አሸባሪው የህወሓት ቡድን ሰኔ 21 ቀን 2013 ዓ.ም መንግሥት ለሰብዓዊነት ቅድሚያ ሰጥቶ ከትግራይ ክልል መከላከያ ሠራዊቱን ማውጣቱን ተከትሎ ወደ አማራና የአፋር ክልሎች ለወረራ ተሰማራ:: በዚህም ወረራ እግሩ በደረሰባቸው አካባቢዎች ሁሉ የቡድኑን አረመኔያዊነት ከገለጠባቸው በሰው ላይ ከፈጸመው ግፍ (ግድያ፣ አስገድዶ መድፈር፣ ማፈናቀልና ሌሎች ሰብዓዊ ጥቃቶች) ባለፈ፤ ሰፊ የንብረት ውድመትና ዘረፋ ፈጽሟል:: በዚህም ሆስፒታሎች፣ ትምህርት ቤቶች፣ ኢንዱስትሪዎች እና ሌሎችም ማሕበራዊና ኢኮኖሚያዊ መሰረተ ልማቶች ይገኙበታል:: በዚህም በአፋርም ሆነ በአማራ ክልሎች ወረራ በፈጸመባቸው አካባቢዎች ሁሉ ይሄንኑ ከግለሰብ ንብረት ጀምሮ፣ የመንግሥት የሆኑትን የሕዝብ መገልገያ መሰረተ ልማቶችን በስፋት አውድሟል::
የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ከሐምሌ ወር 2013 ዓ.ም ጀምሮ በትግራይ ክልል የነበረው ጦርነት ወደ አማራ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች ከመስፋፋቱ ጋር ተያይዞ በህወሓት ኃይሎች የተፈጸሙ የሰብአዊ መብት እና የሰብአዊነት ሕግ ጥሰቶችን በተመለከተ ያደረገውን ምርመራ ሪፖርት ይፋ ማድረጉ ይታወሳል:: በሪፖርቱም የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን የምርመራ ቡድን መረጃዎችን ባሰባሰበባቸው በህወሓት ኃይሎች ቁጥጥር ስር በነበሩ የአማራ ክልል ከተሞች እና የገጠር ስፍራዎች ሁሉ ሰፊ የሆነ ዘረፋ እና የንብረት ውድመት ተፈጽሟል።
የህወሓት ታጣቂዎች በደረሱባቸው ከተሞች የግል መኖሪያ ቤቶችን፣ ባንኮችን፣ የብድርና ቁጠባ ማሕበራትን ጨምሮ የግለሰብ እና የድርጅቶች የንግድ ተቋማትን፣ ሆስፒታሎችን፣ የጤና ጣቢያዎችን፣ ትምህርት ቤቶችን፣ የወረዳ እና የቀበሌ የሕዝብ አስተዳደር ተቋማት ቢሮዎችን እና የመብራት እና የቴሌኮም አገልግሎት መሰረተ ልማቶች በስፋት ዘርፈዋል፤ አውድመዋል። በአንዳንድ ከተሞች የመንግሥት ኃላፊዎችን፣ የሚሊሻ፣ ፋኖ እና የመከላከያ ሠራዊት አባላት እና የቤተሰቦቻቸው መኖሪያ ቤቶችን ለይተው መዝረፋቸው፣ ማቃጠላቸው እና ማውደማቸው ሲረጋገጥ በሌሎች ስፍራዎች ደግሞ ዘረፋው እና የንብረት ውድመቱ በአጠቃላይ ሲቪል ነዋሪዎችና ተቋማትን ኢላማ ያደረገ ነው።
ሕፃናትን፣ አረጋውያንንና ንፁሃን ወጣቶችን በግፍ ተገድለው በጅምላ በትምህርት ቤቶች ውስጥ ተቀብረዋል:: ንጹሃን ዜጎን በየበራቸው ተገድለዋል:: እናቶች በልጆቻቸው ፊት ተደፍረዋል:: ሴት ልጆች በአባቶቻቸው ፊት የግፍን ጽዋ ቀምሰዋል:: በአጠቃላይ ሽብርተኛው የህወሓት ቡድን ኢትዮጵያን አንገት ለማስደፋት ብዙ አስነዋሪ ድርጊቶችን ፈጽሟል:: ነገር ግን ሁሉም በመተባበር በገባባቸው ቦታዎች እንዲቀበር ተደርጓል::
ሽብርተኛው ቡድን በገባባቸው አካባቢዎች ተጠራርጎ እንዲወጣ የተጠናከረ ዘመቻ በመከፈቱ በተወሰነ ጊዜያት ከሁለቱም ክልሎች ተጠራርጎ ወጥቷል:: ህልውና ዘመቻው የመጀመሪያ ምዕራፍ ተጠናቆ በሽብርተኛው የህወሓት ቡድን ተይዘው የነበሩ ቦታዎችም በመንግሥት ቁጥጥር ስር ሆነዋል:: ሽብርተኛው የህወሓት ቡድን ያወደማቸውን ትምህርት ቤቶችና የህክምና መስጫ ተቋማት መልሶ ለማቋቋም የተጀመሩ ሥራዎችን ማስቀጠል ደግሞ የሁሉም ተግባር መሆን አለበት:: ለዚህም እንዲረዳ መንግሥት በቅርቡ የመልሶ ማቋቋሚያ በጀት ማዘጋጀቱ እየተሰማ ነው::
