“ኢህአዴግ በቅርቡ 9ኛ ድርጅታዊ ጉባኤውን አካሂዷል፡፡ በዚህ ጉባኤ ላይ በተለይ በአምስት ዓመቱ የእድገትና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ተስፋ የተሰጠው የግብርና ዕድገት በ2004 ዓ.ም የታሰበውን ያህል ውጤት አለማምጣቱ፣ በዕቅዱ የሰፈሩ የልማት ሥራዎችን ለማሳካትና የልማት ሠራዊት ግንባታ ሂደትን፣ በድርጅቱ አባላት ዘንድ የታዩ የአመለካከት፣ የአድርባይነትና በራስ ያለመተማመን ችግሮችን እንዲሁም በ8ኛ ጉባኤ ላይ ተወስኖ የተጀመረው የመተካካት ስትራቴጂ አተገባበር ላይ በጥልቀት ተወያይቶ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡” የሚለውን፤ የወቅቱ ኢህአዴግ እከተለዋለሁ ይለው የነበረውን የመተካካት ስትራቴጂ (“የአመራር ለውጥ”ም ይባል ነበር) የወቅቱን የሚዲያዎች ሀተታ፣ በዚያው ወቅት ከህዝብ፤ በተለይም “ተቃዋሚ” ይባሉ ከነበሩት የፖለቲካ ፓርቲዎች ሲሰነዘሩ የነበሩ አስተያየቶችንና የሰሉ ሂሶችን በማስታወስ ስለ ስልጣን፣ ባለስልጣንና አሿሿም አንዳንድ ሀሳቦችን እንለዋወጥ።
በተለይ “መተካካት ያስፈለገው ይህን ገዢና አውራ ፓርቲ ለመጪዎቹ 30 እና 40 ዓመታት አገዛዙን ይዞ እንዲቀጥል ለማድረግ ነው፡፡ ከሃገራዊ ፖለቲካ አንፃር የዴሞክራሲ ስርዓቱ እንዲያብብ የሕብረተሰቡ አመለካከት በተለያዩ ፓርቲዎች ተወክሎ በምርጫ መስተናገድ እንዲችል ኢህአዴግ መስራት ከሚገባው አንድ በመቶውን እንኳን እየሰራ ነው ብዬ አላምንም” የሚሉ የተቃዋሚው ጎራ አባላትን አስተያየቶች (ለምሳሌ በወቅቱ ለጉዳዩ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ ያስተናግድ የነበረውን “ኢትዮ ቻናል” ቅዳሜ መጋቢት 21፣ 20005 ዓ.ም ዕትምን ይመለከቷል) ለሚያስታውስ ሰው የ”ስልጣን፣ ባለስልጣንና አሿሿም”ን ከገዢ ፓርቲ ጋር በማያያዝ አስተያየት መስጠት የተለመደ ብቻ ሳይሆን የግድም ነውና ጉዳዩ መቼም ቢሆን አነጋጋሪ፣ አወያይ፣ አመራማሪ ነው። በመሆኑም አሁን በሚሰጡ ሹመቶች ዙሪያም የሚነሱትን አስተያየቶች ከዚሁ አኳያ መገንዘብ ይገባል።
በወቅቱ የነበረው ገዥ/አውራ ፓርቲ “መተካካት ያልኩትን በሚገባ ተግባራዊ እያደረኩ ነው” በማለት በማስረጃነት ሲያቀርበው የነበረው የመተካካት ሂደት፤ ለምሳሌ “ብአዴን 85 የማእከላዊ ኮሚቴ ነባር አባላትን በአዲሱ ትውልድ ተክቷል፡፡” እና የመሳሰሉትን በመጥቀስ ነበር። ግን ማንም “አበጀህ” ያለው አልነበረም። ለዚህ ምክንያቱ ደግሞ በርእሳችን ለማንሳት እንደሞከርነው “ድመት መንኩሳ አመሏን አትረሳ” እንደሚባለው፤ ባለስልጣናትን ቦታ የማቀያየር እንጂ እንደ ተባለው በአዲስ ትውልድ የመተካት ሥራ አልነበረምና ነው። እነዚህ “አበጀህ” ማለት ያልፈለጉ ወገኖችም ያላሉበትንና የማይሉበትን ምክንያትም “… የብአዴንን ሁኔታ ካየን ከሁለት ዓመት በፊት ከድርጅቱ ለቅቀው የነበሩት አቶ አዲሱ ለገሰ ልክ እሳት እንዲያጠፋ እንደተጠራ እሳት አደጋ ዳግም ወደ አመራርነት እንዲመጡ ተደርጓል፡፡” የሚል አስተያየት በመስጠት “የመተካካት ሂደት” የተባለውን ያጣፉታል።
