ካለፉት ሶስት አመታት ወዲህ የሴራ ወይም የደባ ፖለቲካ ለውጡን ከማጠልሸት አልፎ በተወሰነ ደረጃ መጠራጠርንና ልዩነትን እየጎነቆለ ነው። በመንግስትና በሕዝብ መካከል መተማመን እንዳይኖር ሁሉንም ነገር ከሴራ ጋር ማጃመል እየተለመደ ነው። ውሳኔዎችንና አቋሞቹን በቁማቸው ከመተንተን ፣ ከመበየን ፣ ከመጠየቅና ከመሞገት ይልቅ በሴራ እየተለወሱ ከተልዕኳቸው ፣ ከአውዳቸውና ከአላማቸው ውጭ ትርጉም እየተሰጣቸው ሕዝብን ግራ እያጋቡ ይገኛል ። ከፍ ሲልም ሀገርን በድንግዝግዝ እያስቀመጡ ነው ። ለመሆኑ ሀገርንና ሕዝብን እያወናበደ አንዳንዴም ሕዝብንና መንግስትን በጥርጣሬ እንዲተያዩ የሚያደርገው የሴራ ኅልዮት /Conspiracy Theory/ ምን ማለት ነው !?
ተፅዕኖ ፈጣሪ ሰዎች ፣ ባለስልጣናት አልያም የተወሰኑ የፖለቲካ ፣ የአይዶሎጂና የኢኮኖሚ ቡድኖች ሚስጥራዊ ዕቅድ ውጤት የሆነ ሁነት ወይም ክስተት የሴራ ኀልዮት Conspiracy Theory ሲል ይበይነዋል የእንግሊዘኛው መዝገበ ቃለት ሜሪያም ዌቢስተር ። (A theory that explains an event or situation as the result of a secret plan by usually powerful people or groups. ) የኢትዮጵያ ቋንቋዎች ጥናትና ምርምር ማዕከል በ1993 ዓ.ም ባሰናዳው የአማርኛ መዝገበ ቃላት ደግሞ ፤ አድማን፦ ሴራ ዱለታ ፤ ሲል በአጭሩ ይተረጉመዋል ፡፡
ሆኖም በባለስልጣናት ፣ በመንግስት ሆን ብሎ ጉዳት ለማድረስ በሚስጥር የሚፈፀም ደባም የሴራ ኀልዮት ነው ሲሉ ድርሳናት ትርጉሙን ሰፋ ያደርጉታል። ታዋቂው የፖለቲካ ሊቅ ማይክል ባርኩን በበኩሉ ኀልዮቱ አፅናፈ አለም (universe) በአቦሰጥ ሳይሆን በንድፍ (design) ትመራለች በሚለው ታረክ ላይ የተዋቀረ ነው ሲል ይሞግታል ፡፡
እንደ ባርኩን ትንተና የሴራ ኀልዮት ሶስት መገለጫዎች አሉት። የመጀመሪያው ምንም ነገር በአጋጣሚ አይሆንም የሚል ሲሆን ፤ ሁለተኛው ደግሞ ምንም ነገር ላይ ላዩን እንደምናየው ፣ እንደመሰለን አይደልም ይላል ፤ ሶስተኛው ደግሞ ሁሉም ነገር እርስ በርሱ የተያያዘ ነው ብሎ ያምናል። ሌላው የኀልዮቱ ባህሪ ይላል ባርኩን ውሸት መሆኑን በመረጃ ለማስተባበል ፈታኝ መሆኑ ነው ። የኀልዮቱ መነሻ የመሪዎች ግድያ ሲሆን ዘመኑም ከ20ኛው ክፍለ ዘመን መባቻ አንስቶ መሆኑ ድርሳናት ያትታሉ ፡፡
ከእያንዳንዱ ክስተት ጀርባ ሴራ ደባ አለ በማለት በዜጎችና በሕዝቦች መካከል መጠራጠርን የሚቀፈቅፍ ኀልዮት ነው ። በታላቁ መፅሐፍ- “በእግዜአብሔር እናምናለን ፡፡” እና “አይኖቹ በምድር ሁሉ ያያሉ ፡፡” ከሚለው ቅዱስ ቃል ላይ ተመስርቶ በአሜሪካ የአንድ ዶላር ላይ ፈጠሪ ሁሉን እንደሚያይ ፤ አሜሪካ በቅጥሩ በጥበቃው ስር እንደሆነች የሚወክለውን ምስል ( the all seeing eye ) ሳይቀር በአሜሪካ መስራች አባቶች የተሸረበ ሴራ ተደርጎ መቆጠሩ ኀልዮቱ ምን ያህል ጥርጣሬን ለመዝራት ምን ያህል ምቹ እንደሆነ ያሳያል፡፡
