በትግራይና በውጭ የሚገኙ ወታደራዊና ሲቭል አመራሮች በዚያ ሰሞን በሚስጥር ለስድስት ተከታታይ ቀናት በዙም ባደረጉት ስብሰባ ኢትዮጵያን የማፍረስና በፍርስራሿ ላይ ታላቋን ትግራይ እንዴት እንደምትመሠረት ስትራቴጂ ነድፈዋል። የድርጊት መርሀ ግብር በመቅረጽ ተልዕኮ ተከፋፍለዋል። ከሁሉም በላይ ግን ትግራይ ጦርነቱን በአሸናፊነት ልትወጣ እንደሚገባ አጽንኦት ይሰጥና፤ 20 አንኳር ነጥቦችን ይዘረዝራል። እውነት ለመናገር በመከላከያ ተጠልፎ የወጣውን ይሄን ደባም ሆነ በጂኦፓለቲክስ ፕሬስ፤ “ከባዝማ እስከ ኢትዮጵያ” በሚል ርዕስ አደባባይ በተሰጣው ታላቅ ሴራ ያረጋገጥሁት አሸባሪው ህወሓት ኢትዮጵያንን አምርሮ እንደሚጠላና ይሄን የመረረ ጥላቻውንና የስልጣን ጥሙን ለመቁረጥ ምንም ከማድረግ የማይመለስ መሆኑን ነው። ለነገሩ “ኢትዮጵያን ለማፍረስ ሲኦልም ቢሆን እንወርዳለን።” ሲል እቅጩን ነግሮን የለ። የወለደ አንጀት አይቆርጥም ካላልን በስተቀር። የአሸባሪው ህወሓት የቀን ቅዠት ኢትዮጵያ የምትባል ሀገርን አፍርሶ በትኖና ከዓለም ከካርታ ፍቆ በምትኩ “ታላቋን የትግራይ ሪፐብሊክ ፤” መመስረት መሆኑን ከነገረን ግማሽ ክፍለ ዘመን ሊሞላው በጣት የሚቆጠሩ ዓመታት ቀርተዋል።
የትግራይን ሀገረ መንግስት ለመመስረት ኢትዮጵያ ውስጥ ሶስት አብዮቶች መፈጠር አለባቸው ይላል ይህ የዙም ሟርት። የመጀመሪያው አብዮት ኦሮሞ “ፊንፊኔ ኬኛ” ብሎ እንዲያምጽ ከኦነግ ጋር መስራት። ተጋሩዎች አስፈላጊውን ዋጋ ከፍለው የፊንፊኔን ጉዳይ በማነሳሳት የኦሮሚያ አካል ካልሆነች በሚል እሳት መጫር። ያው ድሮም በህቡዕም ሆነ በአደባባይ ተቀናጅተው የሚሰሩ መሆናቸው ፀሐይ የሞቀው ሀቅ ቢሆንም ሰሞኑን ኢትዮጵያን ለማፍረስ ግንባር መፍጠራቸውን በአደባባይ ነግረውናል። ለ27 ዓመታት በኦሮሞ ህዝብ ላይ ህልቆ መሳፍርት የሌለው ግፍ ሲፈጽም ከኖረ አረመኔ ጋር በመቆም ኦነግ ሸኔ የኦሮሞ ሕዝብ ጠላት መሆኑን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ አረጋግጧል። ሁለተኛው በአፋርና በሶማሌ የተፈጠረውን ግጭት ማባባስ። በአፋርና በኢሳ ተፈጥሮ የነበረውን ግጭት መሆኑ ነው። ትግራይ በአፋር ላይ ጦርነት በመክፈት የህልውና ስጋት /existential treat/መፍጠር። በትግራይና በሱማሌ የሚገደለው አፋር ሳይወድ በግዱ ኤርትራና ጁቡቲ ካለው አፋር ጋር መተባበር ይጀምራል።
