ከበረራ አስተናጋጅ እስከ አብራሪ፤ ከተማሪ እስከ ተመራማሪ፣ ከሰብዓዊ ዕርዳታ ሠራተኛ እስከ ፖለቲከኛ፣ ከኢንጅነር እስከ ሃኪም ከወታደር እስከ የፓርላማ አባል ሁሉም ውድ ህይወታቸውን ያጡበት የዕሁድ ለታው የኢትዮጵያ አየር መንገድ በረራ ቁጥር ኢቲ 302 ቦይንግ 737 – 800 ማክስ አውሮፕላን አደጋ መላውን ዓለም አሳዝኗል።
በአደጋው 8 የበረራ ሠራተኞች፣ 9 ኢትዮጵያውያን መንገደኞችና ከ35 አገራት ለተለያየ ጉዳይ ወደ ናይሮቢ ኬኒያ ለመሄድ በአውሮፕላኑ የተሳፈሩ 140 ዜጎች በጥቅሉ የ157 ሰዎች ህይወት አልፏል። 32 ኬኒያውያን፣ 12 ካናዳውያን፣ 9ኙ ከኢትዮጵያ፣ 8 ጣሊያናውያን፣ 8 ቻይናውያን፣ 8 አሜሪካውያን፣ 7 የብሪታንያ፣ 7 ፈረንሳውያን፣ 6 ግብፃዊያን፣ 5 ጀርመናዊያን፣ 4 ህንዳዊያንና 4 ስሎቫኪያዊያን ዜጎች መሆናቸው ታውቋል።
እንዲሁም 3 የኦስትሪያ፣ 3 የስዊድን፣ 3 የሩስያ፣ ሞሮኮ፣ ስፔን፣ ፖላንድና እስራኤልም እያንዳንዳቸው ሁለት ሁለት ዜጎቻቸውን አየርላንድ፣ ኔፓል፣ ሳኡዲ አረቢያ፣ ጅቡቲ፣ ቤልጅየም፣ ኢንዶንኤዥያ፣ ሶማሊያ፣ ኖርዌይ፣ ሰርቢያ፣ ቶጎ፣ ሞዛምቢክ፣ ሩዋንዳ፣ ሱዳን፣ ኡጋንዳና የመን ደግሞ እያንዳንዳቸው አንድ አንድ ዜጎቻቸውን አጥተዋል። የኢፌዴሪ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሰኞ ዕለት ብሄራዊ የሐዘን ቀን አውጆ የዋለ ሲሆን በመላው ኢትዮጵያ እና በመላው ዓለም በሚገኙ የኢትዮጵያ ኤምባሲዎችና ሚሲዮኖች ሰንደቅ ዓላማ ዝቅ ብሎ እንዲውለበለብ ተደርጓል።
መላው ዓለምም እስከአሁን ድረስ ሐዘኑን እየገለጸ ይገኛል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በደረሰው አደጋና ከልብ ማዘናቸውን ገልጸው “ለሁሉም የሟች ወገኖችና ቤተሰቦች መፅናናትን እመኛለሁ” ብለዋል። የኬኒያው ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬኒያታ፣ የካናዳው ጠቅላይ ሚኒስትር ጀስቲን ትሩዶ፣ የብሪታኒያዋ ጠቅላይ ሚኒስትር ቴሬሳ ሜይ፣ የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን፣ በእጅጉ ማዘናቸውን ገልጸው ለሟች ቤተሰቦች “ሃዘናችሁ ሃዘናችን ነው” የሚል የማጽናኛ መልዕክት አስተላልፈዋል።
የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር ሙሳ ፋቂ ማህመትና የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትም በተመሳሳይ ሐዘናቸውን ገልጸዋል። የሃያ አንድ ሠራተኞቹን ህይዎት ያጣውየተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የቀድሞ ዋና ፀሐፊ “አደጋው የሁላችንም ቤት አንኳክቷል፤ ጥልቅ ሐዘንም ተሰምቶናል” በሚል አሳዛኙን አደጋ የገለጹበት መንገድ በእርግጥም በኢትዮጵያ አየር መንገድ ላይ የደረሰው የአውሮፕላን መከስከስ አደጋ ሁሉንም ያዳረሰ መላውን ዓለም ያሳዘነ ክስተት መሆኑን የሚያመላክት ነው። የዓለም መገናኛ ብዙሃንም የ157 ሰዎችን ህይዎት የቀጠፈውንና መላውን ዓለም ያሳዘነውን የአውሮፕላን አደጋ ሰፊ ሽፋን ሰጥተው እየተከታተሉ እየዘገቡት ይገኛሉ።