አንዳንድ የስነ ልቦና ሊቃውንት ኀልዮቱ በማኪያቬሊያዊ ፅንሰ ሀሳብ በዜጋውና በሕዝብ መካከል ፍርሀትን በመንዛት ላይ ያተኮረ መሆኑን ይተነትናሉ። በአለማችን በሴራ ኀልዮት አብነትነት በቀዳሚነት ከሚጠቀሱት መካከል የአሜሪካው 35ኛ ፕሬዚዳንት ጆን ኤፍ ኬኔዲ ግድያ ላይ የሀገሪቱ የስለላ ድርጅት (ሲ.አይ.ኤ) እጁ አለበት ።
እአአ በ1971 አፓሎ የተሰኘች የአሜሪካ መንኮራኮር ለመጀመሪያ ጊዜ ጨረቃ ላይ ማረፏን የሚክደው እንዲሁም በተለምዶ በ9/11 አልቃይዳ በአለም የንግድ ድርጅት ህንፃዎች ፣ በፔንታጎንና በመንገደኞች አውሮፕላን ከ3ሺህ በላይ አሜሪካውያንና የውጭ ዜጎች ባለቁበት የሽብር ጥቃት አሁንም ሲ አይ ኤ ተሳትፎበታል። ኤች አይ ቪ / ኤድስን አሜሪካ ነች ጥቁሮችንና ሌሎች ለመጨረስ በቤተ ሙከራ የፈጠረችው እና የእንግሊዟን ልዕልት ዲያና ፈረንሳይ ፓሪስ በመኪና አደጋ የሞተችው በሀገሪቱ የስለላ ድርጅት ኤም አይ 5ና 6 እና ንጉሳዊ ቤተሰቡ ሴራ ነው የሚሉ ይገኙበታል፡፡
ወደ ሀገራችን ስንመጣ ደግሞ የሴራ ኀልዮትን ባህሪያት ሙሉ በሙሉ ባያሟሉም ህልቁ መሳፍርት ከሆኑ አሉባልታዎች ፣ በሬ ወለደዎች ለአብነት ያህል ሰሞነኛ የሆኑትን ላነሳሳ ። የፌዴራል መንግስት ለኦሮሙማ ወይም የኦሮሞን ቋንቋና ባባህል በሌሎች ላይ ለመጫን እየሰራ ነው ፤ በየተቋማቱ ተረኝነት ነግሷል ፤ ዐቢይ አማራን ለማዳከም እየሰራ ነው ፤ የአማራ ክልል በሕወሓት እንዲወረርና እንዲጨፈጨፍ የተደረገው ሆን ተብሎ ነው ፤ እነ ስብሀት የተፈቱት ከሕወሓት ጋር ድርድር ተደርጎ ነው ፤ ዐቢይ በድብቅ ከደብረጺዎን ጋር እየተደራደረ ነው ፤ ቆየት ካሉት ደግሞ የሰኔ 15ቱ “ መፈንቅለ መንግስት “ ሙከራ ፣ የአማራ ክልል ከፍተኛ አመራሮችና የኢታማዦሮ ሹሙ ግድያ በፌዴራል መንግስት የተቀነባበረ ነው። ለውጡ በኦነግ ተጠልፏል …! ? ጌታቸው አሰፋ በሌላ ሰው ፓስ ፓርትና ማንነቱን ደብቆ በክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይሁንታ ለከፍተኛ ህክምና ወደ ውጭ ሀገር ተልኳል እና ሌሎች የሀበሻ ሴራዎች የቡና ፣ የድራፍት ማጣጫ ከሆኑ ዋል አደር ብለዋል ፡፡
የሴራ ኀልዮት ባህሪያት
ሀ . ጥርጣሬን ማንበር፦
እነዚህን እና ሌሎችን የሴራ ኀልዮቶች የሚያመሳስሏቸው ሕዝብ በመንግስቱ ላይ ጥርጣሬ እንዲያድርበት ፣ እምነቱን እንዲያጣ በተፅዕኖ ፈጣሪዎች የሚሸረቡ መሆናቸው ነው። ለውጡ ከባተ ካለፉት ሶስት አመታት ወዲህ በተለይ በማህበራዊ ሚዲያው የሚነዙ አሉባልታዎችንና በሬ ወለደዎችን እዚህ ላይ ያጤኑአል፡፡
