የራሽያና የዩክሬን ጦርነት መጀመር ለሕወሓት ከመርግ የከበደ መርዶ ነው። ያው ለዓለም ሰላም፤ ለሰው ልጆች ደህንነት ፤ 3ኛው የዓለም ጦርነት በኒውክሌርና በሳይበር ታግዞ እንዳይቀሰቀስ፤ ዓለም አቀፍ ኢኮኖሚያዊ ቀውስ እንዳይከሰት ሰግቶ ወይም አስቦ አይደለም። ሕወሓት አንጥፎ ሀዘን የተቀመጠው በጌቶቹ እንደሚረሳ ሆዱ ስላወቀ ነው። ከምንም በላይ የአሜሪካና የምዕራባውያኑ ትኩረት አፍንጫቸው ስር ወደሚደረግው ጦርነት መዞሩ ነው ሕወሓትን ድንኳን ያስጣለው። እንደፈራው አልቀረም አይደለም ሕወሓት እነ ቻይና፣ እስራኤልና ኢራን ከአንደኛ ደረጃ ትኩረት ወደ 2ኛ ደረጃ ዝቅ ተደርገዋል። ምዕራባውያን በአሁኑ ሰዓት ከውስጥ ጉዳያቸው በማይተናነስ ወይም በላይ 1ኛ የትኩረት አቅጣጫ የራሽያና የዩክሬን ጦርነት፤ የሰሜን ጦር ቃል ኪዳን ድርጅትን (ኔቶ)ን ስቦ ወደ ጦርነት እንዳያስገባቸው ነው። በአንጻራዊነት ከ2ኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ ከ70 አመታት በላይ የዘለቀው አንጻራዊ ሰላም ሙሉ በሙሉ እንዳይታወክ ነው ትኩረታቸው።
መገናኛ ብዙኀኖቻቸው፣ እንደነ አመነስቲ፣ ሒውማን ራይትስዎች፣ የመንግስታቱ ድርጅት፣ የገንዘብና ሌሎች ተቋማት ዋና ትኩረት በራሽያና በዩክሬን ጦርነት ላይ ነው። የተቀረው ዓለም ተረስቷል ማለት ይቻላል። የሕወሓት ዶሴም ለጊዜውም ቢሆን ገለል ተደርጓል። በዚህ የተበሳጨው ሕወሓት ሰሞኑን ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሀኖምንና አቡነ ማቲዎስን በመጠቀም ያጣውን ትኩረት ለማግኘት ጥረት ቢያደርግም ያሰበውን ያህል አልቀናውም። ሆኖም እየየውን ለHR 6600 በግብዓትነት እየተጠቀመበት ነው። በነገራችን ላይ ዶ/ር ቴዎድሮስ አጋጣሚውን ተጠቅሞ ራሽያን እየተበቀላት ነው። የመግለጫ መዓት እያወረደባት ነው። በጸጥታው ምክር ቤት በተደጋጋሚ ከአገራችን ጎን ስለቆመች የዩክሬን ጉዳይ በማስጮህ ራሽያን እያሳጣት ነው። የየመን፣ የሶሪያና የሊቢያ የጤና ተቋማት ውድመትና ይሄን ተከትሎ ስለተፈጠረ የጤና ቀውስ ግን አንድም ቀን ትንፍሽ ብሎ አያውቅም። ምክንያቱም የዚህ ቀውስ ቀፍቃፊዎች ጌቶቹ ምዕራባውያንና አጋሮቻቸው ስለሆኑ።
ወደተነሳሁበት ነጥብ ስመለስ ሕወሓት እንደ ልማዱ እንደ ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ እየጮኸ ነው። ሌላውን እንተወውና ብቸኛውን የእርዳታ ማጓጓዣ የሆነውን የአፋር መስመር ዘግቶ እርዳታ፣ መድሀኒትና ነዳጅ እንዳይደርሰኝ ተደረገ፤ በከበባው ህጻናት፣ ሴቶችና አረጋውያን እያለቁ ነው እያለ እየየውን እያቀለጠው ነው። ጭፍራዎቹ እነ ዶ/ር ቴዎድሮስም እያስተጋቡለት ነው። እንደለመደው ትግራዋይን እንደ ሰብዓዊ ጋሻ እየተጠቀመና በእነሱ ረሀብ ፖለቲካዊ ትርፍ ለመቀላወጥ እየጣረ ነው። መንግስት ለሰብዓዊነት ግጭት አቁሜ በአባላ መቐሌ በኩል