ትናንት በነበረው ፣ ማሕበራዊ መስተጋብር ውስጥ አለመግባባት ፣ ቅሬታና ግጭት ነበር ፤ ዛሬም አለ ፤ ወደፊትም ሊኖር ይችላል:: ግጭት የማሕበራዊ ሕይወት አንዱ መገለጫ ነው:: የአንድ አገር ሕዝቦች ብቻ ሳይሆኑ የአንድ ቤተሰብ አባላትም ሊጋጩ ይችላሉ:: ሕብረተሰባችን ከጥንት ጀምሮ በግጦሽ ሳር ፣ በውሃና በተለያዩ ጉዳዮች እየተጋጨ መልሶ በአገር ሽማግሌዎችና በሃይማኖት አባቶች እርቅ አውርዶ ይኖራል::
በሃሳብ ስላልተግባባን ወይም ስለተጋጨን ከሰውነት ክብራችን ወረድን ማለት አይደለም፤ ግጭቱን መቆጣጠር ካቃተንና ወደከፋ ትርምስና ብጥብጥ ከገባን ብሎም የሕይወት ዋጋ ከከፈልን ግን ያን ጊዜ ሰው መሆናችን አጠያያቂ ሊሆን ይችላል::
ሰው ታላቅ ፍጡር ነው:: ታላቅ ያሰኘውና ከሌሎችች ፍጡራን የሚለየው የሚያስብ በመሆኑ ነው:: ሃሳብ አፍልቆ ወደ ተግባር የመለወጥ ጸጋ ተሰጥቶታል:: በኑሮ ሂደቱ እርስ በእርስ እየተመካከረ፣ እየተማማረ፣ እየተራረመ፣ እየተረዳዳና ይቅር እየተባባለ ስፍር ቁጥር የሌላቸው ችግሮችን እየፈታ ኖሯል:: ይህ ወደፊትም የሚቀጥል ነው::
ሰው ማሕበራዊ አኗኗርን የሚከተል ፍጥረት እንደመሆኑ መጀመሪያ ከአካባቢው ቀጥሎም ከአገሩ ከፍ ሲልም ከዓለም ማሕበረሰብ ጋር አብሮነቱን ማጠናከር ግድ ይለዋል:: የአንድ አገር ሕዝቦች የተለያየ ቋንቋ፣ ባህል፣ ሃይማኖት፣ ፖለቲካዊ ፍላጎትና አመለካከት ሊኖራቸው ይችላል፤ ልዩነታቸውን አጥብበው በጋራ አገራዊ ጉዳይ ላይ መግባባት ካልቻሉ እንደአገር የመቀጠላቸው ነገር አጠያያቂ ይሆናል::
አሁን አሁን በአገራችን አንዳንድ ግለሰቦችና ቡድኖች ባንዲራን ፣ ብሄርን ፣ ሃይማኖትን፣ ማንነትን፣ ወዘተ. መሰረት ያደረጉ ዋልታ ረገጥ አስተሳሰቦችን እያንጸባረቁ በሕዝቦች መካከል መለያየት ለመፍጠር ሲጥሩ ይታያል:: በዚህ የተነሳም በርካታ ንጹኋን ዜጎች በማያውቁት ጉዳይ ጥቃት ሲደርስባቸው ይስተዋላል::
እርግጥ ነው ጥያቄዎች ሊኖሩን ይችላሉ፤ ጥያቄዎቻችንን ማስፈጸም የምንችለው በምክክርና በጋራ መግባባት እንጂ ጦር በመስበቅ ሊሆን አይገባም:: ችግሮቻችንን በመነጋገር መፍታት እየቻልን ነፍጥ ለማንገብ መሽቀዳደም የለብንም:: ነፍጥ ማንገብ የኋላ ቀርነት መገለጫ ነው:: ዜጎች የጋራ ምክክር በማድረግ፣ የጎበጠውን በማቅናት፣ የጎደለውን በመሙላት ሰላምና ፍቅር የነገሰባት አገር መፍጠር ይኖርባቸዋል::
አገር እና መኖሪያ ቤት አንድ ናቸው፤ ግድግዳው ተነድሎ ብርድ የሚያስገባ ፣ ጣሪያው ተበሳስቶ የሚያፈስ ወይም መሰረቱ ተናግቶ የዘመመ ቤት ለነዋሪዎቹ ምቾትም ዋስትናም አይሰጥም:: እንዲህ አይነቱ ቤት አስቸኳይ ጥገና ያስፈልገዋል:: ዋልታና ማገሩ መጠናከር፤ የሚያፈሰው ቆርቆሮም መቀየር አለበት:: ጥገናው በወቅቱ ካልተከናወነ የቤተሰቡ አባላት ምናልባትም የሚገጥማቸው እጣ ከሁለት አንዱ ነው::
አንደኛው የሚመጣውን አደጋ ሁሉ ለመቀበል መዘጋጀት ሲሆን ሁለተኛው ግን ቦታውን ለቆ መሄድ ወይም መፈናቀል ነው::
