ከአጠቃላይ የዓለም ህዝብ 15 በመቶ የሚሆኑት አካል ጉዳተኞች መሆናቸውን ዓለም አቀፉ የጤና ድርጅት ሪፖርት ይጠቁማል። አደጋ በየትኛው አጋጣሚ ሊከሰት ይችላል፡፡ በዚህ ምክንያትም አካል ጉዳተኝነት ይከሰታል። የጉዳቱ ዓይነትና መጠን የተለያየ ቢሆንም ግን በየትኛውም እንቅስቃሴ ተሳትፈው ጉዳት ካልደረሰበት ሰው እኩል ነገሮችን ማከናወን የሚችሉ አሉ።
ይህ ከሚረጋገጥባቸው መንገዶች መካከል አንዱ ደግሞ ስፖርታዊ እንቅስቃሴና ተሳትፎ ነው። ይኸው ስፖርት በባለሙያዎች ዘንድም ለአካል ጉዳት የተዳረጉ ሰዎችን ጥንካሬ ለመመለስ ሁነኛ መፍትሄ ሆኖም ይጠቀሳል። ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ እያደገ የመጣው ይህ የአካል ጉዳተኞች ስፖርትም እስከ ኦሊምፒክ የሚዘልቅ የውድድር መድረክ አለው። «ፓራሊምፒክ» በሚል ስያሜ የሚታወቅው ስፖርቱ እንደ ኢትዮጵያ ባሉ አገራት ያለው ተዘውታሪነት አናሳ ቢሆንም እንቅስቃሴዎች መኖራቸው አልቀረም።
በየዓመቱ በታህሳስ ወር መጀመሪያ የሚከበረውን የዓለም አካል ጉዳተኞች ቀንን አስመልክቶም በኢትዮጵያ የዊልቸር ቅርጫት ኳስ ውድድር ይካሄዳል። በዚህ ዓመትም ለአራተኛ ጊዜ በአዲስ አበባ ትንሿ ስታዲየም ውድድሩ በመካሄድ ላይ ይገኛል። ውድድሩ በኢትዮጵያ ፓራሊምፒክ ኮሚቴ፣ ቅርጫት ኳስ ፌዴሬሽንና በኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማህበር አዘጋጅነት እየተካሄደ ይገኛል። ከትናንት በስቲያ በተጀመረው የዊልቸር ቅርጫት ኳስ ውድድር ላይም በወንድ ስድስት፤ በሴት ደግሞ አራት ክልሎች በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ።
ድሬዳዋና አዲስ አበባ ከተሞች አስተዳደር እንዲሁም የደቡብ፣ የአማራ፣ የኦሮሚያና የትግራይ ክልሎች በወንዶች ምድብ ተሳታፊ በመሆን ላይ ይገኛሉ፡፡ ድሬዳዋ፣ አዲስ አበባ፣ አማራ እና የኦሮሚያ ክልሎች ደግሞ በሴቶች በኩል ተካፋይ የሆኑ ቡድኖች ናቸው። ፌዴሬሽኑ በቀጣዩ ዓመት በዊልቸር ቅርጫት ኳስ ስፖርት የምስራቅ አፍሪካ የዊልቸር ቅርጫት ኳስ ሻምፒዮና ለማዘጋጀት ታቅዷል፡፡ ከዚህ ውድድር ብሄራዊ ቡድኑን ሊወክሉ የሚችሉ ተጫዋቾች የሚለዩ መሆኑን የፌዴሬሽኑ ከፍተኛ ባለሙያ አቶ ታሪኩ እንዳለው ይገልጻሉ።
ዛሬ ሶስተኛ ቀኑን ባስቆጠረው ውድድር ከዚህ ቀደም ከነበረው በተሻለ መልኩ የተወዳዳሪዎች አቅም እየዳበረ መምጣቱን ለመመልከት መቻሉን ባለሙያው ይጠቁማሉ። የተሳታፊዎች ቁጥርም ካለፉት ውድድሮች ጭማሪ ሊያሳይ ችሏል። በስድስት አካባቢዎች በእነዚህ ስፖርቶች የስልጠና ጣቢያዎች ያሉ ሲሆን፤ ዓመቱን ሙሉ በአሰልጣኞች ታግዘው ስልጠናቸውን በመከታተል ላይም ይገኛሉ። ይህ ውድድር ከመካሄዱ በፊትም ለ13ቀናት የቆየ ስልጠና፤ በአሰልጣኝነት፣ በዳኝነትና ጉዳትን በመለየት ዘርፍ በዓለም አቀፍ ባለሙያዎች ሲሰጥ መቆየቱንም ያስታውሳሉ።
