እንደ መደላድል፤
ሥነ ምግባር ለሰው ልጆች ብቻ የተሰጠ የተፈጥሮ ጸጋ ሲሆን፤ “አድርግ” እና “አታድርግ” በሚሉ ጽኑ ማሕበራዊና ኅሊናዊ ሕግጋት ላይ የተመሠረተ የጋራ መርህ ነው። ሥነ ምግባር አንድም የሞራል ሕግጋት ማጥኛ ዘዴ፤ ሁለትም የሰብዓዊ ፍጡር “የልክነት ውበት” መገለጫ ተፈጥሯዊ መርህ ነው። “ሥነ”፡- ሳይንስም ነው፤ በአንጻራዊ መልኩም የውበት ልክ መገለጫ እየተባለ የሚነገርለትም በዚሁ መንትያ ባህርይው ምክንያት ነው።
ማንኛውም ማኅበረሰብ በሃይማኖቱ፣ በባህሉ፣ በትውፊቱ፣ በወጉና በልማዱ ዐውዶች ላይ ተመስርቶና በብዙኃን ይሁንታ በጸደቀ ወይንም ከትውልድ ትውልድ በውርስ ተላልፎለት የሚገዛላቸው በርካታ የሥነ ምግባር ህግጋት ሊኖሩት ይችላሉ። “ሊኖሩት ይችላሉ” ብቻም ሳይሆን ሰብዓዊ ማንነቱና የጀማው ግፊት ግድ ይሉታል ብሎ ማጠናከሩ ይበልጥ የተሻለ ይሆናል። ሕግጋቱ አብዛኛውን ጊዜ በባህርያቸው ቋሚነትና ዘላቂነት ያላቸው መሆኑንም ልብ ይሏል።
ከዚሁ ማሕበራዊና ጀማዊ የሰላማዊ አብሮነት ማጠናከሪያና ማጋመጃ ሕጋግት ጎን ለጎን የሰብዓዊ ፍጡራን ኅሊና ድርሻውና ሚናው ላቅ ያለ መሆኑም ሊዘነጋ አይባም። ኅሊና እያንዳንዱ ግለሰብ በተፈጥሮ የታደለው የሥነ ምግባር ልኬት መመዘኛ (Moral faculty) እና ብይን ሰጭ ዳኛ ነው። “ኅሊና ከሰዋዊ ማንነታችን ጋር ተቆራኝቶ የሚኖር የፈጣሪ ወኪል ነው” መባሉም ስለዚሁ ነው። ለመደበኛ መንግሥታዊ ሕግጋትና ማኅበረሰቡ በአሜንታ ለተቀበላቸው የቡድን መመሪያዎችና ትዕዛዞች ግለሰቦች ወይንም ቡድኖች አሻፈረኝ አንገዛም ወይንም መከራከሪያ ስላለን አንቀጣም ወይንም አንወቀስም ብለው ማመጽ ወይንም መሟገት ይችሉ ይሆናል። ከኅሊና እውነታ ማፈንገጥና ማመጽ ግን በፍጹም የሚሞከርም ሆነ የሚቻል አይደለም።
“ይህ ጉዳይ ትክክል ነው፡- መፈጸም ወይንም ማድረግ አለብኝ፤ ያኛው ጉዳይ ደግሞ “ፍጹም” ስህተት ስለሆነና አግባብም ስላይደለ ማድረግም ሆነ መፈጸም አይገባኝም።” በሚል ውስጣዊ ብያኔ አቋም እንድንይዝ የሚያስገድደን ያለ ማንም የውጭ ጣልቃ ገብነት ኅሊናችን ብቻ ነው። እያንዳንዱ ነፍስ አወቅና ጤነኛ ግለሰብ ኅሊናውን የሚያደምጠውና የሚታዘዘው ቸርና ርሁሩህ ስለሆነ ወይንም ኅሊናዬን ማድመጥ አለብኝ ብሎ ስለሚወስንና ስለ ወደደ ሳይሆን ትዕዛዙን ለማድመጥ የሚገደደው ግድ ስለሆነበት ነው።
ኅሊናን ማድመጥ፣ አድምጦም መታዘዝ ትሩፋቱ ሰላምና የውስጥ እርካታ የሚያስገኝ ታላቅ የፈውስ መድኃኒትም ብልሃትም ነው። ከኅሊና ጋር መታገልም ሆነ መቋሰል ውጤቱ መልካም እንደማይሆን የሚያረጋግጥልን ውጫዊ ኃይል ሳይሆን ተፈጥሯችን ራሱ ነው። ኅሊና ከስሜት ጋር ያለው ግንኙነት እንደ አንድ ሳንቲም አንዱ የአንዱ ግልባጭ ነው ብሎ ለማረጋገጥ ባይቻልም በስሱና በድርበቡ የሚገናኙበት ቀጭን ክር ግን መኖሩን መካድ አይቻልም። ስሜት ይዋዥቃል፣ ይደለላል በተለያዩ ምክንያቶችም ግራ ሊጋባ ይችላል። ኅሊና ግን እንደዚያ አይደለም። በተፈጥሯዊ ሥሪቱ ቋሚና ጽኑ ስለሆነ ልዩነታቸው የሚያርፈው እዚህ ላይ ነው።
