ፋሽስት ጣልያን ለአርባ አመት ዝግጅት አድርጎ በድጋሚ ኢትዮጵያን ለመቆጣጠር በ1928 ኢትዮጵያ ላይ ወረራ ፈጸመ ። ማይጨው ላይ ኢትዮጵያውያንን በዓለም በተከለከለ የመርዝ ጋዝ ጭምር በመጠቀም አሸንፎ አገሪቱን ተቆጣጠረ ። ጦሩን ይመራ የነበረው ግራዝያኒ በድል አድራጊነት ኢትዮጵያን ስለያዘ በጣልያን መንግሥት የጣልያን የምሥራቅ አፍሪካ ግዛት የበላይ ገዥ ተደርጎ ተሾመ ።
ፋሽስት ጣልያን ኢትዮጵያን ከያዘ ከአንድ አመት በኋላ የኔፕልስ ልዕልት በመወለዷ ማርሻል ሮዶልፍ ግራዝያኒ የአዲስ አበባ ሕዝብ ተሰብስቦ ደስታውን እንዲገልጽ አዘዘ ። ይህም የተደረገው ከገነተ ልዑል ቤተመንግሥት ግቢ (የቀድሞው የግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ መኖሪያ ቤተመንግሥት የአሁኑ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ዋናው ግቢ) ሲሆን፣ ደስታውን ሊገልጽ ለሚወጣው ሕዝብ ለእያንዳንዱ ሁለት ማርትሬዛ እንደሚሰጥ ጭምር ጣልያኖች ይፋ ማድረጋቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ ።
በገነት ልዑል ቤተመንግሥት ወደ 3ሺ የመጠጉ ኢትዮጵያውያን ተሰብስበዋል፤ ግራዝያኒን ጨምሮ መኮንኖቹና በወቅቱ በጣልያን ተመድቦ የነበረው የአዲስ አበባ ከንቲባ ጎይዶ ኮርቴሲን በበዓሉ ላይ ታድመው ነበር። በእዚህ ወቅት ነበር አንድ ክስተት የተፈጠረው ።
በዕለቱ በገነተ ልዕል ግቢ ውስጥ በተለያየ አቅጣጫ ወደ ሰባት የሚደርሱ ቦምቦች ፈንዱ ። ጀግኖቹ አብርሃ ደቦጭ እና ሞገስ አስገዶም በወረወሩት ቦምብ ግራዝያኒ እና ሹማምንቱ ቆሰሉ ። ግራዝያኒ ወደ ሕክምና እየተወሰደ በከተማዋ ነዋሪ ላይ ግድያ እንዲፈጸም አዘዘ ። ይህ የሆነው የካቲት 12 ቀን 1929 ዓ.ም ነበር ። ዘንድሮ 85 ዓመት ሞላው ።
ፋሽስቶቹ ጭፍጨፋውን ከቤተመንግሥቱ ግቢ ከነበሩት ተሰብሳቢዎች ጀመረው ወደ ነዋሪው ዘለቁ ። በዚህም ተነሳስተው በሦስት ቀናት ውስጥ ባደረሱት ጭፍጨፋ ከ30ሺህ በላይ ንጹሃን ኢትዮጵያውያን ተጨፈጨፉ ። በጭፍጨፋው አካል ጉዳተኛ፣ አዛውንቶችና ሕፃናት ጭምር በአሰቃቂ ሁኔታ ተገድለዋል ።
የከተማዋ ደሳሳ ጎጆዎች ሳይቀሩ ቤንዚን እየተርከፈከፈባቸው እንዲቃጠሉ ሲደረግ፤ ከቃጠሎው ለማምለጥ የሚወጡትን ደግሞ ፋሽስቶች በር ላይ እየጠበቁ በመትረየስ ጨፈጨፏቸው ። በአጠቃላይ በጭፍጨፋው ብሔር ቋንቋ ፆታና እምነት ሳይነጥሉ በቆዳው ኢትዮጵያዊ (ጥቁር) ነው ያሉትን ሁሉ ገደሉ ። አብርሃ ደቦጭና ሞገስ አስገዶም አምልጠው ደብረ ሊባኖስ ተክለሃይማኖት ገዳም ተሸሽገዋል በመባሉም የጣልያን ሰዎች በገዳሙ ገብተው መኖኮሳቱን ሁሉ ገደሉ ።
በጭፍጨፋው በአዲስ አበባ ደም እንደ ጎርፍ ፈሰሰ። የከተማዋ አነስተኛ መንገዶች ሳይቀሩ ቀባሪ አጥተው በሬሳ መሞላታቸውን የታሪክ ሰነዶች አስነብበዋል ። ከመጀመሪያው ጭፍጨፋ ሁለት ቀን በኋላ በጣልያን የታተመው ዴል ፖፖሎ ጋዜጣ ‹‹አዲስ አበባ ከጥቁሮች ጸድቷል፤ ሁለት ሺ ጥቁሮችም ተይዘው ታስረዋል›› በሚል በኩራት ዜና አውጥቶ አስነበበ ።