አገርም እንዲሁ ሕዝቦችን አሰባስቦ የያዘ ሰፊ ቤት ነው፤ ቤቱ ከዘመመ ወይም ካፈሰሰ አደጋው ለሁሉም ነው፤ እያንዳንዱ ዜጋ መጀመሪያ የጋራ መኖሪያ ቤቱን ዋስትና ለማረጋገጥ ለአገሩ ጉዳይ ዋልታና ማገር መሆን ይገባዋል እንጂ መልሶ ለአገሩ ሰላም ስጋት መሆን የለበትም::
አሁን አገራችን ከአሸባሪው ሕወሓት ቡድን ጋር ተገዳ የገባችበትን ጦርነት ሳትቋጭ ሌሎች አባባሽ ጉዳዮች እየተደራረቡባት ዘላቂ ሰላም ማግኘት አልቻለችም:: በየጊዜው አንድነቷን የሚፈታተኑ ጉዳዮች እየተፈጠሩ ሕዝቦቿ የሰላምን አየር እንዳይረተነፍሱ ሆነዋል::
በዚህች አገር ውስጥ የምንኖር ዜጎች የተለያዩ ጥያቄዎች ሊኖሩን ይችላሉ:: ጥያቄዎቻችን ግን በነፍጥ አይመለሱም:: ነፍጥ ማንገባችን የአገራችንን ውድቀት ለማየት ያሰፈሰፉ አካላትን ያሰፈነጥዝ ካልሆነ በስተቀር ለኢትዮጵያና ለሕዝቦቿ የሚያተርፍላቸው አንዳችም ነገር አይኖርም::
አስተማማኝ ሰላም አስፍነን ልማትና እድገታችንን የምናረጋግጥበት አዋጭ መንገድ መነጋገርና መመካከር ብቻ ነው:: በንግግር ውስጥ ሁሉንም ሊያስማሙ የሚችሉ የተሻሉ ሃሳቦች ይፈልቃሉ፤ ሁሉንም ዜጋ የሚወክሉ አዋቂዎች ተሰባስበው ስለአገራቸው ሃሳብ ቢያዋጡና ቢመክሩ የጋራ መፍትሄ ይገኛል::
በዚህ ረገድ መንግሥት አገራዊ ምክክር እንዲደረግ ቅድመ ዝግጅቶችን እያደረገ ነው:: ብሄራዊ መግባባት ላይ የሚደረሰው አካታችና ግልጽ ውይይት ማድረግ ሲቻል ነው:: በእንዲህ አይነቱ መድረክ የተለያዩ ጥያቄዎች አንድ ቦታ ቀርበው መፍትሄ እንዲያገኙ፣ የሃሳብ የበላይነት እንዲያሸንፍ ሆድና ጀርባ የነበሩ አካላት ሆድ ለሆድ እንዲግባቡ ያስችላል:: የብዙ ሰዎችን ሃሳብ በመጭመቅ የጋራ መግባባት ላይ መድረስ ይቻላል::
አባቶቻችን “አንድ ሰው አስቦ አንድ በሬ ስቦ … ›› በሚለው አባባላቸው የሚያስተምሩን ይህንኑ ነው:: የብዙዎች አቅም ሲሰባሰብ ውጤታማ እንደሚያደርግ ከተሞክሯቸው የተገነዘቡትን በምሳሌ አስረድተውናል::
አባቶቻችን ደግም ኢትዮጵያን እንደአገር አቁመው አልፈዋል:: እኛም ጉድለቶቻችንን እያረምን ኢትዮጵያን ወደፊት የማሸገር ሃላፊነትና አደራ አለብን:: ጉድለቶቻችንን የምናርመው በጠብና በአንባጓሮ ሳይሆን በሃሳብ ልዕልና ነው::
እንደ አሜሪካ ያሉ ሃያላን አገራት ፍትሃዊና ዴሞክራሲያዊ ሥርዓትን አስፍነናል ከማለታቸው በፊት እኛ ኢትዮጵያውያን ችግሮቻችንን መፍታት የሚያስችሉ በርካታ ሃይማኖታዊና ባህላዊ እሴቶችን ታጥቀናል:: እሴቶቻችን የሰውን ሕይወት የሚያጠፉና ንብረት የሚያወድሙ ሳይሆኑ የሚታደጉ ናቸው:: የበደለን የሚወቅሱ ፤ የተበደለን የሚክሱ፣ የሚመክሩ፣ የሚምሩና ያፈነገጠውን የሚቀጡም ጭምር ናቸው::
ሃይማኖታዊና ባህላዊ እሴቶቻችን በሥነ ምግባር ታንጸን እንድናድግ ረድተውናል፤ ፈጣሪያችንን እንድንፈራ፣ አገራችንን እንድንወድ ፣ እንድንከባበር፣ አንድነታችንን እንድንጠብቅ፣ ሽማግሌዎችንና ታላላቆቻችንን እንድናከብር አድርገውናል::
