(ክፍል ሁለት)
አዎ ! በጀግኖች አባቶቻችን ከ125 አመታት በፊት የተቀዳጀነውን ታላቁ የዓድዋ ድልም ሆነ ፤ ከጣሊያን የአምስት አመቱ ቆይታ፤ ከንጉሣዊ አገዛዙ፤ ከጊዜአዊ ወታደራዊ አስተዳደር ደርግ ነፃ የወጣንባቸውን ድሎች ልንከላከላቸውና ልንጠብቃቸው ባለመቻላችን ለአንድ ምዕተ አመት ከሩብ ለዘለቀ አሳር እንደዳረገን ውድ ዋጋ እንዳስከፈሉን በጥሞና ልናንሰላስለው ይገባል።የሚያሳዝነው ከእነዚህ ወሳኝ የታሪክ መታጠፊያዎች ዛሬም አለመማራችን ነው።ብልጥ ብንሆን ከሌሎች የሰው ልጆች ታሪክ መማር በቻልን።
እኛ ግን ከራሳችን ታሪክ መማር ባለመቻላችን ዛሬ ለምንገኝበት ቅርቃር ዳርጎናል።ከትናንቱ የ27 አመታት ግፍ፣ መከራና አሳር እንኳ መማር አልቻልንም።አይደለም የዓድዋውን፣ የአምስት አመት የጣሊያን ወረራ፣ የደርግና የትህነግ / ኢህአዴግ ነፃነቶችን ባለፉት አራት አመታት በአደራ የተረከብነውን የነፃነት ቀብድ እንደቀደሙት ባክኖ፣ ትርጉም አጥቶ እንዳይቀር በአግባቡ ለመጠቀም፣ ከቅልበሳ ለመከላከልና ለመጠበቅ የተዘጋጀን አይመስልም፡፡
ሬይሞንድ፣ አፄ ምኒልክ እና እቴጌ ጣይቱ ወደ ሰሜን የዘመቱት ወራሪውን ፋሽስት ጣሊያን ድል ለመንሳት ብቻ አልነበረም።የአገሪቱን ውስጣዊ አንድነት በደም አስተሳስረው በጋራ ጠላት ላይ በመዝመት የጋራ አገር ለመገንባት እንጂ ይለናል።ይሁንና ዛሬ አገራችን ድንበርን ተሻግሮ የሚወር ጠላት ባይኖራትም ከታላቁ የህዳሴ ግድብ ጋር ተያይዞም ሆነ በሌሎች ፈተናዎች በብሔራዊ ጥቅሟ ጉሮሮ ላይ ለመቆም የጦር ዕቃውን ታጥቆ፣ የራስ ቁሩን ደፍቶ፣ ጡሩሩን ለብሶ፣ ጦሩን እየሰበቀና ዘገሩን እየነቀነቀ ግዳይ ለመጣል አጋጣሚውን በንቃት የሚጠብቅ ኃይል መኖሩን ያቃለልን መሆኑን ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ በአንድ መድረክ ፓርላማ ቀርበው አርድተውናል።በቅጡ ተረድተናቸዋል የሚል እምነት ግን የለኝም።ለሥልጣን ጥም ማርኪያ ብሔራዊ ጥቅሟን፣ አገራዊ አንድነቷን ያለምንም ማቅማማት አሳልፎ ለመስጠት በጥፍሩ የቆመ ኃይል መኖሩን አናንቀነዋል፡፡
የሰላማችን፣ የአንድነታችን፣ የሉዓላዊነታችንና የተስፋችን ስጋት የሆኑ ኃይሎችን ልናስቆማቸው የምንችለው አያት ቅድመ አያቶቻችን የዓድዋ ድልን ለመቀናጀት በአንድነት እንደቆሙት ሁሉ እኛም ልዩነቶቻችንን አቆይተን ይሄን ክፉ ቀን ለማለፍ ዳር እስከ ዳር እጅ ለእጅ ተያይዘን በአንድነት መቆም ስንችል ነው። በታላቅ መስዋዕትነት እጃችን የገባ የጋራ ነፃነትን ለመከላከልና ለመጠበቅ ሌት ተቀን በንቃት መቆም አለብን።