የሰብዓዊ እርዳታ እንዲደርስ እየጣርሁ ነው ማለቱን ተከትሎ ጥረቱን ለማስተጓጎል በዚሁ ግንባር ሰሞኑን ጦርነት አባብሶ ሊከፍት ይችላል። ሕወሓት እንዲህ ነው። ፖለቲካዊ ትርፍ እስካገኝለት ድረስ ትግራዋይ በረሀብ እንደ ቅጠል ቢረግፉ ጉዳዩ አይደለም። በ1977ቱ ድርቅ እኮ ሕዝብ በረሀብ እያለቀ የእርዳታ እህልን ሱዳን ላይ አየር በአየር ሽጦ የጦር መሳሪያ የገዛና የድርጅት ጉባኤ ያካሄደ ግፈኛ ነው።
የሚያሳዝነው ዛሬም የሕወሓት አመራር የሚላከውን እርዳታ ከህጻናትና ከእናቶች ጉሮሮ እየቀማ ለተዋጊዎቹ ስንቅ እያደረገው ሲሆን፤ የተረፈውን ደግሞ የታጣቂ መመልመያ አድርጎታል። የሚላክለትን ነዳጅና እርዳታ ጭነው የሚገቡ ተሽከርካሪዎችን አግቶ ታጣቂዎቹን ለማጓጓዣነት እየተጠቀመባቸው ነው። ልጁን ያልሰጠ እርዳታ አያገኝም በማለት እንደ ማስገደጃ መሳሪያ እየተጠቀመበት መሆኑን በጦርነቱ ወቅት የተማረኩና ከክልሉ የሚወጡ መረጃዎች ያስረዳሉ። ሀፍረተ ቢሱ ሕወሓት ግን ዛሬም በውስኪ እየተራጨና ተጎምጸጽ እያለ የተለመደውን የአዞ እንባውን እያነባ ነው። ሕወሓት እዚህም እዚያም እርካሽ ፖለቲካዊ ትርፉ ከመቃረም ያለፈ ለትግራይ ሕዝብ ደንታ እንደሌለው በተደጋጋሚ አረጋግጧል። ለፖለቲካዊ ትርፍ ሲል የትግራይንም ሆነ የኢትዮጵያን ሕዝብ በተደጋጋሚ ከድቷቸዋል። ከሀዲነቱ ከተነሳ አይቀር የክህደት አልበሙን አብረን ገለጥ ገለጥ እናርግ። ለምን እረሳለሁ!? እያለ ስለሆነ ባለመርሳት እንተባበረው።
ክህደት ለአሸባሪው ሕወሓት ግብሩ፣ ምሱና ማንነቱ ነውና። ከእያንዳንዱ የፖለቲካ የእጅ ስራው ውስጥ የክህደት ክር ይመዘዛል። ይተረተራል። ከልጅነት እስከ እውቀት ክህደት እስትንፋሱ ነው። ጥርሱን ነቅሎበታል። ከደደቢት ጀምሮ የትግል ጓዶችን ትግራዋይ፣ ወላጆቹን፣ ትግራይን፣ ኢትዮጵያን፣ ኤርትራን ወዘተረፈ በአደባባይና በጠራራ ሲከዳ የኖረ ከሀዲ ነው። የሚገርመው ሕወሓት ራሱን ደግሞ ደጋግሞ የከዳ፤ የፖለቲካ ጥቅም እስካስገኘለት ድረስ መርህና ርዕዮተ ዓለም ምኑም እንዳልሆነ ያረጋገጠ እፉኝት ነው። ፖለቲካዊ ትርፍ እስካስገኘለት ድረስ ሚስቱን፣ ወላጅ እናቱንና እህት ወንድሞቹን ከመክዳት የማይመለስ የአስቆርቱ ይሁዳ ነው። አደይ የሚላትን፤ በስሟ የሚምልላትንና የሚገዘትላትን ትግራይን የከዳ ነውረኛ ጉግማንጉግ ስብስብ ነው። ስሟን ለመጥራት የሚጸየፋትን ኢትዮጵያማ ከ1967 ዓ.ም አንስቶ እስከዛሬ እንደከዳት ፤ ያጠባችውን ጡት እንደነከሰ እና ከጀርባ እንደወጋት ነው። ታሪክም ሆነ ትውልድ በፍጹም ሊረሳው የማይችል የሕወሓት ታላቅ ክህደት እናንሳ።
