ከኢትዮጵያ ሕዝብ ከ60 በመቶ የሚልቀው በምሽት ብልጭ የሚያደርጋት መብራት አጥቶ ዛሬም ከጭለማ ጋር ትግል ይገጥማል።አገሪቱ ውስጥ ያሉ አነስተኛና ከፍተኛ ኢንዱስትሪዎች በኃይል እጥረት ፈተና ውስጥ ወድቀዋል።በመልማት ላይ ያለች አገር ናትና ሩቅ አስባ የገነባቻቸው ግዙፍ ፕሮጀክቶች አንቀሳቃሽ ኃይል ናፍቀዋል።የኤሌትሪክ ኃይል አቅርቦት ከፍላጎት ጋር ከቶም ሊጣጣም ባለመቻሉ የኃይል አቅርቦት አለመኖር ለእድገት ማነቆ ለኑሮ ፈተና ሆኖ ዘመናትን ተሻግሯል፡፡
ይህን የተመለከቱት ኢትዮጵያውያን ለዚህ መፍትሔን ዘየዱ።ከ10 ዓመት ቀድመው የዚህ ሁሉ ፍላጎት መሙያ መፍትሔ የሚሆን ግዙፍ ፕሮጀክት ጉባ ላይ ወጠኑ።ታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ መገንባት ጀመሩ።ግንባታውም ብዙ ጫናና ፈተናን፣ የበዛ ሙግትና የእጅ አዙር ሴራን ተሻግሮ ዛሬ ላይ የመጀመሪያው ደረጃ ፍሬውን ለማቋደስ በቃ።በፈተና የሚፀኑት ሲነካኩዋቸው ይበልጥ የሚጠነክሩት ኢትዮጵያውያን በከፍተኛ ተጋድሎ ውጥናቸውን በማሳካት የመጀመሪያውን ብርሃን ለማየት በቁ።
በዚህ ረገድ ለኢትዮጵያውያን የህዳሴ ግድብ ትርጉሙ ይሰፋል።በጋራ አንድ ሆኖ ያቆማቸው በኅብረት መቻልን ያረጋገጠላቸው በራስ አቅም መቆም ይቻላልን ያበሰራቸው ታላቅ ፕሮጀክታቸው ነውና ከሁሉ የተለየ ጥልቅ ትርጓሜ አለው።የአንድነት ካባ ለብሰው በፍቅር የዘመሩለት ያለ ልዩነት በጋራ የቆሙለት ይህ ታላቁ የህዳሴ ግድብ ከምንም በላይ አብይ ጉዳያቸው ነውና ትርጓሜው እጅጉን ይገዝፋል።
ዓባይ ግንድ ይዞ መዞሩን ትቶ፤ ዛሬ ላይ ለአገሩ ኢትዮጵያ ግዴታውን ሊወጣ አንድ ምዕራፍ ተጉዞ እነሆ ብርሃኑን ለናፈቁት ሁሉ ከጉባ በረሃዎች ከተራራው መሐል ደርሶ ብስራቱን አሰምቷል።ከዛሬ ነገ ይሄን ብስራት ለናፈቁ መቶ ሚሊዮኖች፣ ዓይንና ልባቸው ወደ አገሪቱ ሰሜን ምዕራብ ክፍል የምትገኘው ጉባ ላይ ሆኖ ለከረመ ሆሉ የጋራ አሻራቸው ካረፈበት ሥፍራ ከህዳሴያቸው ማህተም ጅማሮ ቦታ የድላቸውን ዜና አስደምጧል።
እናም የጋራ አሻራቸው ያረፈበት የግዙፍ ፕሮጀክታቸውን ፍሬ ማየትን እጅጉን ሽተዋልና የሻቱትን አስገኝቶላቸዋል።ከሰሜን ጫፍ እሰከ ደቡብ መዳረሻ ከምዕራብ መነሻ እስከ ምስራቁ ጠርዝ ያለ ልዩነት ያላቸውን እንካችሁ ያሉበት በአብሮነት ቆመው “የኔ ነው” ካሉት ታላቁ ግድብ ብርሃንን ማየት ናፍቀዋልና እነሆ ናፍቆታቸውን የሚያስታግሱበትን ብርሃን በመጀመሪያው ምዕራፍ ተግባሩ አሳይቷቸዋል፡፡