የዓድዋ አንጸባራቂ ድል የተመዘገበው ሰው ተከፍሎለት አጥንት ተከስክሶለት፣ ደም እንደጎርፍ ፈሶለት እንጂ ዳር ቆሞ አይዞህ በማለት አይደለም።በአገራችን ሀቀኛ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት በአለት ላይ እንዲመሠረት መተኪያ የሌላት የአገራችን ብሔራዊ ጥቅም ለማስከበር ጣት መጠቋቆሙን፣ መጠላለፉን፣ ልዩነትን፣ ወንዜነትን፣ አቃቂር ማውጣቱን፣ አቅላይነትን፣ አሉባልታውን ፣ ወዘተ. ትተን የመፍትሔው አካል በመሆን የዜግነት ግዴታን መወጣት ይጠይቃል።የዓድዋ ትምህርት ሀ ሁ …. ይህ ነው ፡፡
ለአለፉት 125 አመታት ብንቆጥረው ብንቆጥረው አልገባን፣ አልገባው ያለን የታሪክ ፊደል።ለእነ ማዲባ፣ ኦሊቨር፣ ንኩሩማህ፣ ማርከስ፣ ስቲቭ ቢኮ፣ ጆሞ፣ ሙጋቤ፣ ቦብ፣ ለመላው አፍሪካ፣ ለዩናይትድ ስቴትስ መብት ተሟጋቾች ለእነ ማርቲን፣ ሮዛ፣ ጄሲ ጃክሰን፣ ማልኮም ኤክስ፣ ሉዊስ ፋራካህ፣ ኤሊጃህ ሞሀመድ፣ ኦባማ የተቆጠረው የፊደል ገበታ እኛ በአጥንት፣ በማንነት ፖለቲካ፣ በታሪክ ምርኮኝነት፣ በታሪክ ሽሚያ ተጋርዶብን፣ ዛሬም ቅኔ፣ ምስጢር እንደሆነ አለ።በዚህ የተነሳ የጋራ ህልም፣ ርዕይ፣ የታሪክ ብያኔ፣ የጋራ ጀግና፣ የጋራ ድል፣ የጋራ አገር ፣ የጋራ መሪ ፣ የጋራ መነሻና መዳረሻ፣ …፤ እንዳይኖረን አድርጓል።ግርዶሹን ለማንሳትና ከሚያለያዩን ይልቅ አንድ የሚያደርጉንን ማንነቶችን መመልከት እንድንችል በአያት ቅድመ አያቶቻችን ሰው የመሆን ኢትዮጵያዊ ንስር አይን እንመልከት፡፡
ዘመናዊት ኢትዮጵያ!
ባቡሩ ሰገረ ስልኩም ተናገረ ፣
ምኒልክ መልአክ ነው ልቤ ጠረጠረ፡፡
ከታላቁ የዓድዋ ድል ማግስት ጀምሮ የአፄ ምኒልክ፣ የእቴጌ ጣይቱ፣ የኢትዮጵያ ዝና በመላው ዓለም፣ ከአፅናፍ አፅናፍ ናኘ።እንደ ዛሬው TIME መፅሔት በጊዜው ታዋቂ የነበረው ” Vanity Fair ” የአፄ ምኒልክን ምስል ይዞ መውጣቱ፤ ከእነ ቻርለስ ዳርዊን፣ ከታላቁ አሌክሳንደር፣ ከናፖሊዮን ሳልሳዊ እኩል ታዋቂ አድርጓቸዋል።አውሮፓውያን ለልጆቻቸው «ምኒልክ» የሚል ስም እስከማውጣትም ደርሰው ነበር።የአፄ ምኒልክ ቤተ መንግሥት ከመላው ዓለም በሚጎርፉ ደብዳቤዎች ተጨናንቆ እንደነበርም የተለያዩ የታሪክ ድርሳናት መስክረዋል።
አፄ ምኒልክ በተቀዳጁት ሞገስ ተኩራርተው እጃቸውን አጣጥፈው ከመቀመጥ ይልቅ ይህን ዝናቸውን እንደ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም የዘመናዊ ኢትዮጵያን መሠረት ጥለዋል። በአጭር ጊዜ ውስጥም በአገሪቱ የመጀመሪያ የሆነውን ካቢኔአቸውን ከማቋቋም ጀምሮ 61 አዳዲስና የተለያዩ ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን፣ አሠራሮችን፣ አገልግሎቶችን ለማስተዋወቅ ችለዋል።ከእነዚህ ውስጥ የውሃ ቧንቧ፣ የኤሌክትሪክ መብራት፣ በመንገድ የሚሄድ ሰርኪስ ባቡር፣ የሀዲድ ባቡር፣ የብረት መኪና፣ አውቶሞቢል ይገኙበታል፡፡
