የዛን ጊዜው በመማጸኛ ከተማው መቐሌ የመሸገው የዛሬው አሸባሪ ሕወሓት፣ የታሪካዊ ጠላቶቻችን ተላላኪ ሆኖ አገራችንን ለማፍረስና ለመበተን እንደ ልማዱ ተልዕኮ ተቀብሎ በሰብዓዊ ማዕበል ህጻናትን በአሽሽ እያሳበደ ነፍሰ ጡር ሴቶችን አረጋውያንን አካል ጉዳተኞችን መነኮሳትንና የሀይማኖት አባቶችን በጦርነት ማግዷል። ያለ የሌለ ኃይሉን በዋግ ኽምራ በአበር ገሌ በወሎ በራያ በጎንደር በወልቃይት ጠገዴና ጠለምት እንዲሁም በአፋር ክልል ትንኮሳና ጦርነት ከፍቷል። በሰሜን ዕዝ ላይ ታሪክና ትውልድ ይቅር የማይለው ክህደትና ጭፍጨፋ ፈጽሟል። ኢትዮጵያን ለማፍረስ ሲኦልም ቢሆን እወርዳለሁ ብሎ ኢትዮጵያን ለማፍረስ የሚችለውን ያህል የጥፋት በትሩን ሰንዝሯል።
ይህ የሽብር ቡድን፣ ግብጽና ሱዳን ኢትዮጵያን እንዲወርሩ ተንበርክኮ የሚማጸን፤ የአሜሪካንንና የምዕራባውያንን ጣልቃ ገብነት ጫና የኢኮኖሚ ማዕቀብ የሚለማመን ፤ አገርን በሀሰተኛ መረጃ የሚያጠለሽ፤ 110 ሚሊዮን ሕዝብ የባሕር በር አልባ ያደረገ ፤ ከዛድባሬ ወራሪ ጎን የተሰለፈ፤ አገርን ለ27 አመታት በመዝረፍ እርቃን ያስቀረ፤ ኢትዮጵያን አምርሮ የሚጠላ፤ ሌሎችንም አያሌ የክህደት ተግባራትን የፈጸመ ነው።
የሽብር ቡድኑ፣ የዛሬ ሁለት አመት የኢትዮጵያ ታላቁ የህዳሴ ግድብ ተሽጧል እያለ ሲያናፋ፣ ኢትዮጵያውያን ግን የመጀመሪያውን የውሃ ሙሊት ሐምሌ 15 ቀን 2012 ዓ.ም 4 ነጥብ 9 ቢሊዮን ሜትር ኩብ ውሃ እንዲይዝ ተደርጓል። ሁለተኛው የውሃ ሙሊት ደግሞ ባለፈው ሐምሌ 12 ቀን 2013 ዓ.ም 13 ነጥብ 5 ቢሊዮን ሜትር ኩብ ውሃ በመያዝ ተጠናቋል። ሟርተኛውና አሸባሪው ሕወሓት ተሽጧል ያለው ይህ አገራዊ ግዙፍ የብርሃን እሸት የምስራች እንካችሁ ብሏል። ካለፈው የካቲት 13 ቀን 2014 ዓ.ም ጀምሮ ደግሞ በአንድ ተርባይን ብቻ ኃይል ማመንጨት ጀምሯል። የሁለተኛው ተርባይን ገጠማም የተጠናቀቀ ስለሆነ በቅርቡ ተመሳሳይ ኃይል ያመነጫል ተብሎ ይጠበቃል። የቀሪዎቹ ተርባይኖች ገጠማ፤ የግድቡ ግንባታና የኤሌክትሮ ሜካኒካል ስራዎችም ተጠናክረው እየሄዱ ነው።
በክቡር ጠቅላይ ሚንስትር አመራር ግድቡ ገጥመውት የነበሩ ስር የሰደዱ ብልሹ አሰራሮች፣ ሙስናና ደካማ የኮንትራት አስተዳደር ተለይተው የእርምት እርምጃ መወሰዱ ታላቁን የኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ከክሽፈትና ከለየለት ውድቀት ከመታደግ አልፎ ለኢትዮጵያውያን እራትና መብራት ሊሆን እሸት