በአፋር ላይ የተከፈተውን ወረራና 270 ንጹሐን አፋሮች በፈንቲ ረሱ ዞን በጋሊኮማ ጊዜያዊ መጠለያ የተጨፈጨፉት በዕቅድ መሆኑን እዚህ ላይ ልብ ይላል። የአፋር ጦርነት ወደ ሶማሌ ክልል እንዲዛመት፤ የተባበረውን አፋር በሱማሌ በጅቡቲና በሶማሊያ ካለው ሶማሌ ጋር ጦርነት ውስጥ እንዲገባ በማድረግ የታላቋን ሶማሊያ ብሔርተኝነት ትቢያውን አራግፎ ከፊት ማምጣት። ሶስተኛው አብዮት የትግራይ ሀገር የመሆን ዕቅድ ተግባራዊ መሆን ሲጀምር ከአማራና ከአፋር ክልሎች ጋር የመሬትና የወሰን ጥያቄ በማንሳት የትግራይ ሕዝብ ከእነዚህ ሕዝቦች ጋር እስከወዲያኛው እንዲቆራረጥ ማድረግ። በማይካድራም ሆነ ሰሞኑን በራያ ቆቦ አጋምሳ የተፈጸሙ ዘግናኝ ጭፍጨፋዎች ሆን ተብለው ሁለቱን ሕዝቦች ለመለያየት ታቅደው መፈጸማቸውን ያጤኑአል። ይህ እፉኝት ጦርነቱን ሕዝባዊ ማድረግ የመረጠውም ትግራዋይን ከኢትዮጵያውያን ወገኖቹ ለያይቶ የትግራይን ሕዝብ ለዘላለም ለማገትና በሰብዓዊ ጋሻነት ለመጠቀም ነው። አሸባሪው ህወሓት በሁለት ክልሎች ወረራ የፈጸመውም ሆነ ጦርነቱን ሕዝባዊ ያደረገው ትግራዋይ ከኢትዮጵያውያን ከአማራና ከአፋር ደም እንዲቃቡና እንዲለያዩ አበክሮ ማቀዱን ያረጋግጣል። በዚሁ የዙም ውይይት ከኤርትራ ጋር ጦርነት ማስነሳትና የመንግስት ለውጥ እንዲመጣ ማድረግ ሌላው የሴራው ግብ ነው።
አሸባሪው ህወሓት ኢትዮጵያን የማፍረስ እኩይ አላማውን ለማሳካት የማይፈነቅለው ድንጋይ የለም። በለውጡ ማግስት በመማጸኛ ከተማው መቐሌ መሽጎ ለጦርነት ሲዘጋጅ ምዕራባውያን ዕቅዱ ቀጣናውን ወደለየለት ትርምስና ቀውስ የሚከት ስለሆነ ከፌደራል መንግስት ጋር ያለውን ልዩነት በውይይት እንዲፈታ ጫና ሲያደርጉበት የሀገሪቱን 80 በመቶ ሰራዊትና የጦር መሳሪያ በእጁ እንደሆነ በመከላከያ ያሉ ከፍተኛ ወታደራዊ የአመራር ቦታዎችም በእሱ ሰዎች የተያዙ ስለሆኑ ጦርነቱ ወደ ቀጣናው እንደማይስፋፋ በእኔ ይሁንባቸው በማለት አሳምኗቸው ሲያበቃ የሽንፈት ጽዋውን ሲጎነጭና የሽንፈት ከሉን ሲከናነብ ደግሞ ምዕራባውያኑና አለማቀፍ ማህበረሰብ ወደ ግጭቱ ለማስገባት ቀጣናውን የማተራመስ እኩይ ዕቅድ አቧራውን አራግፎ ወደፊት እንዳመጣው ስንታዘብ ለእብሪቱ ለማንአለኸኝነቱና ለስልጣኑ ሲል የሚሄድበትን እርቀት ልብ እንድንል ያስገድደናል። ይህ ሴራው ሲከሽፍ ደግሞ የዐብይ መንግስት የትግራይን ሕዝብ ሊያጠፋው ነው፤ አህዳዊ አገዛዝ ሊያሰፍን ነው፤ ንጹሐን ተጨፈጨፉ፤ አስገድዶ መድፈር ተፈጸመ ፤ ዐብይ ከእነ ኢሳያስና ፎርማጆ ጋር ተባብሮ ጸረ ምዕራባዊ የሆነ ለቻይና የሚያሸረግድ ቀጣናዊ ትብብር ለመፍጠር እየሰራ ነው በማለት እየየውን ያቀልጠዋል።