በአፄ ቴዎድሮስ መሠረቱ የተጣለው የአገረ መንግሥት፣ የአንድነት ግንባታ ህልም፤ በአፄ ዮሐንስ እውን ሊሆን ሲል ሞትና የእርስ በእርስ የሥልጣን ሽኩቻ መንገድ ላይ አስቀርቶታል።በመጨረሻ በአፄ ምኒልክ እና በእቴጌ ጣይቱ ዋልታና ማገርነት በዓድዋ የማዕዘን ራስነት፤ በመላው ኢትዮጵያውያን ክዳንነት እውን ሊሆን ችሏል፡፡
ለ19ኛው ክፍለ ዘመን ታላቁ ዘመቻ ጀግኖች አባቶቻችንን፣ እናቶቻችንን በጥበብ፣ በማስተዋል በፊታውራሪነት መርተው አኩሪ ድልንና ነፃነትን ላቀዳጁን፤ በጊዜው ዓለም ከእነ ናፖሊዎን ሳልሳዊ እኩል ክብር፣ ሞገስ የሰጣቸውን፤ የጣሊያኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ክሪስፒን ከሥልጣን ያወረዱትን፤ የሰው ልጆች የነፃነት ምልክት የሆኑትን አፄ ምኒልክንም ሆነ እቴጌ ጣይቱን ያለልዩነት ዕውቅና ለመስጠትና ብሔራዊ ጀግና ለማድረግ በማንነት ፖለቲካ የተቀየደው እግራችን ወደኋላ ሲጎተት ስመለከት እንደዜጋ ኃፍረት ይሰማኛል።
ባለፉት 50 አመታት በአንድ ሕዝብ ላይ አነጣጥሮ የተሠራ የጥላቻና የፈጠራ ታሪክ አገራችንን የብሔራዊ ጀግኖች ሾተላይ አድርጎት ቆይቷል።ወደፊት ለምንገነባት ዴሞክራሲያዊ፣ ፍትሐዊ አገር ይሄ አሜከላ፣ ኩርንችት በጥንቃቄ መለቀም አለበት።ትርክቶቻችን በሀቀኛ፣ ተጨባጭ፣ ተጠየቃዊ፣ አመክኖአዊ እና ዘመነ ጓዴነትን (contemporaries) በተከተለ ገለልተኛና ሳይንሳዊ ሥነ ዘዴ ላይ ሊመሠረቱ ይገባል፡፡
ዓድዋ! – የኅብረ_ብሔራዊ አንድነት አርማ!
የዓድዋ ድል በሰው ልጆች ታሪክ ወሳኝ መታጠፊያ ነው። ወሳኝ ምዕራፍ ነው። የቅድመ ዓድዋዋ ዓለም በድህረ ዓድዋ እንደነበረች አልቀጠለችም። ታሪክ ተቀይሯል። ተፅፏል። ከዓድዋ ድል በኋላ በጭቆና በቅኝ ግዛት ይማቅቁ የነበሩ የሰው ልጆች ታሪክ ተቀይሯል። ቅኝ ገዥነት፣ እስከ አፍንጫው የታጠቀ የአውሮፓ ወራሪ በጥቁር ሕዝብ ሊረታ ሊሸነፍ እንደ ሚችል ዓይነ ጥላን ገፏል። አንቅቷል። ቀስቅሷል። አደራጅቷል። የአርነት ችቦን ለኩሷል። የነጭ የበላይነትን ለመሞገት ወኔ ሆኗል። እናም ዓድዋ ከፍታ ነው።
በትውልዶች ቅብብል ከሩቅ የሚታይ እንደ ሶሎዳ ባለ ግርማ የተራራ ሰንሰለት ነው። ዓድዋ የሰው ልጆችን የተዛባ ግንኙነትና ትርክት ያረቀ እንደገና የበየነ ጀግና ነው። የጥቁር ሕዝቦች ልዕልና ነው። የሰው ልጆችን ውስብስብና ትብትብ የጎርዲዮስ ቋጠሮ የፈታ ጥበበኛ ነው። የነፃነትና የእኩልነት ከፍ ሲልም የአምሳለ ፈጣሪ ፍጡርነት ምስክር ነው። ዓድዋ ማርሽ ቀያሪ ነው። ቀሰስተኛውን የጥቁርና የቅኝ ተገዥዎችን ሕዝቦች ታሪክ ወደ ነፃነትና እኩልነት ያፈጠነ።