የሕወሓት መስራች ታጋይና የፖሊት ቢሮ አባል የነበሩት አቶ ገብሩ አስራት፤ “ሉዓላዊነትና ዴሞክራሲ በኢትዮጵያ” በተሰኘው ማለፊያ መፅሐፋቸው፣ “የሄጉ የድንበር ኮሚሽን ኢትዮጵያንና ኤርትራን ካከራከረ በኋላ ሚያዚያ 5 ቀን 1994 ዓ.ም ብይኑን ሲሰጥ በሰሜን ምዕራብ ኢትዮጵያ በኩል ከ70 ኪሎ ሜትር ካሬ በላይ የሆነውን የኢትዮጵያ ግዛት ለኤርትራ ለመስጠት ወሰነ። ለኤርትራ በተሰጠው መሬት ውስጥ ለጦርነቱ ኃጢያት ተሸካሚ (scapegoat) የሆነችው ባድመ ስትካተት፤ በሰሜን ምስራቅ ኢትዮጵያ በኩል ደግሞ ቀደም ሲል በታሪክ ምንም የባለቤትነት ጥያቄ ተነስቶበት የማያውቀውን የኢሮብ መሬት በከፊል … እነ ዓይጋን፣ ወርዓትለን ፣ ዘገልባን ፣ ለኤርትራ ተወሰነ። “የወቅቱ የውጭ ጉዳይ ሚንስትር አቶ ስዩም መስፍን ግን አይኑን በጥሬ ጨው ታጥቦ ባድሜን ጨምሮ በርካታ መሬት ለኢትዮጵያ ተወሰነ ብሎ በአደባባይ ዋሸ። በዚህ ትርጉም የለሽ ጦርነት የተሰውና አካላቸው የጎደለ በአስር ሺህዎች የሚቆጠሩ ወጣቶችን፣ ወላጆቻቸውን፣ አገርንና ሕዝብን ካደ። ሕወሓት ማለት እንዲህ ነው።
ከሀዲውና እፉኝቱ ትህነግ የጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም የሰሜን ዕዝ ጥቃት እና የጥቅምት 30ን የማይካድራን ትውልድና ታሪክ ይቅር የማይለውን የክፍለ ዘመኑን ታላቅ ክህደትና ጭፍጨፋ ለመፈጸም ዝግጅቱንና ልምምዱን የጀመረው ከደደቢት ውልደቱ ከየካቲት 11 ቀን 1967 ዓ.ም አንስቶ ነው። ለግማሽ ክፍለ ዘመን በዝግ የተዶለተበት የክህደት ደባ። የጭካኔ ልምምድና ዝግጅት ውጤት። ጠቅላይ ሚኒስትር አምና በፓርላማ ቀርበው እንደገለጹት፤ “ …የመከላከያ ትጥቁም ስንቁም ለአመታት እዚያ ብቻ እንዲከማችበት የተደረገበት ምክንያት አሁን የመጣው ለውጥ ቢመጣም ባይመጣም፤ የአገሪቱ የመከላከያ እዚያ ብቻ እንዲሆን ታስቦ ነው። ምንም ሚስጥርም የለውም። …” የጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር ክህደቱ ቀድሞ የታሰበበትና የተመከረበት ስለመሆኑ ያነሳሁትን ሙግት ያጠናክርልኛል። ሕወሓት የክህደት ልምምዱ አሀዱ ብሎ ከጀመረበት እስከ ፍጻሜው የሚመዘዙ ቅጥልጥል ክህደቶችን እንመልከት።
የከሀዲውን ማንነት ጠንቅቀው ለሚያውቁት ክህደቱ የሚጠበቀና አስቆርቷዊ ነው። ለዚህ ነው እንደ አረጋዊ በርሔ (ዶ/ር) ያሉ ነባር ታጋዮች እና የሸዓቢያ ጉምቱ ሰዎች ትህነግን ከፍጥርጥሩ ጀምረው ስለሚያውቁት በጥቅምት 24ቱ አሳፋሪ ክህደት እንደተቀረው ኢትዮጵያዊ ያልደነገጡት። ያልተገረሙት። ኢትዮጵያውያንን ያለ ልዩነት በድንጋጤ እጃቸውን በአፍ ያስጫነው ክህደቱም ሆነ ጭካኔው በአገሪቱ ታሪክ ተከስቶ የማያውቅና ከሕዝቡ የስነ ልቦና ውቅር ፍጹም ያፈነገጠ መሆኑን ልብ ይሏል። ለ21 አመት በቀበሮ ጉድጓድ ሆኖ ሲጠብቀው የኖረን የወገን ጦር የከዳ ቢኖር ከሀዲውና ተላላኪው ሕወሓት ብቻ ነው።
በአዲስ አበባ ፒያሳ በኬቭ ካፌ በራድ ሻይ ፉት እያለ ሆነ በሌላ ቦታ ሆኖ ወደ “ትግል” ሜዳ ለመውጣት ሲወስንም ሆነ፤ ወስኖ እንደወጣ ታሪክን፣ እውነትን፣ ሰንደቃላማን፣ አብሮነትን፣ ሰብዓዊነትን፣ ኢትዮጵያዊ ማንነትን፣ ፍቅርን፣ ሰውነትን፣ ፈጣሪን፣ ወዘተረፈ ሽምጥጥ አድርጎ ክዶ የራሱን የፈጠራ ትርክት ነው የነበረው።