አቅምሷል። የግብፅን የሱዳንን የአሜሪካና የምዕራባውያንን የአረብ ሊግን አለማቀፍ ዲፕሎማሲያዊና ፖለቲካዊ ጫናን በጥበብና በማስተዋል በመቋቋም እና ግብፅ የግድቡን ጉዳይ የዓለም የደህንነትና የሰላም ስጋት አድርጋ ለማሳየት መጀመሪያ ራሷ በኋላ በአረብ ሊግ አይዞሽ ባይነት ቱኒዚያን በመጠቀም ጉዳዩን ከአፍሪካ ሕብረት በማውጣት ወደ መንግስታቱ ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት አጀንዳነት ለማሳደግ ያደረገችው ጥረት አገራችን በጥብቅ ዲፕሎማሲያዊ ዲስፕሊንና በጥበብ በተመራ አለማቀፍ ግንኙነት አገራትን ከጎኗ በማሰለፍ የተደገሰላት ደባ እንዲከሽፍ ከማድረጓ ባሻገር የግድቡ ጉዳይ የተፋሰሱ አገራትና የአፍሪካ ሕብረት እንጂ የመንግስታቱ ድርጅት አለመሆኑን ማረጋገጥ ችላለች።
ድርድሩም ለሁለተኛ ጊዜ ወደ አፍሪካ ሕብረት ተመልሷል። ጣልቃ ለመግባት አሰፍስፈው የነበሩ ምዕራባውያን እርማቸውን እንዲያወጡ አድርጋለች። ሆኖም ዛሬም ሆነ ጥንት ግብፅ አልተኛችልንም። አባይን ከመነሻው ለመቆጣጠር ከ11 ጊዜ በላይ ልትወረን ልታስገብረንና ቅኝ ልትገዛን ሞክራ እንዳልተሳካላት የታሪክ ድርሳናት ያትታሉ። በዲፕሎማሲው መድረክ ብትረታም በሱዳን አማካኝነት የውክልና ጦርነት ከፍታ መሬታችንን አስወርራለች። አገርን ለከዱ ጡት ነካሾች የገንዘብ የጦር መሳሪያ የዲፕሎማሲና የፖለቲካ ድጋፍ በማድረግ አገራችንን ወደ ለየለት ቀውስና ትርምስ ለመክተት ቀን ከሌት እየሰራች ነው። ይህን የተገነዘቡ ኢትዮጵያውያንም በአንድነት አገራቸውን ከውስጥ ተላላኪዎችና ከውጭ ጥቃት ለመከላከል ቀፎው እንደተነካ ንብ በአንድነት ተነስተዋል።
ግድቡ በአሁኑ ሰዓት ከ18 ነጥብ 4 ቢሊዮን ሜትር ኩብ በላይ ውሃ በመያዝ ራሱን መከላከል የሚችልበት ደረጃ ላይ ደርሷል። ግብፅ ለዘመናት ኢትዮጵያ ሰላም ሆና አንድነቷ የሚጠናከርና ልማቷም የሚፋጠን ከሆነ አባይን ጨምሮ ገና የውሃ ሀብቷን ታለማለች በሚል በስጋት ላይ ያነጣጠረ ስጋት ከውስጥ ተላላኪዎቿ ጋር በመሆን ኢትዮጵያውያንን ለመበታተን ሰርታለች። በወንዝ በጎጥ የተከፋፈለች ደካማ አገር እንድትሆን ሌት ተቀን ሰርታም በተወሰነ ደረጃም ተሳክቶላታል። ዛሬም አሸባሪውን ሕወሓት ሸኔንና ሌሎች ቅጥረኛ ምንደኞችን ተጠቅማ ከውስጥ እየወጋችን ነው። ሆኖም የግብፅና የተላላኪዎቿ የቀን ቅዠት በጀግኖች ልጆቿ ይመክናል። እየመከነም ይገኛል።