ስለ ዓድዋ ባሰብሁና በተነሳ ቁጥር አንድ ጥያቄ ወደ አእምሮዬ ይመላለሳል። ዓድዋን ተጠቦና ተጨንቆ የሠራ መሪና ሕዝብ የጨቋኝ ተጨቋኝ የጎርዲዮስ ቋጠሮ መፍታት ተስኖት ለ122 አመታት መማሰኑና ባለበት መርገጡ ማለትም ለውጡ እስከ ባ’ተበት 2010 ዓ.ም ድረስ መቀጠሉ እንቆቅልሽ ይሆንብኝ ነበር። ደሙን አፍስሶና አጥንቱን ከስክሶ ነፃነትን ለዘረ አዳም ያለ ልዩነትና ስስት ያበረከተና ያደላደለ መሪና ሕዝብ በነፃነት ጠኔ ለዚህ ያህል ጊዜ መቆራመቱ እርስ በርሱ ይጋጭብኝ ነበር።
በነገራችን ላይ የጎርዲዮስ ቋጠሮ የአስቸጋሪ፣ የውስብስብ ነገር ተምሳሌት ሲሆን ጎርዲዮስ በዛሬዋ ቱርክ አካባቢ የፍርጂያ ንጉሥ ነበር። ቋጠሮውን ወደፊት የሚነሳ የእስያ ጠቢብ ንጉሥ ይፈታዋል የሚል ሀተታ ተፈጥሮ / myth / የነበር ቢሆንም ቋጠሮውን ታላቁ እስክንድር በሰይፍ ቆርጦታል። አልፈታውም። ከጥበብና ከማስተዋል ኃይልንና ጉልበትን መጠቀም መርጧል። የአፄ ምኒልክ፣ የልጅ እያሱን፣ የንግሥት ዘውዲቱን የኃይለሥላሴን አቆይተን፤ እንደ ታላቁ እስክንድር በሰይፍ የቆረጥነውን የታኅሣሥ ግርግር፣ የ66 አብዮት እና የትህነግ አገዛዝ ልብ ይሏል። ከትውልድ ወደ ትውልድ ሲንከባለል የመጣውን ቋጠሮ በጥበብ ስላልፈታነው ቋጠሮው ይብስ ተተባትቦ ለእኛ ቆይቶናል።
እኛ ግን ቋጠሮን እንደ ታላቁ እስክንድር በግዕብታዊነት በሰይፍ መቁረጥ ስለተጋባንና ስለለመደብን በትዕግስትና በጥበብ ቋጠሮውን ለመፍታት መታገስ ተስኖን በሰይፉ የሚቆርጥ መንግሥቱንና መለስን እንናፍቃለን። ከዚህ መርገምና አባዜ ሰብረን ካልወጣን የምንመኛትን አገር እና የምንቋምጥለትን ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ማቆም እንዳማረን ይቀራል። ይህን ስል ለውጡ ፍጹም ነው እያልሁ እንዳልሆነ ይመዝገብልኝ። ለነገሩ ፍጹም ለውጥ በዚች ምድር ተከስቶ አያውቅም። አበው እማው ነገርን ነገር ያነሳዋል እንዲሉ ስለ«ቋጠሮዎቻችን» ይህን ያህል ካልሁ ወደ ተነሳሁበት የዓድዋ የሕብረ _ብሔራዊነት ጉዳይ ልመለስ።
ከሀዲውና አሸባሪው ሕወሓት ኢትዮጵያውያንን በማንነት ከፋፍያቸዋለሁ፣ አለያይቻቸዋለሁ፣ አራርቄያቸዋለሁ እንዲሁም ጊዜውን ጠብቆ እንዲፈነዳ በኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት ያጠመድሁትን ፈንጂ አፈንድቸዋለሁ በሚል እርግጠኝነት እና የተሳሳተ ስሌትና መደምደሚያ ከጀርባ አገራችንን ቢወጋም፤ ኢትዮጵያውያን በአንድነት ዳር እስከዳር በመትመም