አሸባሪው ህወሓት እንዲህ የሚላላጠው ዐብይን በሌላ ጠቅላይ ሚንስትር ለመቀየር ወይም ብልጽግና በኒዎ ሊበራሊዝም አልያም በልማታዊ መንግስት ለመተካት አይደለም። ህወሓት ጣረ ሞት ላይ ሆኖም የሚፈራገጠው ኢትዮጵያን ለማፍረስ ለመበተን መሆኑን ያለ አንዳች እፍረት በአደባባይ ነግሮናል። ለዚህም ሲኦል ድረስም ለመውረድ ፎክሯል። በኢትዮጵያ ፍርስራሽ ላይ ታላቋን ትግራይ ለመምስረት ካርታ ነድፎ “ሕገ መንግስት” አርቅቆ ከተቀመጠም ሰነባብቷል። ጸቤ ከዐብይ ጋር ነው የሚለው ማደናገሪያና ማዘናጊያ ነው። ጸቡ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር መሆኑን በሰሜን እዙ ጭፍጨፋና ዘረፋ፤ በማይካድራ በጋሊኮማና በአጋምሳ ጭፍጨፋው ከማረጋገጥ አልፍ ኢትዮጵያን ለማፍረስ ሲኦልም ቢሆን እወርዳለሁ በማለት እቅጩን ነግሮናል።
በዚሁ ጋዜጣ ነጻ ሀሳብ ላይ “ከባዝማ እስከ ኢትዮጵያ” በሚል ርዕስ ባስነበብሁት መጣጥፍ ጂኦፓለቲክስ ፕሬስ፤ Command and Control Fusion Center /C2FC/CCFC/ ወይም” ፕሮጀክት ባዝማ” በተሰኘው መሠሪና አደገኛ ሰነድ ዐብይ ኢሳያስና የሱማሊያው ፎርማጆ አንድነት ፈጥረው ቀጣናውን በበላይነት የመቆጣጠር ዕቅድ እንዳላቸው ያራግባል። በቀጣናው የሚፈጠረው ቀውስ በሳኡዲ አረቢያና በተባበሩት የአረብ ኤሚሬቶች ስጋት መደቀኑ እንደማይቀር ይሄው አደገኛ ሰነድ ይለፍፋል። ግጭቱን ዓለም አቀፍ ለማድረግና የኃያላን መንግስታትን ትኩረት በመሳብ በሚፈጠር ግርግር ከተጠያቂነት ማምለጥና ወደ ስልጣን መመለስ የህወሓት የመጨረሻ ግብ መሆኑን እዚህ ላይ ልብ ይሏል። የሚያሳዝነው ምዕራባውያን የኢትዮጵያን ወቅታዊ ተጨባጭ ሁኔታም ሆነ ታሪኳን የተረዱት ህወሓትና ሸኔ ኦነግ በነበሩት የተሳሳተ ተረክ መሆኑ ነው። በአውሮፓውያን አረዳድ ኢትዮጵያ ወደለየለት ቀውስና መፍረስ ልትገባ የቀራት አንድ ሐሙስ ነው። የተሳሳተ መነሻ የተሳሳተ መደምደሚያ ላይ ያደርሳል እንዲሉ፤ ህወሓትንና መሰሎቹን ወደ ስልጣን ማምጣት የራስን እድል በራስ መወሰን እስከ መገንጠል የሚለውን ጥያቄ በቀላሉ በውሳኔ ሕዝብ ለመቋጨት ያመቻል የሚል የተሳሳተ መደምደሚያ ላይ መድረሳቸው ስሁት መንገዳቸውን ያጋልጣል። በእነሱ ግምገማ ኢትዮጵያ ውስጥ ይህን ጥያቄ የሚያነሱ ኃይሎች እንዳሉ የተሳሳተ መደምደሚያ ላይ ተደርሷል። ይህን የተሳሳተ ግምገማና መደምደሚያ ያስጨበጠው ደግሞ ህወሓት ስለመሆኑ አፍን ሞልቶ መናገር ይቻላል። በ21ኛው ክፍለ ዘመን አውሮፓውያንና አሜሪካውያን ብራስልስና ዋሽንግተን ሆነው የሀገራትን እጣ ፈንታ ለመወሰን ሲንቀሳቀሱ እንደ ማየት ምን የሚያበግን ነገር አለ። ኢትዮጵያ እንደምትበታተን ደምድመው ብትንትኑ ግን እንደ ሶማሌ ላንድ በጅምር እንዳይቀር፤ እንደ ዩጎዝላቪያ ብተና “በስኬት” እንዲጠናቀቅ ህወሓትን ለቅርጫው በአጋፋሪነት፤ ዐብይን እንደ ሚሎሶቪች በሰብዓዊ ፍጡር ላይ በተፈጸመ ወንጀል በዓለም አቀፉ የወንጀል ችሎት ማቆምን በጀ ብለዋል። ለዚህ ነው የእፉኝቱ ህወሓት ሴራ የመንግስት ለውጥ ከማምጣት ያለፈ ሀገር የማፍረስ ታላቅ ደባ ነው የምለው።
ኢትዮጵያውያን ዝናብና ቁር ሳይበግራቸው በነቂስ ወጥተው እስከ ሌሊቱ ሰባት ሰዓት ተሰልፈው በአንጻራዊነት ነጻ ተአማኒና ፍትሐዊ ምርጫ በማድረግ ጠንካራ ማዕከላዊ መንግስት እንዲኖራቸው በወሰኑበት ማግስት፤ በዴሞክራሲ በዜጎች ነጻነት በፍትሕና በዜጎች ሉዓላዊ የስልጣን ምንጭነት እናምናለን የሚሉት ብራስልስና ዋሽንግተን ቃላቸውን አጥፈው በአሸባሪነት ለተፈረጀና ላለፉት 27 ዓመታት በፈጸመው ህልቆ መሳፍርት የሌለው ግፍና ዘረፋ የኢትዮጵያ ሕዝብ አንቅሮ የተፋውን ነፍሰ በላ ቡድን ወደስልጣን ለመመለስ በተቃራኒው በዴሞክራሲያዊ ምርጫ የተመረጠውን ዐብይ ለማግለል መዶለታቸው የፍርደ ገምድልነታቸውን ጥግ ቁልጭ አድርጎ ያሳያል። አሸባሪው ህወሓት በጦርነት አሸንፎ አራት ኪሎ መግባት ካልቻለ በሚል ሌላ የጡት አባትነት ዕቅድ/plan b/ ማዘጋጃታቸው ይሄን ያረጋግጥልናል። ዕቅዱ በኢትዮጵያ ህወሓትን ያሳተፈ ብሔራዊ ምክክርና ድርድር ማድረግና የሽግግር መንግስት መመስረት ነው። ሰሞነኛው የጄፍሪ ፌልትማን ሶስተኛ የቀጣናው “ጉብኝት” የዚህ ፕሮጀክት አካል ነው። ሰሞነኛው የአፍጋኒስታን ቀውስ የአሜሪካን የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ መሳለቂያና መዘባበቻ አድርጎ የሰውየውንም ሆነ የእነ ብሊንከንና ሱዛን ቅስም ባይሰብረው ኖሮ አሜሪካ አሸባሪውን ህወሓት ለመታደግ የማትፈነቅለው ድንጋይ አይኖርም ነበር።