አይደለም ዛሬ ሁለተኛ ዙር ግድባችንን ሞልተን፣ የብርሃን እሸት ቀምሰን፤ ያለአንዳች ኮሽታ ብሔራዊ ምርጫ አካሂደንና በሚያስገርም ሁኔታ በአገራችን ተደቅኖ የነበረን ቀውስ ቀልብሰን፤ ከሁለት አመት በፊት በሴራ ፖለቲካ፣ በተላላኪውና በባንዳው የትህነግ ገዢ ቡድንና ተባባሪዎች ደባ በየእለቱ ቅርጹንና ይዘቱ እየቀያየረ በሚቀፈቀፍ ቀውስ መሀል ሆነን አንደኛውን የውሃ ሙሊት አካሂደናል። ከዚህ በኋላ የሚቀሩን ሙሊቶችም ያለ ምንም ስጋት ይከናወናሉ። በዚህም ቅኝ ካለመገዛት ጋር ብቻ ተያይዞ የነበረውን ነጻነትና
ሉዓላዊነት በኢኮኖሚያዊ በብልፅግና ለመድገም መስፈንጠሪያ ሰሌዳ (ስፕሪንግቦርድ) በመሆን በድህነትና በተመፅዋችነት አንገታቸውን ደፍተው የነበሩ ዜጎች አንገታቸውን ቀና አድርገው በኩራት እንዲራመዱ የሚያደርግ ብሔራዊ (ፍላግሺፕ)ፕሮጀክት ባለቤት መሆን ተችሏል።
ነጋድራስ ገብረህይወት ባይከዳኝ እንዳሉት በድህነትና በኋላ ቀርነት የሚማቅቅ ሕዝብ የተሟላ ሉዓላዊነት ሊኖረው አይችልምና። ስንዴ እየለመኑ፣ እየተመጸወቱ ሉዓላዊነቷን ያላስደፈረች ፤ በነጻነት ታፍራና ተከብራ የኖረች ብሎ መመጻደቅን ድሉን ሙሉኡ አያደርገውም።
መቼም አሸባሪው ትህነግ ለዘረፋና ለስልጣን ሲል የአገሪቱን ብሔራዊ ጥቅም አሳልፎ በመስጠትና በሌብነት ጥርሱን የነቀለበት ስለሆነ እሱ እንደሚያደርገው ግድቡ ተሸጧል ቢል የሚያስገርም አይደለም። እሱ ሽጦት ስለነበረ አይደል ለአጠቃላይ ክሽፈት አንድ ሐሙስ ቀርቶት እያለ የለውጥ ኃይሉ ደርሶ የታደገው። በርሀብ ለተጎዱ ትግራዋይ ተልኮ እንደነበረው ስንዴ ከአንዴም ሁለት ሶስቴ ሽጦት የነበረውስ እሱ ራሱ ሕወሓት ነው። እንጨት ሽጣ ከልጆቿ ጉሮሮ ቀምታ መቀነቷን ፈታ የሰጠችውን ገንዘብ ከመስረቅ በላይ ግድቡን መሸጥ ምን አለ። ተራ የመጠጥ ውሃ ኤሌክትሮ ሜካኒካል እንኳ በቅጡ ገጥሞ ለማያውቅ በብልሹ አሰራርና በሙስና ለበሸቀጠ ተቋም ያለ ጨረታ ከመስጠት በላይ ግድቡን መሸጥ ምን አለ።
ያው ሁላችን እንደምናውቀው የትህነግ እፉኝት ቡድን ለፖለቲካዊ ጥቅምና ስልጣን ሲል ወላጅ እናቱንም ሆነ አገሩን እንደ አስቆርቱ ይሁዳ ከመሸጥ አይመለስም። ለትህነግ ፖለቲካ ማለት ብሔራዊ ጥቅምን አሲዞ መገበያየት፣ የንግድ ውል መፈጣጠም (Transactional) ነው ። በዚህ የልቡና ውቅር (ማይንድሴት) ነው ታላቁ የህዳሴ ግድብ ተሽጧል ሲል የነበረው ። በፈጸመው ግፍና ክህደት በሰራው ስህተት በተናገረው ውሸት ወዘተረፈ ጸጸት የማያውቅና ያልፈጠረበት ሆኖ እንጂ ዛሬ ላይ በጸጸት ጸጉሩን በነጨ። እሱ እቴ ይገረማችሁ ብሎ ኢትዮጵያን ለማፍረስ ሲኦልም ቢሆን እወርዳለሁ ብሎ ቁልቁለቱን ተያይዞታል።