ለሰብዓዊነት የጋራ አካፋይ የሆኑ ዓለም አቀፍ የሥነ ምግባር እሴቶች፤
አንድ አገር የተለያዩ ሃይማኖቶችን፣ ባህሎችን ወጎችንና ልማዶችን ወዘተ. በጋራ አቅፎ እንደሚኖር ይታወቃል። ልዩነቱ እንደተጠበቀ ሆኖ ግን በጠባቡ አገራዊ ጂኦግራፊ ክልልም ሆነ በሰፊዋ ዓለማችን ውስጥ በአብዛኛው የጋራ ከሚሰኙት የሥነ ምግባር እሴቶች መካከል ለእውነት መቆም፣ በታማኝነት መጽናት፣ ደግነትን መለማመድ፣ ለአክብሮት ዋጋ መስጠት፣ ትህትናን መላበስ፣ በጽናት መጠንከር፣ ርህራሄን መጎናጸፍ፣ የሰው ልጆችን ሁሉ በልዩነታቸው አክብሮ መቀበል፣ ለራስ ጥቅም ሲባል ሌሎችን “የጦስ መስዋዕት” ያለማድረግ፣ ከንፉግነት ይልቅ ማካፈልን ማስቀደም ዝርዝራቸውን ላንዘልቅበት ነካካሁት እንጂ ብዛታቸው ከ እስከ የሚሰኝ አይደለም።
በየትኛውም የዓለማችን ጂኦግራፊያዊ ክልል ውስጥ በራሱ ባህልና የአኗኗር ዘይቤ ውስጥ የሚተዳደር ሰብዓዊ ፍጡር ሁሉ በምንም መልኩ አእምሮው ጤነኛ እስከ ሆነ ድረስ በግፍ ድርጊት ንጹሕ ደም ለማፍሰስ አይበረታታም። በርሃብተኞች መካከል ተቀምጦም በእንቁልልጮሽ ስግብግብነት “መከራ የወደቀባቸውን” ግፉዓን እያማለለ በስቃያቸው አይደሰትም። ደካማው እንዲጠቃም አሜን ብሎ አይስማማም። እብሪተኞች ለሚፈጽሙት ግፍና ጭካኔም ቀኝ እጁን በመስጠት “አሹ!” ብሎ ደመኞችን ወይንም አጥፊዎችን አይሸልምም። ይህንን እንዲፈጽም ምድራዊ ሕጉ እንኳን ሽፋን ቢሰጠው ይበልጥ ጠንክሮ የሚገስጸው ግን ኅሊናው ነው።
“ኅሊና ይሞታል!” የሚባለው የተለምዶ አባባል ለጊዜው ይስራ አይስራ በሳይንሳዊ ምርምርም ሆነ በሀገረ ሰብ ዘዴ ስላልተረጋገጠ መደምደሚያ ላይ ደርሶ እንዲህ ነው ለማለት ያዳግታል። የኅሊናን ወቀሳ እየሰሙ አሻፈረኝ ብሎ መጋለብ ባይከለከልም ለአሸናፊነት መብቃት እንደማይቻል ግን መገመቱ አይከብድም። አካልን ደብቆ አመጽ ማቀጣጠል ይቻል ይሆናል፤ ኅሊናን ተሸሽጎ የክፋት ዕቅድን አስፈጽማለሁ ማለት ግን በፍጹም የሚሞከር አይደለም። ኅሊና አይዋሽም፤ አይሸነገልም። ይህንን ርዕሰ ጉዳይ በተለመለከተ አንድ የአገራችን ጎምቱ ገጣሚ ብዕሩን “ያናገረው” እንዲህ በማለት ነበር፡-
”ቢደበቁት ርቀው ቢሸሹት አምርረው፣
እንዳትከተለን ቢሉት አስፈራርተው፣
ሊያርፍ የሚችል የለም ታዞለት ኅሊናው።
ከወቀሳ ሊድን በሽንገላ አታሎ፤
ያሸነፈ የለም ኅሊናውን ታግሎ‘
ከሥነ ምግባር ጋር ከፍተኛ ቁርኝት ስላለው ኅሊና ይህንን ያህል ከቆዘምን ዘንዳ ፊታችንን ወደ ራሳችን ወቅታዊ ጉዳዮች አዙረን ጥቂት ማለቱ ይበጅ ይመስለናል።
እንዲያው ምን ነካን ጎበዝ!?
ማኅበረሰባችን፣ኅብረተሰባችን፣ ጠበቅ እናድርገው ካልንም ኢትዮጵያዊ ማንነታችን በርግጡ “ደረታችንን ነፍተን” እንደምንደሰኩረው በባህላችን የከበርን፣ በሃይማኖታችን የበረታን፣ በአብሮ ኑሯችን በማይላላ ትስስር የተጋመድን ነን? ስናወድሳቸው ሺህ ዘመናት ጠብተው ሺህ ዘመናት የመሸባቸው ትሩፋቶችስ ጎላ አድርገን እንደምንሰብካቸው ከእኛ ጋር እንደከበሩ አሉ? “አንደበታቸው ማር የሚያንጠባጥበው” ቀዳሚ ምስክሮች በቃል እንዳስተላለፉልንና ባለ ወርቃማ ብዕረኞች በሰነዶች እንዳቆዩልን በርግጡ የባህሎቻችንና የሃይማኖቶቻችን “አክሊሎች” ከራሳችን ላይ ወድቀው አልተዋረድንም? ዛሬ ሟሸው ወይንም ሟሙተው ሊሆን ይችል ይሆናል ብልን ማሳበብ ብንችል እንኳን በርግጡ በቀዳሚ ዘመናቱስ መልካቸው ስንተርክላቸው እንደኖርነው ነበርን? እንደ እንቆቆ ቢመረንም ከእውነቱ ጋር ተጋፍጠን ራሳችንን ነፃ ማውጣቱ የሚበጀው ለእኛው ለራሳችን ነው። ለመሆኑ ምን ነክቶናል ምንስ እየሆንን ነው?
እንድንባንን ያስገደደን መራሩ መንስዔ፤
ታይቶም ይሁን ተሰምቶ በማይታወቅ ልክ በአገሪቱ የመከራ ዶፍ እያዘነቡ ያሉት ግፈኞቹና አረመኔዎቹ የወያኔ ፍልፍሎች ፈልቀው የወጡት ሥነ ምግባርን እንደ መጎናጸፊያ ከደረበና ሃይማኖትን እንደ ዘውድ ባናቱ ላይ ከደፋ ማኅበረሰብ ውስጥ ነው ሲባል አልነበረምን? ጽዮን ማርያም ቤተ ክርስቲያንና የነጃሺ ታላቁ መስጊድ የደጀ ሰላማቸው ሁነኛ አእማድ ናቸው እየተባለ ሲተረክስ አልነበረም? ይሄ ሁሉ ውጫዊ መፎከሪያ ቁጥር ውስጥ ባይገባ እንኳን ወራሪዎቹ ሽፍቶች እንደ ማንኛውም ሰው ከፈጣሪ የተለገሰ ኅሊና አላቸው አይደል?
በእነዚህ ጸጋዎች ውስጥ በቅለው አፍርተዋል የሚባሉት ስምሪት ሰጭ ጌቶቻቸውና ስምሪት ተቀባይ ጀሌዎቻቸው መሠረታዊ የሰው ልጆች ሁሉ መለያ ለሆኑት የሥነ ምግባር መርሆዎችና ከኅሊናቸው ዳኝነት አፈንግጠው በተለየ ሁኔታ በአፋርና በአማራ ክልሎችና በተቀረው የአገሪቱ ክፍሎች ንፁሐን ዜጎችን ሲጨፈጭፉ፣ ሀብት ንብረት እየዘረፉ ሲያጓጉዙ፣ ብዙዎችን ሲያፈናቅሉና አስነዋሪና ሰው የተሰኘ ሰው የማይፈጽማቸውን እርኩሰቶች በአደባባይና በፀሐይ ፊት ሲፈጽሙ ኅሊናቸው እንዴት ዝም አላቸው?
እንደሚመስለን ኅሊናቸውን ገድለውና ቀብረው ካልሆነ በስተቀር ግፍን እየተጎነጩ “ዋንጫ ኖር” ለመባባል አቅም ማግኘት ለሰብዓዊ ፍጡር የሚቻል አይመስለንም – ያውም “በወገን ላይ።” እነዚህ የዲያቢሎስ የበኩር ልጆች ምድራዊውና ሰማያዊው ፍጻሜያቸው ምን ሊመስል እንደሚችል ማሰቡ በራሱ ሃሳብ ላይ ይጥላል? የግፋቸውን ዝርዝር አንድ ሁለት እያሉ መዘርዘሩ ሰይጣን ቀምሞ የጋታቸውን የአብሾ ልክፍት ማግዘፍ ስለሚሆን እንደ ክብር የቆጠሩት ነውራቸው ቢገላለጥ ስለሚከረፋ እንዳለ አጅሎ ማለፉ ይበጃል።
ሀዘናችን ቅጥ እንዲያጣ የሚያደርገው ተጓዳኝ ጉዳይ ከአገር ውጭና በአገር ውስጥ ተሸሽገውና ተሰውረው የዚህን አሸባሪ ቡድን ተግባር እንደ ጽድቅ እየተረኩ በቁስላችን ላይ አሲድ የሚነሰንሱት የባንዳዎች ድርጊት ነው። ከሥነ ምግባር መናጠባቸው ብቻ ሳይሆን ኅሊናቸውንም ገድለው ሲቀብሩ እያስተዋልን ምን ልንል እንችላለን?