ምዕራባውያን ይህን አላማቸውን ለማሳካት የመረጃና የፕሮፓጋንዳ ጦርነቱን እንዴት እንደሚመሩት ሳይቀር ስትራቴጂ ነድፈዋል። በአሸባሪው ህወሓትና በኢፌዲሪ መንግስት መካከል የሚካሄደው ጦርነት አስመልክቶ የሚወጡ ዘገባዎች የኢትዮጵያን መንግስት በሚጠቅም መልክ እንዳይዘገቡ ያስጠነቅቃል። በተቃራኒው አሸባሪዎቹን ህወሓትና ኦነግ ሸኔን እንዲጠቅሙ ተደርገው መቀረጽ/frame/እንዳለበት አቅጣጫ ይሰጣል። ይህን አካሄድ የሶሪያን መንግስት ለመገልበጥ እና የቻይናውን ፕሬዝዳንት ዥን ፒንግን ለማጠልሸት የባዝማን ፕሮጀክት እንደተጠቀመበት ጅኦፓለቲክስ ፕሬስ ያስታውሳል። ይህ የባዝማ ህዋስ እንደ ማርቲን ፕላውት ታዋቂ የሚዲያ ሰዎችን ጋዜጠኞችን የዩኒቨርሲቲ ልሒቃን ጠበቃዎችን የዴሞክራሲ ወትዋቾችን የግል የደህንነትና የስለላ ተቋማትን ዓለም አቀፍ ግብረሰናይ ድርጅቶች ወዘተረፈ ያካተተ ነው። እንግዲህ ይህ ስብስብ ነው ማንኛውንም ዘገባ መጣጥፍ ፕሮግራም እየገመገመ የሚያሳልፈው። ሀገራችን እውነትንና ፍትሕን ታቅፋ የቀረቸው ተረኳን የተነጠቀችው እንዲህ ባለ ሴራ ነው። የሁሉንም ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች ዘገባዎች ተመልከቱ ሁሉም ሽብርተኛውን የሚያሞከሹ ሀገራችንን የሚያጠለሹ ናቸው።
እንደ አንክሮ
በመላው ዓለም የሚገኙ የአሸባሪው ህወሓት ፖለቲካዊና ወታደራዊ ጭፍራዎች ለስድስት ቀናት በዙም ያደረጉትን ወይይት እኩይ ዓላማና ያስቀመጡትን ግብ ከ”ባዝማ ፕሮጀክት”እና አሁን እየፈጸሙ ያለውን ወረራና በቤኒሻንጉል ጉምዝ በተደጋጋሚ ሰርጎ በመግባት የታላቁን የህዳሴ ግድብ ግንባታ ለማስተጓጎል የሚያደረጉትን ጥረት ለተመለከተ ሀገር ለማፍረስ ተማምሎ መነሳታቸውን ያረጋግጣል። በዋሽንግተን ዩኒቨርሲቲ የታሪክ መምህር የሆነው ሬይሞንድ ጆናስ ስለ አጼ ምኒልክና አድዋ በሚያወሳው ማለፊያ መጽሐፉ፤ “ልንቀዳጀው የሚገባን ነፃነት ልንከላከለው የሚገባ መሆን አለበት።” እንዳለው ካለፉት ሶስት ዓመታት ወዲህ የተቀዳጀነውን ነጻነት የሚገባን ስለሆነ ከታሪካዊ ጠላቶቻችን ከምዕራባውያን ከባንዳዎችና ከተላላኪዎች ህወሓትና ሸኔ ኦነግ ልንጠብቀውና ልንከላከለው ይገባል።
ሀገራችን ኢትዮጵያ በጀግኖችና እውነተኛ ዜጎች ታፍራና ተከብራ ለዘላለሞ ትኑር !
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)
አዲስ ዘመን ነሐሴ 24/2013 ዓ.ም