ውሎ ሳያድር የአገሪቱን ብሔራዊ ጥቅም አሳልፎ ሽጦ በቀጣናው ጂኦፖለቲካዊ ስፍራዋ መናኛ መሆኑን ሲገነዘብና ለአገዛዙም አደጋ መደቀኑን ሲረዳ የፈፀመውን ታሪካዊ ስህተት ለማጣፋትና ለማወራረድ አገራችን የአሜሪካና የምዕራባውያን የቀጣናው አለማቀፍ የጸረ ሽብር አጋሯ እንድትሆን እጇን የፊጢኝ አስሮ አስረክቧል። በበርካታ ኢትዮጵያውያን መስዋዕትነት አምባገነናዊ አገዛዙ በአሜሪካ፣ በአለማቀፍ ተቋማትና በምዕራባውያን ዘንድ ሞገስን ከማግኘት ባሻገር በቢሊዮን ዶላሮች የሚገመት ብድርና እርዳታ በመቀላወጥ የአገዛዙን እድሜ ማራዘም ችሏል።
የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ወደ ስልጣን መምጣት ተከትሎ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ በ”አሜሪካ ትቅደም !” መሰረት ላይ በመቀረጹ እና ትራምፕ ከአለማቀፍ የጸረ ሽብር ዘመቻ ግዕብታዊ ማፈግፈግ በማድረጉ የተነሳ እንዲሁም ፊቱን ወደ አሜሪካ የውስጥ ጉዳይ በማዞሩ የኢትዮጵያ ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታም ሆነ ጂኦፖለቲካዊ ስፍራ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ መፍጠሩ አልቀረም። በክቡር ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አሕመድ የሚመራው የለውጥ ኃይል ወደ ኃላፊነት መጥቶ ፖለቲካዊ ምህዳሩን ከፈት ከፈት በማድረጉ ፤ ከኤርትራ ጋር የሰላም ስምምነት በመፈራረሙና ከ20 አመታት በኋላ እርቅን በማውረዱ፤ ክቡር ጠቅላይ ሚንስትርም በሰላም የኖቤል ተሸላሚ በመሆናቸው አገራችን በአለማቀፉ መድረክ እንደገና እንድታንሰራር አስችሏል። (መልሶ በታሪካዊ ጠላቶቻችንና በተላላኪዎቻቸው ሀሰተኛ መረጃና ሴራ ለማጠልሸት ሰፊ ዘመቻ የተደረገ ቢሆንም።)
ሆኖም መጀመሪያ ሁለተኛው የሕዳሴው ግድብ ውሃ ሙሊት ፤ አሁን ደግሞ ኃይል ማመንጨት መጀመሩ የቀጣናውን ጂኦፖለቲክስ እንደ አዲስ በይኖታል። የግብፅን የውሃ ዲፕሎማሲና ፖለቲካም ከንቱ አድርጎታል። ለዚህ ነው ዛሬ አሸባሪውን ሕወሓት ተጠቅማ አገራችንን ለመበቀል ሌት ተቀን እየሰራች ያለችው። ሱዳንን ግፊ የምትለው። ከ40 ሺህ በላይ ዜጎቻችን ከሳኡዲ አረቢያ መብታቸው ተገፎና ሰብዓዊ ክብራቸው ተዋርዶ እንዲወጡ ያሴረችው። የቀሩት በሳውዲ ማጎሪያዎች ታስረው እየማቀቁ ያሉት።