ይህን መሰሉ አገራዊ መከራና አሳር ያነሰ ይመስል ቁጥራቸውን ለመገመት የሚያዳግት ዜጎች በሶሻል ሚዲያ ደን ውስጥ ተጋርደው በበርካታ አገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ፣ በመንግሥታዊ አሠራሮችና አተገባበር፣ በፖለቲካ ፍልስፍናና በአንቂነት ሽፋን፣ በሃይማኖት ጉዳዮችና በተለያዩ አጀንዳዎች ላይ ከሥነ ምግባርና ከኅሊና ዳኝነት ባፈነገጡ እንካ ሰላንትያዎች ሲጠዛጠዙና ሲጠዘጥዙ ማስተዋል የባህል ያህል “ተጣብቶናል።” ከፍ ሲል ወደ ሃይማኖት መሪዎችና “አበ ሰላም” ነን ወደሚሉ አባቶች፣ ዝቅ ሲልም ፖለቲካውንና የመንግሥት አስተዳደርን ወደሚመሩ ግለሰቦች፣ አነስ ካለም እርስ በእርስ የሚወረወረው ዘለፋ፣ ስም አይጠሬ ስድብና መረን ለቀቅነት ሲሰሙት የሚያቅለሸልሽ፣ ሲያስተውሱት የሚያቅር ሆኖ በሽታ ከተከለብን ሰነባብቷል።
ሃሳብን በነፃነት መግለጽ ተገቢም አስፈላጊም ነው። ብዕርን በምክንያታዊነት ማጀገንም አግባብ ነው። መቃወምና መደገፍ ያለና የሚኖር የሰው ልጆች ሁሉ መለያ መሆኑም ለማንም አይጠፋም። እንኳን የዲሞክራሲ ስሙ በቀለለበት በእኛ መሰሉ አገር ቀርቶ ነዎሩ ተብሎ በሚወደስበት ምድርም ቢሆን መተቻቸትና መተራረም የተለመደ ባህል ነው። አግባብም ነው። እናስ እኛን ምን ነክቶን ነው የሥነ ምግባር ስብራት ያስነከሰን?
ባህል የረከሰበት፣ ሃይማኖት ዋጋ የተነፈገበት፣ ሽበት የቀለለበት፣ አንቱታ የተረገጠበት፣ በጥቅሉ ሥነ ምግባር ከደጃፋችን እንዲሰደድ አዚም ያደረገብን ምንና ማን ነው? ቴክኖሎጂው? ወይንስ ባንኖርበትም ተጀቡነንበት የኖርነው ምንትሳችን? ሥነ ምግባር እንደዚህ ዘመን ድንገቴ ጦርነት ተከፍቶበት የተዋረደበት ወቅት ስለመኖሩ የሚያውቅ ቢያሳውቀንና ቢያረጋጋን ሳይጠቅመን አይቀርም።
ኢትዮጵያ ሆይ ራስሽን ፈትሺ! ቢያሻሽ እያለቀስሽ፣ ከበረታሽ ወደ ፈጣሪ የተዘረጋውን እጆችሽን ይበልጥ አስረዝምሽ “ኤሎሄ! ኤሎሄ! ላማ ሰበቅታኒ!” እያልሽ መጮኹ ላይ ብትበረቺ ላንቺም ለራስሽ፤ ለእኛም ልጆች ተብዬዎች ሳይበጀን አይቀርም። ባህሎቼ፣ እምነቶቼ፣ ወግና ልማዶቼ እያልሽ የተመካሽባቸውን የውበት ጌጦችሽን ሙዳይ እንድትፈትሺ ግዜው ግድ ይልሻል። “መጎናጸፊያዬ ወርቅና አልማዝ ነው” እያልሽ በመተረክ ያወረስሽን ውበትሽ በርግጡ አለ? ካለ ለምን ፊትሽን ማዲያት አከሰለው? ወርቅና አልማዝሽስ ለምን አርቴፊሻል መስሎ ታየን? ሥነ ምግባር ሆይ ወዴት አለህ? ሰላም ይሁን!
(ጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን የካቲት 16/2014