በማህበራዊ ሚዲያውም እንደዚሁ ዋነኛ የመወያያ ርዕስ ሆኖ ቀጥሏል። ታዲያ ከዚሁ ከደረሰው ጉዳትና ከተፈጠረው ሐዘን እኩል በዓለም መገናኛ ብዙሃኑ ትኩረት ተሰጥቶት በስፋት እየተዘገበ የሚገኘው አደጋውን ያስተናገደው የቦይንግ ስሪቱ 737 -800 ማክስ አውሮፕላን ጉዳይ ነው። ለምን? ቀጥለን የምንመለከተው ይሆናል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የበረራ ደህንነትና የአብራሪው ብቃት የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ተወልደ ገብረማርም ከአደጋው በኋላ ለመገናኛ ብዙሃን በሰጡት መግለጫ እንደተናገሩት አደጋው የደረሰበት አውሮፕላን ከቦይንግ ኩባንያ ከተገዛ አራት ወራትን ብቻ ያስቆጠረና አዲስ ነው። አውሮፕላኑ እስከአሁን ድረስ የበረረውም 1200 ሰዓታትን ብቻ ሲሆን በጥር ወርም የቴክኒክ ምርመራ ተደርጎለታል።
የአውሮፕላኑ አብራሪ ግማሽ ኢትዮጵያዊና ግማሽ ኬንያዊ ዜግነት ያለው ካፕቴን ያሬድ ጌታቸውም 8 ሺ ሰዓቶችን ያበረረና ብቁ መሆኑ የተመሰከረለት ነው። እንደዚሁ ረዳት አብራሪውም 200 ሰዓታትን ያበረረ ነው። ከዚህ አኳያ ምንም እንኳን የአደጋው መንስኤ እየተጣራ ቢሆንም ከተገዛ አራት ወራትን ብቻ ያስቆጠረና የካበተ ልምድ ባላቸው አብራሪዎች ሲበር የነበረ አውሮፕላን በዚህ መንገድ ለአደጋ መጋለጡ በርካቶች በስሪቱ ላይ ጥርጣሬ እንዲያድርባቸው አድርጓል። የሲ.ኤን.ኤኑ የአቬሽን ኤክስፐርት ሪቻርድ ክዌስትም “የኢትዮጵያ አየር መንገድ በዓለም ላይ ለደህንነት ተመራጭ ከሆኑት መካከል ቀዳሚው ነው” በማለት የዋና ሥራ አስፈጻሚውን ሃሳብ ይደግፋሉ።
ከዚህ ቀደም በኢንዶን ኤዥያ አየር መንገድ ላይ ተመሳሳይ አደጋ መድረሱ ከዛሬ ስድስት ወር በፊት በአውሮፓውያኑ ጥቅምት 2018 የእነዚህ አውሮፕላኖች ተመሳሳይ በኢንዶኖዥያ አደጋ የደረሰበት መሆኑና አደጋው ስድስት ወር ባልሞላ ጊዜያት ውስጥ ተመልሶ መከሰቱ የአምራች ድርጅቱን ሃሳብ ውስጥ እንዲገባ ማድረጉን ቢቢሲ ዘግቧል። ስለሆነም ኢንዶኖዥያ ከዚህ አውሮፕላን ጋር የሚመሳሰሉት አውሮፕላኖችን ከበረራ አግዳለች። የኢትዮጵያ አየር መንገድም በተመሳሳይ የተጓዦቹን ደህንነት ለመጠበቅ ሲል ያሉትን የቦይንግ 737 ማክስ አውሮፕላኖች በጊዜያዊነት ከበረራ አግዷል።
ይህን ተከትሎም ሌሎችም በርካታ አገራት ተመሳሳይ ዕርምጃ በመውሰድ ላይ ይገኛሉ። ቻይና ከፍተኛ የቦይንግ 737 ማክስ አውሮፕላን ተጠቃሚ አገር ስትሆን በዚህ ሞዴል የሚጠሩ ሁሉንም አውሮፕላኖቿን ማገዷን ይፋ ማድረጓን ሲ ኤን ኤንና ቢቢሲ ዘግበዋል። የሜክሲኮው ኤየር ሜክሲኮ፣ የአርጀንቲናው ኤየርላይኒያስ አርጀንቲንስ፣ የደቡብ አፍሪካው ኮሜየር፣ ካይማን ኤርዌይስ፣ የደቡብ ኮሪያው ኢስታርዌይስ፣ የብሪታኒያው ቲዩአይ፣ የብራዚሉ ጎል ሊናስ ኤርያስ፣ ማሊዥያ፣ ኤስላንደር፣ ጀርመን፣ ፍላይ ዱባይ፣ ኮንገኮንግ፣ ፊጅ ኤርዌይስ፣ የሩስያው ኤስ 7 አየር መንገድና የካናዳው ሰንዊንግ አየር መንገድ አውሮፕላናቸውን በከፊል አሳርፈዋል። ሲንጋፖር፣ አውስትራሊያ፣ ብሪታኒያ፣ ኦማን፣ ኖርዌይ፣ ፈረንሳይ፣ አየርላንድ፣ ቱርክ፣ የተባበሩት አረብ ኢሚሬት፣ ኩዌት፣ ኒውዝላንድ፣ የአውሮፓ ህብረትና ህንድ በቦይንግ 737 ማክስ አውሮፕላን ላይ ሙሉ ዕገዳ የጣሉ አገሮች ሆነዋል። በአንጻሩ ንብረትነታቸው የአሜሪካ የሆኑት አሜሪካን ኤርላይንስ፣ ዩናይትድ ኤርላንስና ሳውዝዌስት ኤርላይንስ፤ ፍላይ ዱባይና የካናዳው ውስትጄት አሁንም ቦይንግ 737 ማክስ አውሮፕላኖችን እየተጠቀሙ የሚገኙ አየር መንገዶች መሆናቸውን የሲ.ኤን.ኤን ዘገባ ያመለክታል።
በርካታ አገራት በቦይንግ 737 ማክስ አውሮፕላን ላይ የጣሉትን ዕገዳ ተከትሎም የቦይንግ ኩባንያ ሽያጭ ያሽቆለቆለ ሲሆን ማግኘት ከሚገባው አውሮፕላን ሽያጭ ገቢም አስራ ሦስት በመቶ የሚሆነውን አጥቷል። ከመስከረም አስራ አንዱ አሜሪካ የሽብር ጥቃት በኋላም ኩባንያው በታሪኩ እጅግ መጥፎ የሚባል የንግድ ቀናትን አስተናግዷል። በመሆኑም የቦንግ ኩባንያ በኢትዮጵያ አየር መንገድ አደጋው ከደረሰበት ጋር ተመሳሳይ የሆኑ ሁሉንም የቦይንግ 737 ማክስ አውሮፕላኖችን በጊዜያዊነት ከአገልግሎት እንዲያግድና ደህንነታቸውን እንዲመረምር ከየአቅጣጫው ግፊት በርትቶበታል።
ይሁን እንጂ “የአደጋው መንስኤ ገና ምን እንደሆነ ባልታወቀበት ሁኔታና የምርመራው ሂደት በጅምር ባለበት በአውሮፕላናችን እንቅስቃሴ ላይ የምናመጣው ምንም ዓይነት አዲስ አሠራር አይኖርም” በማለት በምክትል ፕሬዚዳንቱ ቻርሊ ሚለር አማካኝነት ምላሽ ሰጥቷል። በዚህ ሳምንት ለመጀመሪያ ጊዜ ለገበያ ሊያቀርባቸው አስቧቸው የነበሩ አዳዲስ ቦይንግ 777 ጀትላይነር አውሮፕላኖችን ላልተወሰነ ጊዜ አራዝሟል። ኩባንያው ለደህነነት ጉዳይ ቅድሚያ ሰጥቶ የሚሠራ መሆኑንና በኢትዮጵያ አየር መንገድ የበረራ ቁጥር ኢቲ 302 ቦይንግ 737 -800 ማክስ አውሮፕላን ላይ በደረሰው አደጋ ከልብ ማዘኑንና የአደጋውን መንስኤ ለማወቅ በሚደረገው ምርመራ ላይ የራሱን የቴክኒክ የምርመራ ቡድን እንደሚልክና ከዓለም አቀፉ የምርመራ ቡድን ጋር ተባብሮ እንደሚሠራ አስታውቋል።
በአሁኑ ሰዓት ከኢትዮጵያ ብሔራዊ አቪዬሽን ደህንነት ኤጀንሲ፣ ከተባበሩት መንግሥታት የብሔራዊ ትራንስፖርት ደህንነት ቦርድና ከአሜሪካ የፌዴራል አቬሽን አስተዳደር የተውጣጣውና በኢትዮጵያ የሚመራው ዓለም አቀፉ የምርመራ ቡድን ምርመራ እየተካሄደ መሆኑን ዘ ቶክ ኦፍ ላስ ቬጋስ የተባለ ድረገጽ ዘግቧል። በተደረገው ምርመራም የአደጋውን መንስኤ ሊጠቁም የሚችለው የአይሮፕላኑ የመረጃ ቋት የሆነው ‹‹ጥቁር ሳጥን›› ተገኝቷል። የአውሮፕላን አደጋ መርማሪ ቡድኑ በቦይንግ ላይም ምርመራ የሚካሂድ መሆኑንና ውጤቱን ተከትሎም በአውሮፕላኖቹና በአጠቃላይ የኩባንያው አሠራር ላይ ለውጥ የሚያስፈልግ ከሆነ የሚያሳውቅ መሆኑን ዘገባው ጨምሮ አመላክቷል።
አዲስ ዘመን መጋቢት 5/2011
በይበል ካሳ