እንደለመደው አገርን ለመሸጥ ተስማምቶ በግብፅ የእጅ አዙር የዲፕሎማሲና የፖለቲካ ድጋፍ፤ በምዕራባውያንና አለማቀፉ ማኅበረሰብ ጫና እንዲሁም እንዳሻቸው በሚጠመዝዟቸው ሚዲያዎችና የሰብዓዊ መብት ተቆርቋሪ ነን ባዮች ወከባ አፈር ልሶ የተነሳው አሸባሪው ሕወሓት፤ አንድ ጊዜ ተሽጧል ሌላ ጊዜ ለፖለቲካዊ ጥቅም ተለውጧል እያለ የውሸት መአት ሲነዛበት የኖረው የኢትዮጵያ ታላቁ የህዳሴ ግድብ ከአንድም ሁለት ጊዜ ውሃ በመያዝ ወደ 16 ቢሊዮን ብር ከድሃው ጓዳቸው ያዋጡለትን ዜጎች ልብ በመግዛት ለሌላ ዙር ድጋፍ አነሳስቷቸዋል።
አገራችን ላለፉት 30 አመታት አጥታው የነበረውን የቀጣናውን ጂኦፖለቲካም መልሳ እንድትረከበው አስችሏል። የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ፤ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የመጀመሪያው ምዕራፍ ኃይል የማመንጨት ሥራ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ጉባ ላይ ባስተላለፉት መልዕክተ አኮቴት መጣጥፌን ልቋጭ።
መልዕክተ አኮቴት
ያለፍንበትን ሁለት ሦስት ዓመታት እና ዛሬ የሆነውን ነገር ስመለከት የፈጣሪ ቸርነት እና እርዳታ በእጅጉ ያስደምመኛል። ስለሆነም ንግግሬን የማደርገው በአብዛኛው በምስጋና ላይ ብቻ ያተኮረ ይሆናል። በመጀመሪያ እጅግ የተከበራችሁ የሥራ ኃላፊዎች፣ አፄ ኃይለሥላሴን እንዳመሰግናቸው እንዲፈቀድልኝ እጠይቃለሁ። አፄ ኃይለሥላሴ፣ በዚያን ጊዜ ማድረግ የሚያስቸግርም ቢሆን፤ መልካም ሃሳብ፣ መልካም ዘር ለልጆቻቸው ማቆየትና ቀጣዩ ትውልድ ሊሠራው እንደሚችል አስበው በዚህ ቦታ ላይ ይሄንን ፕሮጀክት ዲዛይን አሠርተው ቀጣዩ ትውልድ ይገነባዋል የሚል እጅግ ትልቅ ራዕይ በመሰነቃቸው እና ያም ሕልም በልጆቻቸው እውን ስለሆነ ክብር እና ምስጋና ይገባቸዋል። ከእሳቸው በመቀበል ፕሮጀክቱን እውን ያደረጉ መሪዎችን ፣ ሚኒስትሮችን፣ ስራ አስኪያጆችን፣ ባለሙያዎችን፣ ሰራተኞችንና ሌሎች የኅብረተሰብ ክፍሎችን አመስግነው መላው ኢትዮጵያውያን በአንድነት እንዲቆሙ ጥሪ አቅርበዋል።
አገራችን ኢትዮጵያንና ሕዝቧን ፈጣሪ አብዝቶ ይባርክ !
አሜን።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን) fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን የካቲት 17/2014