በየክልሉ የሚገኙት የማሰልጠኛ ጣቢያዎች በኢትዮጵያ ቅርጫት ኳስ ፌዴሬሽን ክትትልና ድጋፍ ይደረግላቸዋል። ፌዴሬሽኑ ከቀይ መስቀል ማህበር ጋር በመሆንም የዊልቸርና የኳስ ድጋፍ ያደርጋል፡፡ እንዲሁም ባለሙያዎችንም በማሰልጠን ኃላፊነቱን በመወጣት ላይ ይገኛል። በተለይ የአማራ እና ኦሮሚያ ክልሎች ባላቸው የማሰልጠን አቅም የተሻሉ በመሆናቸው በውድድሩ ላይም ጠንካራ አቅማቸውን አሳይተዋል። ነገር ግን በአንዳንድ ክልሎች ላይ ስፖርቱ በፓራሊምፒክ፤ በሌሎች ክልሎች ደግሞ በፌዴሬሽኖች ይመራል።
በመሆኑም በዚህ ወቅት ከፓራሊምፒክ ኮሚቴ ጋር በጋራ በመሆን እየተሰራ ነው። ነገር ግን ስፖርቱ ራሱን የቻለ ማህበር ለመሆን የሚያስችለውን ቅድመ ሁኔታ በማጠናቀቁ የዊልቸር ቅርጫት ኳስ ማህበር ለመመስረት በሂደት ላይ እንደሚገኝም ነው ባለሙያው የሚያስረዱት። በቅርቡም ራሱን ችሎ በመውጣት የሚቀጥለው ዓመት የሚካሄደውን ውድድር በራሱ አቅም ያካሂዳል ተብሎም ይጠበቃል።
በኢትዮጵያ ፓራሊምፒክ ኮሚቴ የቴክኒክ ኃላፊ አቶ ዮናስ ገብረማርያም፤ ከአምናው ይልቅ የተሻለ የቡድኖች ተሳትፎ በውድድሩ መታየቱን ይገልጻሉ። ከተወዳዳሪዎች ቁጥር ባሻገር ብቃታቸውም በዚያው ልክ ለውጥ የታየበት ሲሆን፤ ለዚህም የተሻለ ስልጠና መሰጠቱ አስተዋጽኦ አድርጓል ። ከዚህ ባሻገር አመቱን ሙሉ በዚህ ላይ የተሻለ ስራ በማከናወን ላይ የሚገኙት የኦሮሚያና የአማራ ክልሎች የበላይነትም ሊስተዋል መቻሉንም ኃላፊው ያነሳሉ።
እንዲህ ዓይነት ስፖርቶች እንዲሁም ስልጠናዎች ለአገሪቷ አዲስ በመሆኑ በየክልሉ ያለው አቅም ጎልብቷል ለማለት አያስችልም። ለአብነት ያህል በኦሮሚያ ክልል በአዳማ እና አሰላ ከተሞች፣ በአማራ ክልል በባህርዳር፤ በትግራይ ክልል በመቀሌ፣ ደቡብ ወልቂጤ እንዲሁም በአዲስ አበባ እና ድሬዳዋ ከተማ አስተዳደሮች ላይ ብቻ በመሆኑም ውሱንነቱን እንደሚያመላክት ኃላፊው ያብራራሉ። በአገሪቷ ካለው የአካል ጉዳተኞች ቁጥር አንጻር ሲታይም፤ በሁሉም አካባቢዎች ተደራሽ ሁኗል ለማለትም አያስደፍርም። እንደ ጅምር ሲታይ ግን የስልጠና ጣቢያዎቹ በሚገኙባቸው አካባቢዎች የተሻለ ለውጥ እየታየ ነው ይላሉ።
በፓራሊምፒክ 22 የሚሆኑ ስፖርቶች ይዘውተሩ እንጂ፤ ኢትዮጵያ በአራት ስፖርቶች ብቻ ነው እየሰራች የምትገኘው። እነዚህም በፓራሊምፒክ ፣አትሌቲክስ፣ ቅርጫት ኳስ፣ ክብደት ማንሳት እንዲሁም ጠረጴዛ ቴኒስ ስፖርቶች ናቸው። በአንጻሩ የጎረቤት አገራት ተሞክሮም ከ8 እስከ11 የሚሆኑ ስፖርቶች የሚዘወተሩ መሆናቸውን ኃላፊው ይጠቅሳሉ። በኢትዮጵያ ከሚዘወተሩት ስፖርቶች መካከል ከፍተኛውን ቁጥር የሚይዘው የአትሌቲክስ ስፖርት ሲሆን፤ በቀጣይ በፓራ ቴኳንዶ፣ ባድሜንተን፣ ቮሊቦል ለማካሄድ እንቅስቃሴ ተጀምሯል።
ፓራሊምፒክ ራሱን የቻለ ፌዴሬሽን ይሁን እንጂ በተለያዩ የስፖርቶች ውስጥ ተሳታፊ እንደመሆኑ ከሌሎች ፌዴሬሽኖች ጋር አብሮ መስራት ተገቢ ይሆናል። ነገር ግን በዚህ ላይ የተሰራው ስራ አመርቂ የሚባል አይደለም፤ ለአብነት ያህልም የአትሌቲክስ ስፖርት ራሱን የቻለ የዓለም አቀፍ የፓራሊምፒክ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ያለው በመሆኑ በእርሱ የሚመራ ይሆናል። ነገር ግን በሌላው ዓለም እንደሚታየው የአትሌቲክስ ውድድሮች ሲካሄዱ ጎን ለጎን ፓራሊምፒክንም ማካሄድ አልተለመደም።