ተርፏቸው ሳይሆን ከሌላቸው ላይ ቀንሰው አሻራቸው ያሳረፉበት ግድብ ዛሬ ላይ ለፍሬ ሊበቃ መቃረቡን ሰምተዋው፤ በአንድ ልብ ያለ ልዩነት በነቃ ጆሮ ብስራት መስማትን ፈልገው፤ በጎለበተ ተስፋ ለእድገታችን ምርኩዝ ነው ያሉት ግድብ ብርሃን መፈንጠቅ ጀመረ የሚለውን ማየት ከምንም በላይ ሽተው ነበርና ይሆናል በሚል የሰሙት መሆኑ፤ አጥብቀው የፈለጉትና የሻቱት የጉድለታቸው ሙሊት እንደተመኙት ሆኖላቸዋል፡፡
ለግድቡ አቅመ ደካማ እናት ከመቀነታቸው ፈተው እጃቸውን ዘርግተዋል፤ ተማሪ ከደብተርና ከእስክሪቢቶ መግዣው ላይ ቀንሶ ነገዬን ብርሃን አድርጉልኝ የእኔም አሻራ ይኑርበት ብሏል፤ ከሊቅ እስከ ደቂቁ ሳይሰስት ከአስር ዓመታት በላይ ለግድቤ ብሎ ያለውን አዋጥቷል።ዓባይ ዐብይ ጉዳያቸው ነውና ኢትዮጵያውያን አንድነታቸውን በጉልህ ያሳዩበት የመልማት ውጥናቸው ማሳኪያ፣ የፍትሐዊ ተጠቃሚነታቸው ማሳያ የሆነው ታላቁ የሕዳሴ ግድብ የተመለከተ ብሩህ ዜና ከወደ ጉባ መስማት ችለዋል፡፡
ኢትዮጵያ በራስዋ ተፈጥሯዊ ሀብት የመልማት ፍላጎትዋ ማሳያና የህዳሴ ጉዞዋ ፈር ቀዳጅ የሆነው ታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ከተጀመረ 11 ዓመት ሊሞላው የአንድ ወር እድሜ ብቻ ቀርቶታል።በእነዚህ ሁሉ ዓመታት የተለያዩ ፈተናዎች የገጠሙት ግድቡ አሁን ላይ በተጠናከረና እጅግ አመርቂ በሆነ ውጤት ላይ ከመድረስም በላይ በ11ኛ ዓመቱ ዋዜማ ላይ ሆኖ የመጀመሪያው ምዕራፍ ውጤቱ የሆነውን ብርሃን እነሆ ብሏል፡፡
እንደ አገር የዚህ ታላቅ ፕሮጀክት ስኬት ላይ ለማድረስና ከፍሬው ለመቋደስ በሚደረግ ጥረት ውስጥ የበዙ ፈተናዎች ተጋርጠውብን አልፏል።ምን አልባትም ወደፊትም በምትፈጥረው አቅም የሚለካ ከውጪና ከውስጥ የኢትዮጵያን ለውጥ በማይፈልጉ ኃይላት ጫናና እንቅፋት መፍጠራቸው አይቀር ይሆናል።ነገር ግን እንገነባዋለን ብለው የጀመሩት ኢትዮጵያውያን ናቸውና ወደ ፍፃሜው ፍጻሜ እያቃረቡት ይገኛሉ፤ ጫናዎቹን ሁሉ ተሻገረው እንደሚፈጽሙትም ሙሉ እምነት አለኝ።
ከጅማሮ እስካሁን ባለው የግድቡ ግንባታ ሂደት በተፋሰሱ አገራት መካከል የሚነሱ አለመግባባቶችና በውሃው አጠቃቀም ፍትሐዊነት ጉዳይ ኢትዮጵያ በጋራ መልማትና ተጠቃሚነት ላይ የማያወላውል አቋም ደጋግማ አሳውቃለች።አብረን አንዳችን ሌላችን ሳንጎዳ አልምተን በጋራ እንደግ ጥሪዋን አልሰማት ብለውም፤ የራስዋን አሳልፋ የማትሰጥ የሰውን የማትነካ የጀግኖች ምድር መሆንዋን ዘንግተው ብዙ ሞከሩ፡፡