በወቅቱ “አቶ አዲሱ ለገሰን በተመለከተ የተናገሩት ግን ፍፁም የተሳሳተ ነው፡፡ ከሁለት ዓመት ቀደም ብሎ ከብአዴን ምክትል ሊቀመንበርነት ኃላፊነታቸው ተነስተው ቦታቸውን ለተተኪ መስጠታቸው እውነት ነው፡፡ ይሁን እንጂ የማእከላዊ ኮሚቴ አባል ሆነው ቀጥለዋል፡፡” የሚለውና ከወደ ኢህአዴጎች አካባቢ ሲሰጥ የነበረው ማስተባበያ ምንም አይነት ሆድ የሚያባባ ነገር ይዞ ሊመጣ ባለመቻሉ “የመተካካት ስትራቴጂው ከሽፏል፤ ሲጀመርም የውሸት ነበር ….” በማለት አስተያየት የሚሰጡ ወገኖችን አንጀት ሊያራራ አልቻለም ነበር።
ጭራሽ ማስተባበያ የተባለው ህዝቡን ወደ ባሰ ቅያሜና ተቃውሞ እየገፋው በመሄዱ የፓርቲው መጨረሻ በብልፅግና መተካት ሆነና አረፈው። እውነትም ያ ሁሉ “መተካካት” ምንም የፈየደው ነገር አልነበረም። ባለመኖሩም እነሆ ዛሬ ጊዜው የብልፅግና ሊሆን፤ የወቅቱ አውራም በብልፅግና ሊተካ በቅቷል። ይህ ደግሞ የሚያሳየው ብቻ ሳይሆን የሚያስተምረው አቢይ ጉዳይ ቢኖር በአገር ጉዳይ፣ በህዝብ ፍላጎት … ላይ ማላገጥ መጨረሻው ያማረ አለመሆኑን ነውና ብልፅግናም እየሰጣቸው ባሉት “አዳዲስ” ሹመቶችና ተሿሚዎች ላይ አስፈላጊውን ፖለቲካዊ ጥንቃቄ ሊያደርግ ይገባል ለማለት ነው።
በኢህአዴግ 9ኛ ድርጅታዊ ጉባኤና በተለይ የጉባኤው አንድ አጀንዳ በነበረው መተካካት ላይ ይሰጡ የነበሩ ሃያሲ አስተያየቶችን፤ ፊት መሪ የለውጡ አራማጅ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማሪያም፤
“ወግ ነው ሲዳሩ ማልቀስ ይባል ነበር ዱሮ ፣
ወግ ነው ምርጫ ማሸነፍ ሆነ ዘንድሮ!” (“ፍትህ” መጽሄት)
ያሉትን ሳይቀር እዚህ ማንሳታችን ያኔም ሆነ አሁን ችግሩ ያለው የራሳችን ችግሩን በማረምና በማስተካከል አለመድገምም ያለብን ራሳችን በመሆናችን ላይ ሲሆን፤ ወደ አሁኑ ወቅት ስንመጣም ወቅቱ ከሕዝብ ጋር እየተመከረበት ያለ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ ለሕዝብ ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት ሲባል የሹም-ሽር እንቅስቃሴዎች ሊታዩ የሚችሉበት ስለሚሆን ወደ’ዛው ሄደን አንዳንድ ጉዳዮችን እናንሳ።
ፕሮፌሰር መስፍን የቀድሞው አውራ (ኢህአዴግ) አባላትና ተሿሚዎቹ በሚናገርበት ጊዜ፤ ሁሉ እያነሣ የመጣልና እየጣለ የማንሣት ዝንባሌን እንደሚያሳይ በመገንዘባቸው ይመስላል፣
“ወደድኩህ ወደድከኝ፤ ጠላሁህ፣ ጠላኸኝ፤
እንደሚጣራ ጠጅ እየጣልክ አታንሣኝ!”