በታላላቆቻችን ቁጣና ተግሳጽ ብቻ ጠብ እያበረድን ፤ እርቅና ሰላምን እያወረድን አብሮነታችንን አስቀጥለናል፤ ሕግ አርቅቀን ሥራ ላይ ከማዋላችን በፊት እሴቶቻችንን እንደ ሕጋዊ ከለላ ተጠቅመንባቸዋል:: ዛሬም ጥቅም እየሰጡን ነው::
ለዚህም ነው ግጭትና ክርክር ይዘው ወደ ፍርድ ቤት የሚቀርቡ ሰዎች መጀመሪያ ጉዳያቸውን በአገር ሽማግሌዎች /በባህላዊ ወግና ሥርዓት/ እንዲፈቱ እድል የሚሰጣቸው:: ባህላዊ እሴቶቻችን ጽፈን ካጸደቅናቸው ሕጎች ያልተናነሰ ሚና ያላቸው መሆኑን ከዚህ መረዳት ይቻላል::
ኢትዮጵያውያን እንደየአካባቢውና እንደየማህበረሳባችን ሁኔታ ግጭቶችን የምንፈታባቸው ባህላዊና ሃይማኖታዊ እሴቶች በርካቶች ናቸው:: ለዚህ አንድ ማሳያ እንዲሆን በአንድ ወቅት የአርባ ምንጭ ከተማ ወጣቶች በቁጣ ስሜት ተነሳስተው አደጋ ሊፈጽሙ ሲነሱ የጋሞ አባቶች ለምለም ሳር በእጃቸው ይዘው ገስጸው ያስቆሟቸውን ክስተት ማስታወስ ያስፈልጋል::
በየቦታው መሰል አለመግባባቶችና ግጭቶች ሲፈጸሙ አባ ገዳዎች፣ የዘመድ ዳኞች፣ የሃይማኖት አባቶች ጥላቻን በፍቅር ፣ ቂምን በይቅርታ ፣ ጭካኔን በርህራሄ፣ ኀዘንን በደስታ የመለወጥ ማሕበራዊ ሃላፊነታቸውን እየተወጡ አብሮነታችንን አስቀጥለውልናል::
መንግሥትም ለማሕበራዊ እሴቶቻችን ዋጋ በመስጠት ለይቅርታ፣ ለፍቅርና ለሰላም የዘረጋቸው እጆቹ አሁን ድረስ አልታጠፉም:: ለምሳሌ፣ አሸባሪው የሕወሓት ቡድን በሕዝብ እና በለውጥ ሃይሉ ትግል ከሥልጣን ተባሮ መቀሌ ከመሸገ በኋላ በሥልጣን ዘመኑ በፈጸመው ወንጀል ሳይጠየቅ በይቅርታ ታልፎ ነበር:: የአገር ሽማግሌዎችና የሃይማኖት አባቶች ያደረጉት የሽምግልና ጥረትም የሚረሳ አይደለም::
መንግሥት የሕዝቦች አብሮነትና ማሕበራዊ መስተጋብር እንዳይበላሽ የወሰደው እርምጃ ግን ለአሸባሪ ቡድኑ ሌላ ትርጉም ነበረው:: ለዚህም ነው በእብሪት ተሞልቶ የሰሜን ዕዝ መከላከያ ሰራዊትን በማጥቃት ኢትዮጵያን ለማፈራረስ የተነሳው::
አሸባሪው የሕወሓት ቡድን ለሁለተኛ ጊዜ የተሰጠውን የጥሞናና የማሰላሰያ እድል አሻፈረኝ ብሎ የአማራና የአፋር ክልሎችን ወርሮ ሰብዓዊና ቁሳዊ ጉዳቶችን ማድረሱ የሚታወስ ነው:: ዛሬም በአፋር፣ በጎንደርና በወሎ ትንኮሳውን አላቆመም::
አሸባሪው የሕወሓት ቡድን ‹‹ድመት መንኩሳ አመሏን አትረሳ›› እንደሚባለው ሆኖ እንጂ ለሰላምና ለይቅርታ ያልተጋበዘበት ጊዜ አልነበረም:: በተመሳሳይ የዚሁ ቡድን ተቀጥላ የሆነው የሸኔ ታጣቂዎችም ቢሆኑ በሰላማዊ መንገድ እንዲታገሉ በአባገዳዎች ተደጋጋሚ ጥሪ ሲደረግላቸው ነበር::
አገራዊ ምክክር እና ብሄራዊ መግባባት ለመፍጠር የሌሎች አገራት ተሞክሮ ሳያስፈልገን ባህላዊ እና ሃይማኖታዊ እሴቶቻችንን ተጠቅመን የምንፈልጋትን አገር መፍጠር እንችላለን:: ግን ቅን ልቦና ይስጠን::
ሜላት ኢያሱ
አዲስ ዘመን የካቲት 16/2014