የአገሪቱን ታሪክ ወደ 100 አመታት አሳንሶ፤ እውነትን ኅልቁ መሳፍርት በሌለው ውሸት ተክቶ፤ ሰንደቃላማን ጨርቅና የአንድ ሃይማኖት አርማ ነው ብሎ፤ አብሮነትን በመለያየት ቀይሮ፤ ሰብዓዊነትን በአረመኔነት ለውጦ፤ ኢትዮጵያዊ ማንነትን በጎሳ ሰንጥቆ፤ የትግራይ ሕዝብ ጠላት የአማራው ገዥ መደብና ኦርቶዶክስ ነው ብሎ፤ ፈጣሪን ክዶ ራሱን ወደጣኦትነት ቀይሮ እስከማስመለክ የደረሰ፤ ወዘተረፈ የራሱን ተረክና እውነት በይኖ በራሱ ዓለም ሲዳክር የኖረ ባተሌ ስብስብ ነው።
የእውነትን፣ አገራዊ ነባራዊ ሁኔታን፣ የዜጋውን የልቦና ውቅርና የታሪክን ፈለግ ተከትሎ ርዕዮት ዓለም መንደፍ የማታገያ ስልት መትለም ሲገባው፤ በተቃራኒው እውነትን፣ አገራዊ ተጨባጭ ሁኔታን፣ የዜጋውን ልቦና ውቅርና ታሪክ በድቡሽት ላይ ለተቀለሰ ማንፌስቶው እንዲመጥኑ እጃቸውን ጠምዝዞና አጣሞ እንደገና መበየኑ እና ካፈርሁ አይመልሰኝ በሚል በስሁት መንገዱ ልምምዱን መቀጠሉ ጎልማሳው ከሀዲ አድርጎታል። ከጥፋቱና ከዕድሜው የማይማር ልበ ቢስ። ጠቅላይ ሚንስትሩ እንዳሉት ያለፈውን የመርሳት አባዜ ስላለብን ዋና ዋና ክህደቶቹን ብቻ እናስታውስ።
ቢያንስ ወደ ስምንት ሺህ አመት የሚጠጋ ቀደምት አገረ መንግስትና ታሪክ ያላትን ጥንታዊት አገር በልኩ ካሰፋው የታሪክና የርዕዮት ዓለም ቁምጣ ጋር ለማስኬድ ሲል በአሳሽ እንደነ አሜሪካ የተገኘች ይመስል ታሪኳን የ100 አመት ነው ሲል በአደባባይ የካደ የነውረኞች ስብስብ ነው ። የዛሬዋ ኢትዮጵያ ቅርጽ ስሪት በአፄ ምኒልክ የተፈጠረ ነው አለ። በጎሳ ላይ የተመሰረተው አስመሳይ ፌደራሊዝም የተዋቀረው በዚህ ክህደት ላይ። የአንድ አገር ጥንታዊነት ተካደ ማለት የቁጥር ጉዳይ ብቻ አይደለም። የዜጎችን አብሮነት፣ የአገሪቱን የአገረ መንግስት ልምምድና አጠቃላይ ማንነቷን የሚያኮሰምን ክህደት ነው። ዜጋው በአገሩና በታሪኩ ያለውን እምነት ለመሸርሸርና አንድ አርገው አጋምደው ያቆዩትን ወረቶች ለማስጣል የተከናወነ መሰሪ ክህደት ነው።
ይህ ብቻ አይደለም ለአገሪቱ ያለው ጥላቻ ግዝፎ ነስቶ የተገለጠበት ክህደት ጭምር ነው። በዓለማችን ላይ የአገሩን ታሪክ አሳንሶ ሽንጡን ይዞ የተከራከረ እና አምርሮ የሚጠላትን አገር የገዛ እንደ ከሀዲው ሕወሓት/ትህነግ ያለ ቡድን የለም። ይህን ጥላቻውን አገዛዝ ላይ እያለ በሚያራምዳቸው ስሁት ፖለቲካዊ አቋሙና አይን ያወጣ ዘረፋው አረጋግጧል። ከገዢነቱ በሕዝባዊ ማዕበልና በለውጥ ኃይሉ ከተሽቀነጠረ በኋላ እኔ ረግጬ የማልገዛትና የማልዘርፋት አገር ትውደም በሚል የሔደበትን እርቀት ታሪክም ትውልድም በቁዘማ ሲያስታውሰው ይኖራል።
አገራችን ኢትዮጵያ በጀግኖችና እውነተኛ ልጆቿ ታፍራና ተከብራ ለዘላለም ትኑር !!!
አሜን።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)
fenote1971@admin
አዲስ ዘመን መጋቢት 18 ቀን 2014 ዓ.ም