ለ . የሌለ ምስል መከሰት፦
የሴራ ኀልዮት የማይገናኙ ሁነቶችን ነጥቦችን በማገናኘት በማገጣጠም ትርጉም መስጠት ፣ ምስል መከሰት መለያ ባህሪው ነው ። ከለውጡ ማግስት ጀምሮ በሕወሓት በበላይነት ተይዘው የነበሩ የኃላፊነት ቦታዎች ላይ የብሔር ተዋፅኦን መሰረት ባደረገ መልኩ የኦሮሚያ ብልጽግና አባላት ወደ ኃላፊነት መምጣት ተከትሎ “ተረኝነት” ሰፍኗል ብሎ የሌለን ምስልን ለመከሰት የተሄደበትን እርቀት እዚህ ላይ ያስተውሏል ፡፡
በነገራችን ላይ እዚህ ላይ የቡድን መብትን የሚያስቀድመው እና በቋንቋ ላይ የተመሰረተው የፌዴራል ስርዓት እስካለ ድረስ ከፍተኛ የሕዝብ ብዛት ያለው በቅደም ተከተል የስልጣን ፣ የሀብት ተጠቃሚ መሆኑን መቀበል (pragmatist መሆን) የግድ ይላል ። ይሄን የምለው ትክክል ነው እያልሁ ሳይሁን የመጫወቻ ሕጉን ከግምት በማስገባት ነው፡፡
ሐ . ተአማኒነት፣ ተቀባይነት፦
አሜሪካውያኑ የሴራ ኀልዮት አጥኝዎችና የፖለቲካ ሳይንስ ሊቃውንት ጆሴፍ ኡዚነስኪ እና ባልንጀራው ከ5 አመታት በፊት በሀገረ አሜሪካ ባካሄዱት ጥናት የሴራ ኀልዮት ጾታ ፣ ሀይማኖት ፣ ዘር ፣ ዕድሜ ሳይለይ ተቀባይነት ታማኝነት ቢኖረውም በወጣቶች ግን ይበልጥ ተቀባይነት እንዳለው አረጋግጠዋል ። ከተፈጥሮ አደጋዎች ፣ እንደ 9/11 ያሉ ሰው ሰራሽ ጥቃቶች ፣ የስራ አጥነት ፣ ተስፋ መቁረጥና ድብርት ወጣቱን የኀልዮቱ ሰለባ እንዳደረገው ጥናቱ አክሎ ጠቁሟል ። የሀገራችን ወጣቶች የኀልዮቱ ሰለባ የሆኑበት ምክንያት ከዚህ ብዙ የሚለይ አይደለም ። ስለዚህ ወጣቱ ሕልም ፣ ተስፋ ፣ ስራ እንዲኖረው በማድረግ ከሴራ ኀልዮት ምርኮኝነት ነፃ ማውጣት ከማስቻሉ ባሻገር የጥቂቶች ክፉ አጀንዳ አስፈፃሚ ከመሆን መታደግ ይቻላል ። በአንድ ጠጠር …ይሉት ይሄን አይደል !?
መ . የቡድን ማንነት፦
አንድ የህብረተሰብ ክፍልን ማለትም ነጭ ፣ ጥቁር፣ አይሁድ ፣ እስላም ኢላማ ያደረጉ የሴራ ኀልዮቶችን መንዛት ሌላው መለያው ነው ። አማራን ፣ ኦሮሞን፣ ኦርቶዶክስን ፣ እስልምናን ፣ ክርስትናንና ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎችን ኢላማ አድርገው የሚነዙ ደባዎችን ልብ ይላሉ ። ከውጭ ኤች አይ ቪ / ኤድስ ጥቁሮችን ለመጨረስ በቤተ ሙከራ የተፈጠረ በሽታ ነው። አይሁዶች ሚዲያውን በሞላ ተቆጣጥረዋል የሚሉ የሴራ ትርክቶች በአብነት ይጠቀሳሉ። ወደሀገራችን ስንመጣ ደግሞ በመካከላችን ጥላቻን ፣ መጠራጠርን ለመንዛት በመሳሪያነት እያገለገለ መሆኑን ከፍ ብሎ ተመልክቷል ።
ሰ . ፖለቲካዊ አይዶሎጂ፦