በአማራ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች የወደሙ ንብረቶችና መኖሪያ ቤቶች መልሰው እንዲያገግሙ ለማድረግ በክልሉ ደረጃ የተጠና እቅድ መንደፍ ይጠይቃል:: ምክንያቱም ክልሉ ከደረሰበት ወረራና ውድመት ወደ ኋላ ተጉዞ የነበሩትን ሁኔታዎች እንዲያሰላስል ስለሚያደርጉት ነው:: ክልሉ መልሶ ወደ ነበረበት እንዲመለስ ረጅም ጊዜ የሚፈጅ ቢሆንም በተጠና መልኩ ሥራዎች ከአሁኑ መጀመር አለባቸው:: መኖሪያ ቤትና ሌሎች ንብቶቻቸውን ያጡ ነዋሪዎችም መልሶ ለማቋቋምም የተጠናከረ አመራር እንደሚያስፈልግ እሙን ነው::
የአማራና የአፋር ክልሎችን መልሶ ለማቋቋም የተለያዩ ድጋፎች እየተደረጉ ናቸው:: እነዚህ ድጋፎች ትምህርት ቤቶችን፣ ሆስፒታሎችንና የመንግሥት አገልግሎት መስጫ ተቋማትን መልሶ ሥራ ለማስጀመር እገዛ ያደርጋሉ:: በአዲስ አበባ ይሁን በሌሎች ክልሎች የሚገኙ የመንግሥት ተቋማት የማይጠቀሟቸውን ንብረቶች አሰባስበው ልከዋል:: ሰራተኞቻቸውም ልብሶችን፣ የንፅህና መጠበቂያዎችንና ሌሎች ደራሽ የምግብ ፍጆታዎችን በተጎዱ አካባቢዎች በመሄድ ድጋፍ አድርገዋል:: እዚህ ጋር መዘንጋት የሌለበት ግን በእርዳታ መልክ የሚመጡ ንብረቶችም ሆኑ ገንዘቦች የታለመላቸው ቦታ መድረሳቸው ሊረጋገጥ ይገባል:: ምክንያቱም በክልሎቹ የደረሰው ውድመት የከፋ እንዲሆን ካደረጉት ምክንያቶች አንዱ የባንዳ አመራሮች መብዛት መሆኑ አይዘነጋም::
ሽብርተኛው ሕወሓት ወረራ ባካሄደባቸው ቦታዎች የራሱ ሰዎችና ባንዳ አመራሮች ተጨባጭ መረጃዎች ስላደረሱት በቀላሉ ውድመት እንዲፈጽም አግዞታል:: ከዚህም በዘለለ ወረራ በተካሄደባቸው ቦታዎች ውስጥ የሽብርተኛው ህወሓት ደጋፊና አባላት ዘግናኝ የሆነ ኢ-ሰብዓዊ ድርጊት መፈፀማቸው ተጎጂዎች ላይ የሥነ ልቦና ጫና ፈጥሯል:: ይህንንም ለማከም ከፍተኛ ሥራ ይጠይቃል::
የፌዴራል መንግሥት በሽብርተኛው ህወሓት ቡድን ላይ ድል ከተቀዳጀ በኋላ በሌሎች ቦታዎች የጦርነት አዝማሚያዎች እየታዩ ነው:: ሽብርተኛው የህወሓት ቡድን መሸነፍ የማይዋጥላቸው በመንግሥት መስሪያቤቶችም ሆነ በሌሎች ቦታዎች ላይ የሚገኙ የትግራይ ተወላጆች ላይ ትኩረት ሊደረግ ይገባል:: እዚህ ጋር ማስተዋል የሚገባው በመንግሥት መስሪያ ቤት ውስጥ ሆነው አጥፊውን ቡድን ሲደግፉና ሲያበረታቱ የነበሩ ሰዎች እንደነበሩ መዘንጋ የለበትም:: ተልዕኮ ተቀብለውም የሽብር ስራዎች ሊያከናውኑ የሚችሉበት ሁኔታም ሊፈጠር ስለሚችል ቀደም ተብሎ የማጥራት ሥራው ቢጀመር መልካም ነው::
ከጦርነቱ በኋላ የተረጋጋ መንግሥት መፍጠር ካልተቻለ ለአገር አንድነት አደጋ ከመሆኑ በላይ ሌሎች አጥፊ ቡድኖች እንዲፈጠሩ ምክንያት ሊሆን ይችላል:: በሌላም በኩል እከሌ ብሄር ተሸናፊ በመሆኑ በአገሪቱ ጉዳይ አገባውም ወደሚል ድምዳሜ እንዳንደርስ ከወዲሁ ትኩረት የሚፈልግም ጉዳይ ነው:: በጦርነቱ ምክንያት በአማራና በአፋር ክልል የወደሙ ንብረቶችን መተካትና ሰብዓዊ ድጋፍ ማድረግ የሁሉም ክልል ግዴታ ሊሆን ይገባል::
ከጦርነቱ በኋላ ሌላው ትኩረት ሊደረግ የሚገባው በአማራና በአፋር ክልል በሚገኙ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ እየተማሩ ለነበሩ ተማሪዎች ነው:: በዚህ ዓመት ለመመረቅ ዝግጅት ያደረጉ ተማሪዎች እጣ ፋንታ ፈጣን በሆነ መንገድ ሊመለስም ይገባል:: በተጨማሪም በክልሉ የሚገኙ መደበኛ ተማሪዎችም ወደ ትምህርት ገበታቸው የሚመለሱበት ሁኔታም መመቻቸት አለበት:: በአሁኑ ወቅት በአማራና በአፋር ክልል ሊደረጉ ለሚገቡ ሥራዎች በተለይ ሰላም ለማስከበር፣ ሰብዓዊ ድጋፍ ለማድረግ እንዲሁም ዘላቂ አመራር ለመፍጠር ሁሉም ክልሎች በተቻላቸው አቅም ድጋፍ ሊያደርጉ ይገባል::
አምኃየስ መርዕድ
አዲስ ዘመን የካቲት 17/2014