ብቻዬን ካልበላሁ የሚል እልህና ያረጀ እሳቤን ሙጥኝ ያሉት የታችኞቹ ተፋሰስ አገራት ግብፅና ጋሻ ጃግሬዎችዋ ሱዳን ዛሬ ድረስ በተለያየ መልኩ እጅ ለመጠምዘዝ የሚያደርጉትን ጥረት ቀጥለውበታል።በእርግጥ ኢትዮጵያውያን የሚጠመዘዝ እጅ አልነበራቸውምና ወደ ብስራት ዜናቸው ገሰገሱ፤ ወደ ልማትና እድገታቸው መቃረባቸውን ቀጠሉ፤ እናም የግስጋሴያቸው አንዱ የብርሃን ጫፍ የሆነውን ዜና ለራሳቸውም ለወዳጆቻቸውም አበሰሩ፡፡
ዛሬ ከምንም በላይ ታላቅ የሆነ አገራዊ ጉዳይ፤ ከየትኛውም ጊዜ በላቀ ሁናቴ የሚጠበቅ ተናፋቂ የብስራት ዜና፤ ቁንጮ የሆነ ግዙፍ ፕሮጀክት፤ የመቶ ሚሊዮኖች አይን የሚሳሳለትና ተስፋ የጣሉበት ኃያል ሥራ፤ ውጤቱ የግዝፈቱን ያህል በታላቅ ጉጉት የሚጠበቅ ዋነኛ ጉዳይ፤ ጭለማን የሚገፍ ብርሃንን የሚያላብስ የጋራ አሻራ ያረፈበት፤ በረዥሙ ወንዝ ላይ ከተገነባው ግዙፉ ፕሮጀክት የሚጠበቀው በረከት፤ የአህጉሪቱ ትልቁ መነጋገሪያ፣ በተለይ ለኢትዮጵያውያን ዋነኛ ጉዳይ ዐቢይ ጉዳይ፤ ታላቁ የህዳሴው ግድብ ነው፡፡
አቅም አጥተን ለዘመናት ትቶን በመሄዱ ረግመነዋል፤ ስላልቻልን ቁልቁል ሲሸመጥጥ ዋ! አስብሎናል።ትላንት ከእንቅልፋችን ስንነቃ ለምን? ብለን መጠየቃችን ምላሽ አስገኝቶ ዛሬ የጥረታችን ፍሬ የአንድ መሆናችን ተምሳሌት የህዳሴያችን ጅማሮ ለማየት ችለናል።አዎን ግድቡ ለዚህ ሕዝብ ትርጉሙ ያላቀ ከሚታሰበውም ከፍ ያለ ትርጓሜ ያለው የወደፊት የመለወጥ ጉጉቱ ማሳያ ተምሳሌቱ ነው።
በአገር ጠሎች ሴራ ከሞት የዳነው ግድብ በኢትዮጵያ ልጆች ተጋድሎ መልሶ የጎመራው ኃያሉ ፕሮጀክት ዛሬ ላይ የመጀመሪያ ምዕራፉን ብስራት በማሰማት ወደ ፍፃሜው ፍጻሜ ተቃርቧል።ኢትዮጵያውያንም የእስከዛሬው የጋራ ርብርባቸው ውጤት የአንድነታቸው ማሰሪያ ግድባቸው ብርሃን መፈንጠቅ መጀመረ ዜና ሊሰሙ በጉጉት ጠብቀው ነበርና ብስራቱን ሰምተዋል፤ ብርሃኑንም ተመልክተዋል፡፡
ይህ ደግሞ የኢትዮጵያውያን ሕያው የሆነ የማንነታቸው ማህተም፣ የመቻላቸው መገለጫ፣ የአብሮነትና ትብብራቸው መከሰቻ ሆኖ ለዓለም ዳግም የገለጣቸው ታላቅ ፕሮጀክታቸው፤ የነገ ጉዟቸው ብርሃን ሆኖ የሚያሻግራቸው ብርታት የሆነ ክብራቸው፤ በዓለም አደባባይ ከፍ ብለው እንዲገለጡ ብቻ ሳይሆን የተናገሩትን የመፈጸም ባህላቸውን አምኖ በመቀበል የሚሉትን የሚሰማቸው በርከት ብሎ እንዲፈጠር የሚያስችል፤ በጥቅሉ የታላቅነታቸው ማህተም ሆኖ ወደ ከፍታቸው የሚያወጣቸው ነውና እንኳን ደስ ያለን ልል እወዳለሁ፡፡
ሆኖም ይህ የመጀመሪያ ምዕራፍ ደስታችን ሙሉ እንዲሆን ቀጣይ ምዕራፎችም በስኬት እንዲጓዙ ማድረግና የፍጻሜውን ፍጻሜ ለማየት እንድንታትት ስል አደራ ማለት እወዳለሁ።ቸር ሰንብቱ! የፍጻሜውን ብስራትም የምንሰማ ድርገን፡፡
አዲስ ዘመን የካቲት 14 ቀን 2014 ዓ.ም