም፤ አልፎ አልፎ ብቻ በባህልና ስፖርት (በቀድሞው ባህልና ቱሪዝም) ሚኒስቴር ‹‹የአፍ መፍቻ ቋንቋ›› እየተባለ ውይይቶች ይደረጋሉ።
በአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የሳይንስ ትምህርት በአፍ መፍቻ ቋንቋ አለመሆኑ ከፍተኛ ጉዳት እንዳለው ይታመናል። ታችኛው የክፍል ደረጃ ላይ ደግሞ ሳይንሱ የአካባቢ ሳይንስ በሚል ነው የሚሰጠው። ሳይንስ ተፈጥሮ ነው፤ ተፈጥሮን ማወቅ የምንጀምረው ከአካባቢያችን ተነስተን ነው፤ አካባቢያችንን የምናውቀው ደግሞ በቋንቋ ነው። በአካባቢያችን ያሉ ነገሮችን አሳምሮ የሚገልጻቸው እነዚያ ተፈጥሮዎች የሚጠሩበት የአካባቢው ቋንቋ ነው። ሕጻናት የተክልና፣ የእንስሳት አይነቶችን፣ የተለያዩ የተፈጥሮ ሀብቶችን የሚያውቁት ከአካባቢያቸው ነው፤ የሚያውቁት ደግሞ በአካባቢያቸው በሚነገረው ቋንቋ ነው።
በአማርኛ የማውቃቸው የሳይንስ ቃላት ጽንሰ ሀሳቡ እንዲገባኝ ያደርጉኛል። መጀመሪያ በአማርኛ ካወቅኳቸው በኋላ ነው እንግሊዝኛው የሚገባኝ። አለበለዚያ መሸምደድ ብቻ ነው የሚሆነው። የአማርኛውን ቃል ከቤተሰብ ጀምሮ በአካባቢዬ ሲነገር አውቀዋለሁ፤ እንግሊዘኛውን ግን ያየሁት መማሪያ መጽሐፉ ላይ ብቻ ነው፤ ስለዚህ ድርጊት ገላጭ አይሆንም። ጽንሰ ሀሳቡ ገላጭ የሚሆነው እንግሊዘኛን በአፍ መፍቻነት ጭምር ካወቁት ወይም ማኅበራዊ እንቅስቃሴዎች በእንግሊዘኛ ከሆኑ ነው። የእሳት ዳር ጨዋታዎች ሁሉ በእንግሊዘኛ ከሆኑ ነው።
የሳይንስ ቃላት በአፍ መፍቻ ቋንቋ መገለጻቸው የዚያን ቃል ትርጉም በቀላሉ ለማወቅ ያግዛል። ለምሳሌ፤ በሳይንሱ ደም መላሽ እና ደም ወሳጅ የሚባሉ የደም ቧንቧ አይነቶች አሉ። ወሳጅ የሚለውም ሆነ መላሽ የሚለው ቃል ምንን እንደሚገልጽ አፉን በአማርኛ የፈታ ለመረዳት ብዙም አይቸገርም፤ ለማስረዳትም አያስቸግርም። ከቃሉ ጋር ከሕጻንነቱ ጀምሮ ተላምዷል። ስለዚህ ‹‹ደምን ከልብ ወደ ተለያዩ የሰውነት ክፍሎች የሚወስድ የደም ቧንቧ ምን ይባላል?›› ተብሎ ቢጠየቅ፤ ‹‹ወሳጅ›› የሚለው ቃል ድርጊቱን ስለሚገልጽ ‹‹ደም ወሳጅ›› ብሎ ይመልሳል ማለት ነው።
‹‹የሰውነት ሕዋሳት ተጠቅመውበት የቆሸሸውን ደም ወደ ልብ የሚመልስ የደም ቧንቧ ምን ይባላል?›› ቢባል ‹‹መላሽ›› የሚለው ቃል ድርጊቱን ስለሚገልጽ ‹‹ደም መላሽ›› ብሎ ይመልሳል ማለት ነው። Arteries እና Veins የሚሉት የእንግሊዘኛ ቃላት ግን ለ4ኛና 5ኛ ክፍል ተማሪ የአማርኛውን ያህል ሊገልጹለት አይችሉም። ጽንሰ ሀሳቡን ሳይሆን የሚይዘው ለሽምደዳ ነው የሚታገል።
ለዚህ ሀሳብ መነሻ የሆነኝ ከፍ ብዬ እንደጠቀስኩት በሃገራችን አንድ የቴሌቪዥን ጣቢያ ሲተላለፍ በነበረ የትምህርት በቴሌቪዥን ስርጭት የተመለከትኳቸው የሳይንስ ትምህርት የአማርኛ ቃላት ናቸው። በትምህርቱ ውስጥ ‹‹ፅብረቃ፣ የብርሃን ሀመልማሎ…›› የሚሉ ቃላት አሉ። እነዚህ ቃላት ትርጉምን መግለጽ ብቻ ሳይሆን ስነ ጽሑፋዊ ውበትም አላቸው። ማንፀባረቅ ከሚለው ቃል ጽብረቃ የሚል ድርጊት አመልካች ቃል ይፈጠራል ማለት ነው። ሂደቱ ጽብረቃ ይባላል። በተለይ የስነ ሕይወት (ባዮሎጂ) ቃላት በአፍ መፍቻ ሲሆኑ ደግሞ የበለጠ ገላጭ ይሆናሉና ተማሪዎች ጽንሰ ሀሳብን ይይዙ ዘንድ ፋይዳቸው ከፍተኛ ነው።
የተፈጥሮ ሳይንስን ብቻ አይደለም፤ የማኅበራዊ ሳይንስም በአፍ መፍቻ ሲሆን ተማሪዎች ታሪክ፣ ስነ ዜጋና ስነ ምግባር በቀላሉ እንዲገባቸው ያደርጋል። የታሪክ እና የስነ ዜጋ ይዘቶች በተዘዋዋሪ በቤት ውስጥም የሚወሩ እንደመሆናቸው ቃላቱ በአፍ መፍቻ ቋንቋ መገለጻቸው በሕይወት ገጠመኝ ውስጥ የሚያውቁትን መደበኛው ትምህርት ውስጥ እንዲያገኙት ለማድረግ ያስችላሉ።
ስለትምህርት ጥራት ሲታሰብ የአፍ መፍቻ ቋንቋ ነገርም ተያይዞ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል። የመማሪያ መጻሕፍት በተገቢው ቋንቋ ባይጽፉ እንኳን መምህራን ግልጽ አድርገው ማስተማር አለባቸው። በዚህ በኩል ከመማሪያ መጻሕፍቱ ይልቅ በሬዲዮና በቴሌቪዥን ትምህርቶች የተሻለ ሁኔታ ይታያል።
አንደኛ ደረጃ ላይ ትምህርት በአፍ መፍቻ ቋንቋ መሰጠት ያለበት መሆኑ ታምኖበት እየተሠራበት እንደመሆኑ ሁሉ፣ ለአንደኛ ደረጃ ተማሪዎች የሚዘጋጁት የመማሪያ መጻሕፍትም በሚገባ ቋንቋ መጻፍ አለባቸው፤ መጻሕፍቱ ላይ ክፍተት ካለ ደግሞ የሚመለከታቸው አካላት መሙላትና ማሻሻል ላይ ትኩረት አርገው መሥራት ይኖርባቸዋል፤ ይህ እስኪሆን ደግሞ መምህራን በማስተማር ዘዴ ተማሪዎቹን በመርዳት ሊያሳውቁ ይገባል!
ዋለልኝ አየለ
አዲስ ዘመን ግንቦት 3 /2014