ጣልያኖች በየካቲት 12ቱ ጭፍጨፋ ኢትዮጵያውያንን አደብ ማስገዛት፣ተስፋ ማስቆረጥ ይቻላል፤ ይህ ሲሆን በጣልያን ጸጥ ለጥ ብለው ቅኝ ይገዛሉ ብለው ቢያስቡም፤ ኢትዮጵያውያን እንሞታለን እንጂ ቅኝ አንገዛም ብለው ነው ትግላቸውን ያጠናከሩት ። ጣልያኖች በወቅቱ ያደረሱት ጭፍጨፋ ዘግናኝ ቢሆንም ሕዝቡ ግን አልተንበረከከም። የገጠሩ ሕዝብ ከአርበኞች ጋር እየሆነ በዱር በገደል እየተንቀሳቀሰ ጣልያኖችን መውጫ መገቢያ አሳጣ ። መንግሥትና መሪ በሌለበት አገር በየቦታው የጎበዝ አለቃ እየመረጠ ፋሽስቶችን እየገደለና መሣሪያቸውን እየነጠቀ ለአምስት ዓመታት ታገለ ። በዚህም ትግል ወራሪውን ፋሽስት ድል አድርጎ አባረረ ።
ይህ የኢትዮጵያውያን የተጋድሎ ታሪክ ፊትም የነበረ ከየካቲት 12 ሁለቱ የፋሽስቶች ጭፍጨፋ በኋላም የቀጠለ ነው ። ኢትዮጵያውያን በወራሪው የሶማሌያው ጦር ላይም ተመሳሳይ አንጸባራቂ ድል ተቀዳጅተው የአገራቸውን ሉአላዊነት አስጠብቀዋል ። በቅርቡም ከሀዲው ትህነግ በሰሜን እዝ ላይ የፈጸመውን የክህደት ድርጊት ተከትሎ ኢትዮጵያውያን በአጭር ጊዜ ውስጥ ተቀናጅተው በወሰዱት እርምጃ ቡድኑን ሰባብረው ጥለውታል ።
ቡድኑ በአማራና አፋር ክልሎች ላይ የፈጸመውን ወረራና በኃይል ሥልጣን ለመያዝ የከፈተውን ጦርነትም በድል ተወጥተዋል ። ድጋፍ ሲያደርጉላቸውና ለድላቸው ሲቋምጡ የነበሩ አሜሪካና ምዕራባውያን በተባበረው ኢትዮጵያዊም አፍሪካዊም የ«በቃ» ድምጽ አደብ በማስያዝ፤ ይህም ኢትዮጵያውያኑ የአያት ቅድመ አያቶቻቸውን ታሪክ በምዕራባውያኑ ላይ ደግመው ገልጠውታል ።
ዳያስፖራዎቹ በኖሞር ዘመቻው ብቻ አልተገቱም ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ የኢትዮጵያ ኃይሎች በወራሪው የትህነግ ታጣቂዎች ላይ ድል መቀዳጀታቸውን ተከትሎ ዳያስፖራው ገናንና ጥምቀትን በአገሩ እንዲያከብር ላቀረቡት ጥሪ ፈጣን ምላሽ በመስጠት ወደ አገራቸው በመምጣት ተግብረውታል ። ዳያስፖራው መሪ ሲጠራ አቤት ይባላል ብሎ ወደ አገሩ ሲተም የኢትዮጵያ ጠላቶች በሌላው ግንባርም ድል ተመቱ ።
ኢትዮጵያውያኑ ወደ አገር ገብተው አገርም፤ መዲናዋ ሸገርም ሰላም እንደሆነች ሲያሳውቁና የልደትና የጥምቀት በዓላትን በሰላም ሲያከብሩ፤ ምዕራባውያኑ፣ ተባባሪዎቻቸውና ዓለምአቀፍ ሚዲያዎች ሟርታቸውን ለማስተጋባት ያልለፈለፉትን ያህል ድምፃቸውን አጥፍተው ተቀመጡ ። የዳያስፖራው ወደ አገሩ መምጣት የአገሩን ሰላም ከማረጋገጡም ባሻገር፤ በኮሮና ወረርሽኝ የተቀዛቀዘውን ኢኮኖሚም ማነቃቃታቸው ለኢትዮጵያ ጠላቶች ሌላ የውርደት ማቅ ያለበሰ ታላቅ ገድል ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል ።