ከሀዲውን ትህነግን በሕብረ _ ብሔራዊነት ድል ሊነሱት ችለዋል። ለዚያውም ሰራዊቱ በውድቅት ሌሊት በገዛ አዛዦቹና አባሎቹ ከተጨፈጨፈ እና ከነፍስ ወከፍ እስከ ከባድ የጦር መሣሪያው በተዘረፈ ማግስት። ከዓድዋው፣ ከካራማራውና ከሰሞነኛው አንጸባራቂ ድል ጀርባ ኅብረ _ ብሔራዊነታችንና አንድነታችን እንደ ዓድዋው አለ። ባለፉት አራት አመታት ከወደቀበት ትቢያው ተራግፎ ተነስቷል።
አኩሪው የጥቁር ሕዝቦች ድል ዓድዋ የተመዘገበባቸው በርካታ ምክንያቶቸ አሉ። ዘመን የተሻገረ የአገረ መንግሥት ልምምድ፣ የአገር ፍቅር፣ የአፄ ምኒልክና የእቴጌ ጣይቱ የመሪነት ብቃት፣ የአፄ ምኒልክ ስሪተ መንግሥት ብዝሀነትና ኅብረ_ብሔራዊነት፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን እና የኢትዮጵያ ሙስሊሞች ኅብረ _ ብሔራዊነት እና የአገናኝ ድልድይነት፣ ወዘተረፈ ዋና ዋናዎች ናቸው።
አፄ ምኒልክ የሰርጸ ድንግል የልጅ ልጅ የሆኑት የንጉሥ ሳህለሥላሴ ልጅ የንጉሥ ኃይለመለኮት ልጅ ናቸው። በዚህ ማንነት ውስጥ ከቀዳማይ ምኒልክ የሚመዘዝ አይሁድነትና ከንግሥት ሳባ የሚመዘዝ ኢትዮጵያዊነት የሚቀዳ ኅብረ _ብሔራዊነት አለ። የኦሮሞና የአማራ ማንነትም ተንሰላስሎ ሳይጣላ በአንድ ላይ አለ። አፄ ምኒልክ አማራና ኦሮሞ ሲሆኑ እቴጌ ጣይቱ የኦሮሞና የእስልምና የኋላ ማንነት አላቸው። የንጉሡን ሹማምንት ብንመለከት፤ ሼህ ሆጅሌ ጉሙዝ/በርታ፣ አፈ ንጉሥ ነሲቡ ኦሮሞና አማራ፣ ፊትአውራሪ ገበየሁ የአብቹ ኦሮሞና የቡልጋ አማራ፣ ፊታውራሪ ሀብተጊዮርጊስ ዲነግዴ ኦሮሞና ጉራጌ፣ ደጃዝማች ባልቻ ሳፎ ኦሮሞና ጉራጌ፣ ወዘተረፈ ሁለትና ከዚያ በላይ የጎሳ ማንነት ነበራቸው።
እንግዲህ የአፄ ምኒልክ መንግሥት ኅብረ_ብሔራዊ ከነበረ፤ ወዶ ገቡ 100ሺህ የገበሬ ጦሩም የዚህ ብዝኃነትና ኅብረ _ ብሔራዊነት ድምር ውጤት መሆኑ አያጠያይቅም። ፕሮፌሰር ባሕሩ ዘውዴ ፣«የኢትዮጵያ ታሪክ 1847_1983» ፤ በተሰኘው መጽሐፋቸው ገጽ 85 ላይ ፣ «የምኒልክ ጦር…ድፍን ኢትዮጵያን የወከለ በመሆኑም ልዩ ትኩረት የሚሰጠው ነበር።
ለንጉሠ ነገሥቱ ነፃነትና የአገር ድንበርን የማስከበር ጥሪ ጦር ያልላከ የአገሪቱ ክፍል አልነበረም።» እንዳሉት በዚህ አኩሪ ድል ያልተሳተፈ ጎሳ አልነበረም። ለዛሬ በዚህ ላብቃ፤ እንኳን ታላቁ የሰው ልጆች ሁሉ የነፃነት የድል በዓል የሆነው ዓድዋ 126ኛ አመት «ደረሰባችሁ፤ ደረሰብን»።እኛ እዚያ ከፍታ ላይ መድረስ አይደለም ከማንነት ፌርማታችን ገና አልተንቀሳቀስንም፡፡
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን የካቲት 25/2014