ሕዝበኝነት ሶሻሊዚም ካፒታሊዝም ቀኝ ዘመም ሆነ ግራ ዘመም አይዶሎጂዎች የየራሳቸው የሴራ የደባ ኀልዮት ትርክቶች አሏቸው። ሕዝበኞች ሉላዊነትን ካፒታሊዝምን አውሮፓ ሕብረትን ኔቶን ስደተኝነትን የሚያጠለሹ ፣ የሚያሰየጥኑ ታረኮችን ሲነዙ ። ግራ ዘመሞች በበኩላቸው ሚዲያውንና የፖለቲካ ፓርቲዎችን በባለጠጋዎች ጭፍራነት የሚወነጅሉ የሴራ ኀልዮቶችን ያነብራሉ ። የተቀሩትን አይዶሎጂዎች አሰላለፍ በዚህ አግባብ መለየት ይቻላል ፡፡
ረ . የትምህርት ደረጃ፦
መማር የሴራ ኀልዮት ምርኮኝነትን ሊቀንስ ይችላል የሚል አጠቃላይ ዕምነት ቢኖርም የእነ ኡዚነስኪ ጥናት የደረሱበት መደምደሚያ ግን ለየቅል ነው ። የድህረ ምረቃ ትምህርታቸውን ከተከታተሉ 5 አሜሪካውያን 1ዱ ለኀልዮት ልባቸውን ጆሮአቸውን ቀልባቸውን አሳልፈው የሰጡ ናቸው ይላል ፡፡
ወደ ሀገራችን ስንመጣ የተደረገ ጥናት ባይኖርም ሁለትና ከዚያ በላይ ዲግሪ ያላቸው አንዳንድ ጓደኞች በሴራ ፖለቲካ ተጠልፈው በጉንጭ አልፋ ጭቅጭቅ ልቤን ሲያወልቁኝ ስለምውል የጥናቱን ግኝት እጋራና በአመክንዮ ፣ በተጠየቅ ፣ በጥልቅ እሳቤ መሟገት ካልተቻለ የተነበበው የተሰማው ሁሉ እንደ እስፖንጅ ከተመጠጠ ታዲያ መማር ምኑ ላይ ነው !? አበው እመው ተምሮ እማይፅፈ ጾሞ የማያከፍል እንደሚሉት ፡፡
በእነዚህ ባህሪያት ማጥለያነት የትኛው የሴራ ኀልዮት ትርክት እንደሆነ ለመለየት እና አበክሮ ጥንቃቄ ለማድረግ ከውዥንብር ከመደናገር ለመውጣት ይቻላል፡፡
መውጫ
የሴራ ኀልዮቶችን ማለትም የሴራ ወሬዎችን እውነትነት እና ሀሰትነት ፈትኖ ማጣራት ኃላፊነት የሚሰማው ዜጋ ሚዲያና መንግስት ቀዳሚ ተግባር ሊሆን ይገባል። በዘመነ ማህበራዊ ሚዲያ በጥቂት ደቂቃዎች ሀገር የሚያዳርሱ የሴራ የደባ ዋና ዋና ወሬዎችን እግር በእግር እየተከታተሉ በተጨባጭና ሀቀኛ መረጃዎችን ፉርሽ ማድረግ ማክሸፍ ካልተቻለ ሊፈጠረ የሚችለውን ሀገራዊ አደጋ እያየነው ነው ፡፡
ጦር ከፈታው ወሬ የፈታው እንዲሉ። ሀገር ፣ ወገን በበሬ ወለደ ሴራ እንዳይፈታ አበክሮ በቅንጅትና በርብርብ ሊሰራ ይገባል። የጠቅላይ ሚ/ሩ እና የክልል ፕሬስ ሴክሬታሪት መደበኛ ሚዲያዎች ከእነ ማህበራዊ ገጾቻቸው መረጃን በጥራት በፍጥነት በተደራሽነት 24/7 ማሰራጨት ይጠበቅባቸዋል። አሰራራቸውን አደረጃጀታቸውን እና ብቃታቸውን ከዚህ አንጻር ቆም ብለው መፈተሽ ሰልፋቸውን ማሳመር ይጠበቅባቸዋል፡፡
ልሒቃን የፖለቲካ ፓርቲዎችና ተከታዮቻቸው በመጨረሻም መላ ሕዝብ አሉባልታ የሴራ የደባ ወሬ ሲሰሙ በተቻለ መጠን ማጣራት በተለያዩ ምንጮች ማመሳከር ፣ ማገናዘብና ማረጋገጥ ይጠበቅባቸዋል። ስውር አጀንዳ ያላቸው ኃይላት መጠቀሚያ እንዳያደርጓቸው ከመቼውም ጊዜ በበለጠ መጠንቀቅ ይኖርባቸዋል ።