ለዚህም የአቅም ውስንነት እና የአመለካከት ችግር ሊነሳ ይችላል። በተመሳሳይ በሌሎች ስፖርቶችም በሚፈለገው ልክ እየተሰራ ነው ለማለት እንደሚያስቸግር ኃላፊው ይጠቁማሉ። ጠረጴዛ ቴኒስ፣ ቴኳንዶ እንዲሁም ባድሜንተን ስፖርቶች ከፓራሊምፒክ ጋር በጋራ የሚሰራ ነው። በኢትዮጵያ ያለው ተሞክሮ ግን አካል ጉዳተኞች ላይ ለመስራት ፌዴሬሽኖቹ የአቅም ውስንነት አለባቸው። ከዚህ ባሻገር የኮሚቴው ጥረት አናሳ መሆኑንም ኃላፊው አልሸሸጉም።
በቀጣይም ስራ አስፈጻሚው በዚህ ላይ ትኩረቱን አድርጎ መስራት አለበት። በተለይ ከኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴ አትሌቲክስ፣ ቅርጫት ኳስ እና ጠረጴዛ ቴኒስ ፌዴሬሽኖች ጋር በአጋርነት ለመስራት የሚያስችል ፊርማ ለማካሄድ በዝግጅት ላይም ይገኛል። ምላሻቸው እንደየ ፌዴሬሽኖቹ ቁመና የተለያየ ቢሆንም አብሮ ከመስራት አኳያ የተጀመረው ተግባር መልካም የሚባልም ነው።
ኮሚቴው በማዘውተሪያ ስፍራዎች ላይ ሃሳብና ምክር በመስጠት እየተሳተፈም ይገኛል። እያንዳንዱ ግንባታ ሲካሄድ አሳታፊ እንዲሆን ከፓራሊምፒክ ተወዳዳሪዎች ባሻገር ለአካል ጉዳተኛ ደጋፊዎች እንዲሆን እየተሰራ ነው። ለአካል ጉዳተኞች የሚሆኑ የመወዳደሪያ ቁሳቁሶችን ከውጭ አገር አጋር ድርጅቶች ጋር በመሆን የማቅረብ እና የማገዝ ስራዎች ላይም ተሳታፊ ነው። ስፖንሰሮችን በማፈላለግ ላይም በሚፈለገው ልክም ባይሆን እየተሰራ ነው።
በአቅም ግንባታ ስልጠና ረገድ ያለፈው ሳምንት በርካታ አገራት የተሳተፉበት ስልጠና መካሄዱን ኃላፊው ያስታውሳሉ። ይህም ስፖርቱ በተሻለ ቁመና ላይ እንዲገኝ የራሱን አስተዋጽኦ ቢያበረክትም እንደ መንግስት እየተሰጠ ያለው ትኩረት አናሳ ነው። ፌዴሬሽኑ ካለበት ውስብስብ ባህሪ አንጻር እየታየ የሚገኘው ችግር እንደ ሌሎች ስፖርቶች ሲሆን፤ ከሌሎች አገራት ተሞክሮ መቅሰም እንደሚያስፈልግም ያሰምሩበታል።
ፌዴሬሽኑ በስፖርት ኮሚሽን ከሚዘጋጁ አገር አቀፍ ውድድሮች ባሻገር በዓመት ውስጥ ምንም ዓይነት ሻምፒዮና አያካሂድም። ብቸኛው ዓመታዊ የቅርጫት ኳስ ውድድርም ከቅርጫት ኳስ ፌዴሬሽን ጋር በጋራ በመሆን ነው የሚያካሄደው። በዓለም አቀፍ ደረጃም በኦሊምፒክ እና በመላ አፍሪካ ጨዋታዎች ካልሆነ በሌሎች ሻምፒዮናዎች ተሳትፎ የሌለው መሆኑም ይገልጻሉ።
ችግሮችን ለመቅረፍም ኮሚቴው ከኢፌዴሪ ስፖርት ኮሚሽን፣ ከሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር እንዲሁም ከጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ጋር በመሆን እየተሰራ እንደሚገኝ ኃላፊው ይጠቁማሉ። ከዚህ ባሻገር አገርንም ሊያስጠራ የሚችል ስፖርት እንደመሆኑ ሁሉም አካል የራሱን ድርሻ ለመወጣት መረባረብ አለበት። ሌሎች ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮችም በዚህ ስፖርት ላይ መስራትና ተሳታፊዎችንም ማፍራት ይጠበቅባቸዋል። እስከ መጪው ቅዳሜ በሚቀጥለው ውድድርም ህብረተሰቡ በትንሿ ስታዲየም ተገኝቶ ስፖርተኞቹን ቢያበረታታ የሚል ጥሪም አቅርበዋል።
ብርሃን ፈይሳ