35ኛው የአፍሪካ ኅብረት የመሪዎች ጉባኤና ከእሱ ጋር ተያያዥ የሆኑ በርካታ ስብሰባዎች በአዲስ አበባ እንዳይካሄዱ ምዕራባውያኑን ጨምሮ የኢትዮጵያ ጠላቶች ያልፈነቀሉት ድንጋይ አልነበረም ። ይህን ጥረታቸውን ገደል መክተት የተቻለው ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ከጦርነቱ ባልተናነሰ መልኩ ከፍተኛ የሆነ የዲፕሎማሲ ሥራ ማካሄዳቸው ነው ።
ይህ ጉባኤና ከጉባኤው ጋር የተያያዙ የተለያዩ ስብሰባዎች በከተማዋ ለአንድ ሳምንት መካሄዳቸው ሸገር ሰላም አይደለችም፤ በትህነግና ሸኔ ሰራዊት ተከባለች፤ አዲስ አበባን አልፎም ተርፎ ኢትዮጵያን ለቃችሁ ውጡ ወደ ኢትዮጵያም እግራችሁን እንዳታነሱ ሲሉ የነበሩ ጠላቶቻችን ሌላ ቅሌት የተከናነቡት በኢትዮጵያውያን የተባበረ ክንድ በተደረገ ጥረት ጉባኤውን እንደ እስከ አሁኑ ሁሉ በኢትዮጵያ አዲስ አበባ እንዲካሄድ ማድረግ በመቻሉ ነው ። በጉባኤው ላይ ከተገኙት የ53 አገራት መሪዎች በተጨማሪ 340 የሚደርሱ ጋዜጠኞች ተገኝተው ሂደቱን ዘግበዋል ። በተለይ ጋዜጠኞቹ በአዲስ አበባ መገኘታቸው ከተማችን ሰላም ስለመሆኗ ጥሩ ማሳያ ነበር ።
ይሄም ሆኖ ኢትዮጵያ ጠላቶቿ አሁንም አልተኙም። አሸባሪው ትህነግ በአፋር ክልል ላይ አሁንም ትንኮሳ ብቻ ሳይሆን ጥቃትም እየፈጸመ ነው ። ሙሉ ለሙሉ ያልለቀቃቸው የአማራ ክልል አካባቢዎች እንዳሉም ይነገራል ። ምዕራባውያኑ አሁንም የቡድኑን አጀንዳ ይዘው እየተንቀሳቀሱ ናቸው ። ሰሞኑን ለአሜሪካ ኮንግሬስ የውጭ ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ ከቀረበ ረቂቅ ሕግ መረዳት የሚቻለውም ይህንኑ ነው ።
አሁንም ረቂቅ ሕጉ ኢትዮጵያን ሊጎዳ እንደሚችል ዜጎችና የተለያዩ አካላት እያሳሰቡ ናቸው ። ረቂቅ ሕጉ በሌለ መረጃ ላይ ተመስርቶ የተዘጋጀ እና ጠንከር ያሉ ዕርምጃዎችን በኢትዮጵያ ላይ ለመውሰድ የሚያስችል ነው ተብሏል ። ረቂቅ ሕጉ “Ethiopia Stabilization, Peace and Democracy Act” በሚል ርዕስ የቀረበ ሲሆን፣ በ25 ገጾችና በ12 ክፍሎች የቀረቡ አንቀጾችን የያዘ ነው ።
በመሆኑም መንግሥት የሚሠራው የዲፕሎማሲ ሥራ እንዳለ ሆኖ የአሸባሪው ትህነግና ተባባሪዎቹ ሴራ እስካልጠፋ ድረስ የኢትዮጵያ ቀኝ እጅ እየሆነ የሚገኘው ዳያስፖራው አሁንም ተባብሮ ይህን ረቂቅ ሕግ በመቃወም እንዲመክን ማድረግ ላይ አተኩሮ መሥራት ይኖርበታል ። ይህን በማድረግ እንደ እስከ አሁኑ ሁሉ ኢትዮጵያውያን በተዘጋጀላቸው ወጥመድ ሳይያዙ አገራቸውን ከጥቃት መታደጋቸውን መቀጠል ይጠበቅባቸዋል ።
የካቲት 12ቱ ጭፍጨፋ ኢትዮጵያውያን ለነፃነታቸው ያደርጉት የነበረውን ተጋድሎ እንዳላቆመው፤ ይልቁንም በእልህ ተጋድለው ለድል እንዳበቃቸው ሁሉ፤ የዚህ ዘመን ኢትዮጵያውያንም ለየትኛውም የውጭም ሆነ የውስጥ ጠላቶቻችን ሴራ ሳይሸበሩ ሳይንበረከኩ በድል ላይ ድል እያስመዘገቡ መጓዝ ይኖርባቸዋል ። ይህ ሲሆን ነው ኢትዮጵያዊነት ለፈተና ተንበርክኮ እጅ ያለመስጠት መሆኑ በተግባር የሚገለጸው ።
ኃይለማርያም ወንድሙ
አዲስ ዘመን የካቲት 13/2014