ይሁንና እነዚህ ኀልዮቶች የዳበሩ የዴሞክራሲ ተቋማትና ሚዲያዎች ባሉባቸው ምዕራባውያን ዘንድ ያላቸው ተቀባይነት እንደኛ ካሉ ሀገራት ጋር ሲነጻጸሩ ያን ያህል ተፅዕኖ የማያሳድሩ መሆናቸውን ጥናቶች ያመለክቷሉ ። በአንጻሩ የዳበሩ ዴሞክራሲያዊ ተቋማት በተለይ ጠንካራ ሚዲያዎች ባልደረጁባቸው ሀገራት የሚያሳድሩት ተፅዕኖ ከፍ ያለ መሆኑን እነዚሁ ጥናቶች ያረጋግጣሉ፡፡
ሀገራችንን እንደ አብነት ብናነሳ ከሶስት አመት በፊት ለውጡ የነበረው ተቀባይነት እና ዛሬ ያለው ተቀባይነት ሲነጻጸር በተመሳሳይ ደረጃ ላይ አይገኝም ። ደጋፊን መራጭን ላለማጣትም ሆነ ለማስደሰት ሲባል የተፈፀሙ ፖለቲካው ስህተቶች የራሳቸው ድርሻ ቢኖራቸውም እንደ በሬ ወለደ አይነት ነጭ ውሸቶችን አልቧልታዎችን የሴራ ኀልዮቶችን ያህል ተፅዕኖ እንደሌላቸው ለመግለፅ የሕዝብ አስተያየት ጥናት እስኪያደርግ መጠበቅ አያስፈልግም ። የተቀናጀ የደባ የሴራ ፖለቲካ ለውጡንም የሀገራችንን መጻኢ ዕድልም አደጋ ላይ እንደጣለው ከልብ ልብ ማለት ያስፈልጋል ። መንግስት ሚዲያዎች ሀገር ወዳድ ዜጎች የችግሩን አደገኝነት የሚመጥን የተቀናጀና የተናበበ ስራ መስረት ይጠበቅባቸዋል ፡፡
በተለይ መንግስትና ሚዲያው አሉባልታው ወደ ሴራ ደባ ኀልዮት ፖለቲካ ከማደጉና በሕዘብ ዘንድ መደናገርን መጠራጠርን ውዥንብርን ከመፍጠሩ በፊት የሆነውን ከስር ከስር ለሕዝብ ማሳወቅ ይገባል ። ቀደም ሲል እንዳሳሰብሁት አሰራርን አደረጃጀትን ከዚህ አንጻር መቃኘት መከለስ ያስፈልጋል ። የመንግስት አሰራር ከዚህ ይበልጥ ግልፅ ፣ አሳታፊና ተጠያቂ ሊሆን ይገባል ። ጦር ከፈታው ወሬ የፈታው ነውና ብሂሉ ሀገር ለውጡ በበሬ ወለደ ውሸት እንዳይፈታ በትጋት መስራት ይገዳል ፡፡
በሀገራችን የመጣው ለውጥ የሴራ የደባ የመጠላለፍ ፖለቲካ ጥላ እንዳጠላበት እና ከፊቱ አደጋ እንደተደቀነበት ምልክቶችን እያየን ነው። ይሄን ለውጥ ዳር ለማድረስ ያጠላበትን ጥላ የመግፈፍ የዜግነት ድርሻችንን የመወጣት ኃላፊነት ተጥሎብናል ። ይሄን ተማፅኖ የማቀርበው ይሄን ለውጥ ከእነ ውስንነቶቹ ከማሳካት ዳር ከማድረስ በቀር አማራጭም አቋራጭም አለን ብዬ ስለማላምን ነው። በታሪካችን ከአንዴም ሁለት ሶስቴ ይሄን መሰል አጋጣሚዎችን አባክነናል። አሁን ግን ለማባከን የሚያቀናጣ ሌላ ዕድል እጃችን ላይ የለም። ይሄን ታሪካዊ መታጠፊያ በእንዝህላልነት ማባከን በአግባቡ አለመጠቀም ልንገምተው ወደማንችል መቀመቅ ተያይዞ ለመውረድ የመወሰን ያህል ሆኖ ይሰማኛል። ስለሆነም ከለውጡ ጎን ልንሆን ይገባል።
ሀገራችን ኢትዮጵያ በጀግኖች ልጆቿ ታፍራና ተከብራ ለዘላለም ትኑር !
አሜን።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን የካቲት 13/2014