የምትል የአንዲት አረጋዊት እንጉርጉሮ ድምጽን የምታስተጋባ መንቶን በማዋዣነት ጣል ሲያደርጉ የነበረው፡፡ እናም አሁንም ከ”ተጣሉ” በኋላ የሚነሱ፤ ከ”ተነሱ” በኋላ የሚጣሉ (ይህ እንኳን በምክንያት ከሆነ ችግር የለውም) እየበዙ ነው የሚሉ አስተያየቶች እየተሰሙ መሆናቸው የፕሮፌሰርን መንቶ እንደገና እንዳነሳ ተገድጃለሁ።
አንድ ወቅታዊ ምሳሌን ላንሳ። ባለፈው የካቲት ወር የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት የእቅድ አፈፃፀም ግምገማ ሪፖርት ባዳመጠበት ወቅት፤ በሪፖርቱ ከመሬት ወረራ፣ ዘረፋ …. ጋር (ብቻ) በተያያዘ 155 አመራሮችና 80 ባለሙያዎች በተግባሩ ተሳታፊ ሆነው መገኘታቸው ተገልጾ ነበር፡ ፡ እነዚህን በፕሮፌሰር መስፍን ቋንቋ እንግለፃቸው ከተባለ “ተጣሉ” ማለት ነው። በመሆኑም ሕዝቡ እነዚህን በስራቸው ሲጠየቁ እንጂ በምንም መንገድ “ተነስተው” ማየት አይፈልግም። በቃ “ጠላሁ” ላለ ህዝብ ከዚህ ዞር ተደርገው በጓሮ በር ተመልሰው ከተፍ እንዲሉበትና ሌላ ዙር ዘረፋን እንዲፈጽሙበት አይፈልግም።
ተሿሚዎቹም ቢሆኑ (የሰሩትን ያውቁታልና) የፕሮፌሰሩን “እየጣልክ አታንሣኝ!”ን መድገም አለባቸው። ሰሞኑን በተካሄደው የብልፅግና 1ኛ መደበኛ ጉባኤ ላይ “ቻው” የተባሉት ከ10ሺህ በላይ የፓርቲው አባላትም እንደዛው። አይ ተብሎ የጣሉትን ማንሳት የግድ ነው ከተባለ ህዝብም ሌላው ቢቀር እንኳን፣ “ድመት መንኩሳ ….” ማለቱ አይቀርምና ጉዳዩ እዳው ገብስ አይደለም። በዛው ልክ ሕዝብ አንድ አካባቢ ላይ በቃኝ ያላቸውን ወስዶ ወደ ሌላ የማስቀመጥ ልምዳችንም ሊታረም ይገባዋል፡፡
ምክንያቱም አንድ ቦታ ላይ ሕዝብ ያማረረ መሪ ወደሌላ ቦታ ሲዛወር ምንም እንኳን የዛ አካባቢ ሕዝብ የጠላው ቢሆንም አሰራርና ምግባሩ ለፓርቲው/ ለመንግሥት አሰራር ምቹ ነው የሚል ትርጉም የሚያሰጠው ነው፡፡ ይህ ደግሞ የተዛወረው አመራር ከክፉ ተግባሩ እንዳይማር፤ ሌሎችም የእሱን ተግባር በአርዓያነት እንዲከተሉ፤ ሕዝብም በመንግሥት/ ገዢው ፓርቲ ላይ እምነት እንዲያጣ የሚያደርጉ ናቸው፡፡ በመሆኑም የተጣሉትን ማንሳትም ሆነ ሽግሽግ መስራት ለሕዝብ ጥያቄ መልስ ካለማሰጠቱም በላይ፤ “ድመት መንኩሳ…” ነውና ራሳቸውም ሌሎችም ትምህርት እንዳይወስዱ፤ የበለጠ ለጥፋት እንዲሰሩ የሚያደርጋቸው መሆኑን ልብ ሊሉ ያስፈልጋል፡፡
አዲስ ዘመን መጋቢት 18 ቀን 2014 ዓ.ም
ግርማ መንግሥቴ